መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ያየኸው ይድናል

የትምህርቱ ርዕስ | ያየኸው ይድናል

የልብን ጩኸት ፣ የነፍስን መቃተት ፣ የመንፈስን አሰሳ የምታስተውል ጌታ ፣ የለም ያሉህን እየሻርህ አንተ ግን በሚያበራ ሕልውና ትኖራለህ ። ከተድላ ርቆ ልቅሶን ለተዛመደው ፣ ከሕያዋን ሸሽቶ ከመቃብር መንደር ለሚኖረው ፣ እኔ ምልምል ዛፍ ነኝ ብሎ በረሃ ላይ ብቻውን ለቆመው አንተ በፍቅር ድምፅ ታነጋግረዋለህ ። ስንጥቅ ልቡንም ገጥመህ ትይዝለታለህ ። የሚያፈሰውን ብሶት ትገድብለታለህ ። ከልቡ የትካዜን ዙፋን ትሽራለህ ፣ ከፊቱ የእንባን ጅረት ታደርቃለህ ። የእጁን ሰንሰለት ቆርጠህ ፣ የጠሉትን ወዳጅ አድርገህ ፣ በተሰደደበት ቤት ሹመህ ፣ የገዛ ነፍሱን ምርኮ አድርገህ ሰጥተህ ታኖረዋለህ ። ዓለም ቤቴ አይደለም ላለው ዓለም ሁነህ ታኖረዋለህ ። ተስፋ ሁነህ ልቡን ታበራለታለህ ። የልቅሶ ዜማን በቅዳሴ ፣ የኀዘን እንጉርጉሮን በቅኔ ፣  ደረት መድቃትን በልብ ሐሤት ትለውጥለታለህ ። የተከደነውን ሳትከፍት ፣ የተጋረደውን ሳትገልጥ ታያለህ ። ለመርዳት እንጂ ለመታዘብ አታይም ። ለማቀፍ እንጂ ለመገፍተር አትጠጋም ። አንተ የልብስ ወዳጅ አይደለህም ፣ አንተ የሰው ወዳጅ ነህ ። አንተ የሽቱ ወዳጅ አይደለህም ፣ አንተ የነፍስ ወዳጅ ነህ ። ያንተ ኅብረት ከመቆም ከመነሣት ፣ ከጤና ከበሽታ ጋር አይደለም ፣ አንተ የምታከብረው ሕይወትን ነው ። ሕይወት በአልጋም  በጎዳናም ያው ሕይወት ናት ። እኔ ግን የቁመና ወዳጅ ነኝና ሲወድቁ የለሁም ። እኔ ግን የጤና ወዳጅ ነኝና ሲያቃስቱ እሸሻለሁ ።
ጌታ ሆይ በነቀፋና በወቀሳ የደነቆረውን በፍቅርህ ዜማ ታነቃዋለህ ። እኔ ላንተ አልሆንም ያለህን ይበልጥ ትወደዋለህ ። ሊርቅህ ምክንያት የሚያቀርበውን ያለ ምክንያት ታፈቅረዋለህ ። እንደ ባሪያው እንኳ በሆንሁ ለሚልህ የልጅነት ቀለበት ታስርለታለህ ። ተርቦ ለመጣው ፍሪዳ አርደህ ትቀበለዋለህ ። የእርያ ጓደኛ የነበረውን የመላእክት ማኅበረተኛ ታደርገዋለህ ። በሰማይ በምድር በደልሁህ ላለህ ፣ በሰማይ በምድር ርስት ትሰጠዋለህ ። በገዛ እልሁ የደከመውን ፣ የገዛ ጉልበቱ የከዳውን ፣ የልጅ ባላጋራ የገጠመውን ፣ ከራሱ የተሰደደውን ያንን ፈሪ ጨለማውን ታነጋለታለህ ። ቅድስናን አልብሰህ ጽልመታዊውን ድሪቶ ትገፍለታለህ ።
የደረቀ መሬትን የምታለመልም ፣ ፍሬ አልባዋን ዛፍ የምትባርክ ፣ ደረቅ ነኝ ያለውን ጃንደረባ በቤትህና በቅጥርህ የማይጠፋ መታሰቢያና ስም የምትሰጥ አንተ ነህ ። አንተን ላለ አንተ አለህ ። እጅግ እንወድህ ዘንድ እርዳን ። በተመረጠች ቀን እንዳንተኛ አንቃን ። ክፉ ሲመለስልንም ደግ መሆንን አስተምረን ። ያየኸው ይድንልሃል ፣ እባክህ እየንና እንዳን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /7
የካቲት 23 ቀን 2012 ዓ.ም
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም