መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » የፈካ አበባ

የትምህርቱ ርዕስ | የፈካ አበባ

 

ወዳጄ ሆይ !

ሞት በተጋረጠበት ዘመን በሕይወት የሚያሻግር እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ከሞት ውጭ ያሉ ፈተናዎች ሕይወትን እንድትወዳት አሊያም እንድትጠላት ያደርጉሃል ። ሕይወትን የምትወዳት ታመህ ለመዳን ፣ ተሰደህ ጥግ ለማግኘት ፣ አጥተህ ለመባረክ ስትሻ ነው ። ሕይወትን የምትጠላት ደግሞ በመሰልቸትህና ዛሬ የዓለም ፍጻሜ ሆኖ ሲሰማህ ነው ። ከፊት ለፊት ያለው ጅረት አጭር ቢሆንም ሩቅ ነው ። ከፊትህ ያለው ደራሽ ውኃ ከኋላህ ሲሆን ትዝታም አይኖረውም ። 

ወዳጄ ሆይ !

የደቦ ሹመት በደቦ ጩኸት ያበቃል ። የሹመት ሠረገላህን መውረድህን እያሰብህ ተሳፈራት ። ስትወርድም ያንተ የሆነችውን ሀብት አትተዋት ። መክበር እንዳለ መዋረድ ፣ ማግኘት እንዳለ ማጣት አለና ከመሬት አትራቅ ። ወደ ሰማይ ማየት እንጂ ወደ መሬት እያዩ መኖር ስጋት ነው ። እርሱም የዚህ ዓለም ከፍታ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ናፍቆት በውስጥህ ከሌለ እንደ ሰው ሳይሆን እንደ ዕቃ እየኖርህ ነው ። ከሩቅ የመጣው የሚመዝንህ አብሮህ ላለው በምትሰጠው ክብር ነው ። እደርሳለሁ ሳትል ዛሬን ካየህ ነገም በእግዚአብሔር እጅ ነው ። ለሞቱ ቀርቶ ላሟሟቱ የሚለቀስበት ዘመን ነውና ተግተህ ጸልይ ። የሰጠ እጅህ ሲነከስ የተቸነከረውን መድኃኔ ዓለምን አስታውስ ። ደግ አልቆ የተሻለ ክፉ ሲመረጥ ያ ዘመን የዘመን ልቅላቂ ነው ። ወዳጅ በዕንቈም አይገዛም ። 

ወዳጄ ሆይ !

ስለ ፀሐይ አመስግነህ ፣ ስለ ዝናብ እግዚአብሔርን አወድሰህ የማታውቅ ከሆነ ስለሌላ ለማመስገን አትጠበቅም ። ጠበሉ ሲቀዘቅዝ እሰይ እሰይ ፣ ሲያቃጥልም እሰይ እሰይ ይባላል ። የተሰጠህን ነገርም በምስጋና ተቀበል ። የተሞላ ሰው እስኪያወጣው ፣ ጥይት ያቃመ ሰውም እስኪጨርሰው ጠብቀው ። ባዶ ሆኖ ታገኘዋለህ ። 

ወዳጄ ሆይ !

መልእክት መልአክ ይፈልጋል ። መልአክ የሌለው መልእክት እግር አልባ ፣ መልእክት የሌለው መልአክ ዱዳ ናቸው ። ዛሬ ትላንት ፣ አንተም ሬሳ ሳትባል እወቅበት ። ንዴት የትዕግሥት ድህነት ነው ። ንዴት ካጣኸው በላይ ያሳጣሃል ። ንዴት ለቅጽበት በውስጥህ የተደበቀውን አውሬ ያወጣዋል ። የሚገርመው ያ አውሬ ወጥቶ አለመቅረቱ መልሶ መደበቁ ነው ። ለመውጣት የፈለከው መሰላል ለመውረድም ያስፈልግሃልና ከበርሁ ብለህ ሕዝብ አትናቅ ። 

ወዳጄ ሆይ ! 

በረከሰች ከተማ መቀደስ እንደ ሎጥ ፣ በተቀደሰች ገነት መርከስ እንደ አዳም አለና ልብህን መርምር ። አባቶቻችን ሰው ቦታን ፣ ቦታም ሰውን ይቀድሳል ያሉትም እውነት ነው ። እርሱ ነው ከማለት እኔ ነኝ ማለት ማዕበልን ያበርዳል ። የጀመረ ካልጨረሰ አይከብርም ፣ የጨረሰም ካላመሰገነ አይደሰትም ። የአንድ ነገር መጨረሻ የሌላ ነገር መጀመሪያ ነውና ደስ ይበልህ ። ይታዩ ዘንድ ከተማውን የዞሩ ፣ ይደበቁ ዘንድ ዋሻውን ያጣሉ ። በመካከላችን እግዚአብሔር አለና እውነት እንነጋገር ። 

በቸር ዋሉ !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 26 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም