መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » ኤፌሶን ትርጓሜ » ያልተማርነው ክርስቶስ

የትምህርቱ ርዕስ | ያልተማርነው ክርስቶስ

/ማሳሰቢያ፡- ይነበብ/

“እናንተ ግን ክርስቶስን እንደዚህ አልተማራችሁም ፤” ኤፌ. 4 ፡ 20 ።

አዳም በልምድ ፣ በቅብብሎሽ ፣ በትምህርት ፣ በምርምር ፣ በፍልስፍና ፣ በታሪክ ፣ በግኝት ከሚገኘው እውቀት ይልቅ ሰፊ የሆነ ጥበብን ተቀብሎ ነበር ። ጥበብ በኃጢአት ትጎሳቆላለች ። ፈሪሀ እግዚአብሔር ሲጠፋም የሰው እውቀቱ ከእንስሳት እያነሰ ይመጣል ። የትምህርት የመጀመሪያው ክፍል የሰው ልቡና ነው ። ሰው ራሱን በራሱ ፣ ራሱን በክስተት ፣ ራሱን በተፈጥሮ ፣ ራሱን በመንፈሳዊ መብራት የሚያስተምርበት የልቡና ክፍል ከሁሉ የላቀ ነው ። ከዚህ በፊት ሰምቶት ፣ አስቦት የማያውቀውን እውነት ሲሰማ ልክ ነው ይላል ። ልክ ነው ያለበት መመዘኛ ከየት መጣ ካልን በኃጢአት ምክንያት ተዳፍኖ የነበረ የእግዚአብሔር መብራት የሆነ እውቀት በውስጡ ስላለ ነው ። የሚሰማው እውቀት የተዳፈነውን መብራት ፍርድ ይሰጥ ዘንድ ገለል ያደርግለታል ። እውቀት እንደ ነፋስ ነው ፣ ትቢያን ያራግፋል ። እንደ እሳት ሆኖም እርጥቡን ያደርቃል ። ሰው በእውቀት አይለወጥም ፣ እውቀቱ በመንፈሳዊነት ሲታገዝ ግን እየተለወጠ ይመጣል ። በኖረ ቍጥር ፀጉሩ እያረረ ፣ ጥፍሩ እየዘረዘረ/እየጠነከረ ይመጣል ። እንዲሁም በኖረ ቍጥር ጠባዩ እየገነተረ ይመጣልና ዕድሜም አይለውጠውም ። ልቡናን የመጀመሪያው የትምህርት ክፍል ብንለውም ከዚያ በፊት የሚቀድሙ አሉ ። የትምህርት ሁለተኛው ክፍል የእናት እቅፍ ነው ። በእናቱ እቅፍ ውስጥ ሁኖ ፍቅርን ከወተት ጋር እየተመገበ ሕጻኑ ያድጋል ። ፍቅሩ ያለ ወተት ፣ ወተቱም ያለ ፍቅር አይሟሉም ።

ሦስተኛው የትምህርት ክፍል ቤተሰብ ነው ። ቤተሰብ ለሕጻኑ ይህችን ዓለምና ማኅበራዊነትን የምታስተምር የመማሪያ ክፍል ናት ። ጭካኔን ወይም ርኅራኄን ሕጻኑ ይማራል ። ሕጻኑ ግን ከቃል ይልቅ በቤተሰቡ ጠባይ እየተቀረጸ ይመጣል ። ሰው ቤተሰቡን ይመስላል ። እግዚአብሔር በመልኩና በምሳሌው ፈጠረን ፤ ቤተሰብ ደግሞ በመልኩና በምሳሌው ያሳድገናል ። በመልኩ ሲያሳድገን አፍቃሪ ወይም ዘረኛ አድርጎ ይስለናል ። በምሳሌው ሲያስተምረንም በውይይት ወይም በዱላ እንድናሳምን አድርጎ ያዘጋጀናል ። እስክንሞት ድረስ ወላጆቻችንን ተሸክመን የምንዞር ነን ። ከዚህ ከአሮጌው ቤተሰብ የምንለየው ክርስቶስን ሕይወት ስናደርግ ብቻ ነው ።

አራተኛው ትምህርት ቤት ዜማ ነው ። ስብሐተ እግዚአብሔርን ለማድረስ የአምልኮ ጥማተኛ ያደርገናል አሊያም ዘፈን ወዳድ የዝሙት ሎሌ ያደርገናል ። ዜማ በሰው ነፍስ ውስጥ ነውጥ ይፈጥራል ። ሁሉን ስለሚወድ ስለ እግዚአብሔር ፍቅር የምንማረው በዜማ ነው ። ዘፈን ያለበት ዜማ ደግሞ ፍቅር ከተቃራኒ ጾታ ውጭ ለሌላ የማይሰጥ አድርጎ የሚቀርጸን ነው ። በርግጥ ሁሉም ዘፈን የዝሙት ማስታወቂያ አይደለም ። አገርንና ተፈጥሮን የሚያሳይ ዜማ አለ ። ጾታዊ ፍቅር ተገቢ ቢሆንም ጅማሬውና ፍጻሜው ሥጋዊ ፈቃድ ከሆነ ነፍስ የተለየው በድን ነው ። መምህራን ይህችን ዓለምና ሕይወትን የምንማርባቸው አምስተኛ ትምህርት ቤት ናቸው ። ለመምህራን ክብር የማይሰጥ አገር ትውልድን የከሰረ ነው ። ነገ ምን እንደሆነ የምናውቀው ለመምህራን በምናደርገው እንክብካቤ ነው ። መምህራን ሲራቡ ብስጩ ፣ ሲበሳጩ ሱሰኛ ፣ ሱሰኛ ሲሆኑ የተማሪ ጓደኛ ይሆናሉ ። መምህሩን መምሰል ለአንድ ተማሪ የተፈጥሮ ተጽእኖ ነው ። በመንፈሳዊውም ሆነ በሥጋዊ ጎዳና መምህራን ይቀርጹናል ። ሐረገ ትውልድ በቤተሰብ ብቻ ሳይሆን በትምህርት ቤትም አለ ። የአባት ዕዳ ለልጅ እንደሚተርፍ የመምህር ዕዳም ለተማሪ ይተርፋል ።

ስድስተኛው ትምህርት ቤት እንቢ የማንለው ኑሮ ነው ። ትዳር የሚጣፍጠው ትምህርት ቤት መሆኑን አምነው ለገቡበት ነው ። ሰው ራሱን የሚያገኝበት ትምህርት ቤት ነው ። “በሦስት ጉልቻ ይቅጣሽ” የሚል ርግማን በትዳር ተቀጪ ማለት ነው ። “ወልደህ እየው” የሚለው ርግማን ፣ ሲሰማ ቀላል ሲመጣ ግን ከባድ ነው ። ሰባተኛው ትምህርት ቤት ሰዎች ናቸው ፤ ሰዎችም ትልቅ መማሪያዎቻችን ናቸው ። ጎረቤት ተለዋዋጭነትን ማለትም በቀን ሰባት ጊዜ ማበድን ያስተምረናል ከጠዋት እስከ ማታ ወጥ ሰው መሆን መታደል ነው ። የሥራ ባልደረቦች ለእንጀራ መስገድን ፣ ለሚጠፋ መብል መኖርን በግርምት ያስተምሩናል ፤ ሰው ለኑሮው ሕይወትን ለምድር ዘላለምን ይሠዋል ። አለቃ በሌላ አለቃ እየደነበረ የሚኖር መሆኑን ፣ ለአለቃም አለቃ እንዳለው ይነግረናል ። ቀላል ሰዎች ክብርን እንደማይወዱ ፣ ወዳጆችም በስሜት እንጂ በእውነት መውደድ እንደማይችሉ ያስተምሩናል ።

በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ትምህርት ያስተማሩን ቢኖሩም የተማርናቸው ሰዎች ግን ላይኖሩ ይችላሉ ። የተማርናቸው ሰዎች ካሉ እነርሱ ክርስቶስን የሚመስሉ ናቸው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እውነት ነው ። እውቀት እውነት ይፈልጋል ። አሊያ አለማወቅ ነው ። አዳም እግዚአብሔርንና መልካምን የማወቅ እውቀት ነበረው ። ክፉን ግን በትእዛዝ እንጂ በገቢር አያውቃትም ነበር ። እግዚአብሔርም ክፉን በትእዛዝ እንጂ በተግባር አትወቃት ብሎ ሕግ ሰጠው ። አዳም ግን ክፉን በተግባር ሲያውቅ ወደቀ ። ሞትን ሞቶ አወቀ ። ጥይት እንደሚገድል ያወቅነው ቀምሰነው ሳይሆን ተምረነው ፣ በሌሎች ሞት አይተነው ነው ። አዳምም በትእዛዝ ማወቅ ፣ በሰይጣን ውድቀት መገንዘብ ሲገባው ሞትን ሞቼ ልወቅ አለ ። እውነተኛ እውቀት ግን ሕይወትን የሚሰጥ ነው ። ኒውክለርን የሠሩ ሄሮሽማና ናጋሳኪን ሲያስቡ ደስተኛ አይሆኑም ። ስልክ የሠሩ ግን በሰላም በአልጋቸው ይተኛሉ ። የዕለቱንም ዘላቂውንም እንቅልፍ /ሞትን/ በደስታ ያንቀላፋሉ ።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምንማረው እውነት ነው ። እርሱ መንገድ ሁኖ ወደ እውነት ያደርሰናል ። እውነት ደግሞ ነጻ ታወጣናለች ። ነጻነትም ሕይወትን ትሰጠናለች ። መንገድም ፣ እውነትም ፣ ሕይወትም ክርስቶስ ነው ።

ክርስቶስን እንዲህ አልተማርነውም ። ደስ ካለኝ ሁሉም ነገር ትክክል ነው ብለን ክርስቶስን አልተማርነውም ። ደስታ ለእግዚአብሔርና ለሰዎች መኖር ነው ። አላውቅም ፣ አልሰማም ፣ አላይም እያሉ መኖርን ከክርስቶስ አልተማርንም ። መፍትሔ ፈላጊነትን ተምረናል ። ብራብ አብልታችሁኛል የሚለው ረሀብተኛን ማየትን የሚጠቁም ነው ። አላይም ያለ ረሀብተኛን ፣ አልሰማም ያለ እስረኛን አይጎበኝም ። ሽሽትን ከክርስቶስ አልተማርንም ። እርሱ በጓዳ ሳይሆን በአደባባይ መሰቀሉ በር ከፍተን እንድንወጣና መሥዋዕት እንድንሆን የሚያስተምረን ነው ። ላለመውደድና ላለመወደድ ተጠንቅቆ መጓዝን ከክርስቶስ አልተማርንም ። የሚያደነዝዝ የዝሙት ትእይንትን ስናይ ለመዋልና ለማደር አልተጠራንም ። ራሳችንን ለክርስቶስ መስጠትን እንጂ ለሴሰኝነት አሳልፎ መስጠትን ክርስቶስን ከመሰሉ አባቶች አልተማርንም ።

የተማርነውን ክርስቶስን እንኑረው ።

ቸር ክርስቶስ ሆይ አንተን ለሚወድዱ ፀሐይ ይውጣላቸው ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 17 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም