መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ያንተ ፍቅር

የትምህርቱ ርዕስ | ያንተ ፍቅር

  
ወደ ዙፋንህ ለመቅረብ ፣ ወደ ህልውናህ ለመድረስ አልችልም ። ከዙፋንህ መራቅ ፣ ከህልውናህም መሰወር አይሆንልኝም ። ሊቀርቡህ ግርማዊ ፣ ሊርቁህ ሞገሳዊ ነህ ። ማስፈራትን ከውበት ጋር ፣ ፍቅርን ከፍርድ ጋር ፣ ዙፋንን ከበረት ጋር ፣ ሞትን ከሕያውነት ጋር ያስተባበረ እንደ አንተ ማን አለ ! አንተ የእኔ የሆንከው በፍቅር ነው ። እኔ ያንተ የምሆነው በግድ ነው ። አንተ ግን ራስህን ስትሰጠኝ እኔ ርቄሃለሁ ። አስገድደህ ልታሰግደኝ ስትችል በፍቅር ታባብለኛለህ ። እሳቴ እንዳይጠፋ ፍቅሬን አበርታ ። መቅረዜ እንዳይወሰድ መንፈስህን ከማሳዘን ጠብቀኝ ። በሌለህበት ከመገኘት ፣ ባለህበት ከመታጣት ጠብቀኝ ። ጎበዝ ሁሉ ሲቆረጥ ደካማውን እኔን ትከለኝ ። የጠገቡ በሚራቡበት ቀን እኔን ችግረኛውን ዋስ ሁነኝ ። አገሩን የሞሉ አድራሻቸው ሲጠፋ ለእኔ ጥግ ስጠኝ ።
ካንተ ውጭ ማንም የለም ። ካንተ ውስጥም ምንም አይታጣም ። የሚሞቱ ነገሥታትን የምትሾም ሕያው ንጉሥ ፣ የሚሻሩትን የምትቀባ የዘላለም ቅዱስ አንተ ነህ ። እስከ ሞት ብናገለግልህ እስከ በሌለው ዘላለም ታገለግለናለህ ። ከምንሰጥህ የምትሰጠን ይበልጣል ። ሠረገላዎችህ አይነኩም እሳት ናቸው ። ቅጥርህ አይደፈርም ነበልባል ነው ። የቤትህ ግድግዳና ጠፈር በውኃ የታነፀ ነው ። መሠረቱም የደም ነው ። ልዑል ሆይ ማደሪያዎችህን ነፍሴ ወደደቻቸው ። የሃይማኖት መሠረት ፣ የደናግል ንጽሕና ፣ የሰማዕታት ጭከና አንተ ነህ ። ፍቅርህ ከሞት ይልቅ ይበረታል ። እንዲህ ባትወደን አንድንም ነበር ። መርከቤ ሲናወጥ ሥላሴ ሆይ መቅዘፊያውን ያዝልኝ ። ግራና ቀኝ ማዕበል ሲያማታኝ የቃልህ መልሕቅ ያጽናኝ ። ሞት ከፊቴ ቆሞ ሲፎክር ትንሣኤህ ብርታት ይሁነኝ ። ወደቡ ሲርቀኝ የመንፈስህ ተስፋ ይደግፈኝ ። ጭነቱ ሲከብደኝ መስቀልህ ቤዛ ይሁነኝ ። መሐል ባሕር ላይ አቅጣጫ ሲጠፋኝ ብርሃንህና እውነትህ እነርሱ ይምሩኝ ። መሠረቴ ውኃ ፣ ዙሪያዬ ማዕበል ሲሆን የጠራኸኝ ጌታ አጽናኝ ።
አማኑኤል ሆይ በክንፍህ መዘርጋት ይህን ትውልድ አንተ ጋርድ ። ከጣፈጠን ስህተት አውጣን ። የመረረንን እውነት አጣፍጥልን ። ዛሬን ያለፉት ዘመኖች ካሣ አድርግልን ። የቤተ ክርስቲያንን ምርኮ መልስ ፤ የሄዱብንን መልካም ነገሮች ሁሉ እንደገና ገንዘብ አድርግልን ። ከትእዛዝህ አታርቀን ፣ ከመውደድህ አትለየን ። ጣዕም ካለው ዜማ ፣ ምዑዝ ከሆነ ዕጣን ፣ ከሚያውድ የናርዶስ ሽቱ የሚበልጠው ያንተ ፍቅር ነፍሴን ይቆጣጠር ። የማይረዱኝን ፍለጋ ፣ የማያድኑኝን አሰሳ ይብቃኝ ። በዚህ ዓለም ሹሞች ሳይሆን ማመኔን ባንተ አድርግልኝ ። ልቤን ባንተ አሳርፍልኝ ።
ምስጋናህ ከመላእክት ትጋት በላይ ነው ። ከተፈጠሩ ቀን ጀምሮ እስከዚች ቅጽበት ያለ ዕረፍት ፣ ምስጋናህ ዕረፍት ሁኗቸው ያመሰግኑሃል ። ክብርህን መዝለቅ ፣ ታላቅነትህን በዜማ መደምደም አልተቻላቸውም ። የደናግል ንጽሕና ያንተን ቅድስና አይገልጥም ። የሰማዩ ስፋት ለትልቅነትህ ፣ የምድር ጽናት ለብርታትህ መግለጫ አይሆንም ። እኔም ያቀረብሁልህ ምስጋና ምንኛ ትንሽ መባ ነው ። አንተ ሆይ ፣ ጌታው ሆይ አብዝተህ ተቀበለው ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /9
መጋቢት 1 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም