መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ይሉኝታ የእግር ብረት ሲሆን

የትምህርቱ ርዕስ | ይሉኝታ የእግር ብረት ሲሆን

የምንበላው የምንጠጣው ለራሳችን ነው ፣ የምንኖረው ግን ለሰው ነው ። ደስ ያለንን አንናገርም ፣ ደስ ያለንን ልብስ አንለብስም ፣ ሰዎች ደስ የሚላቸውን እንደ አዝማሪ እናዜማለን ፣ ሰዎች ደስ የሚላቸውን እንለብሳለን ። “ሰው አፍ እንዳትገባ” ፣ “ሰው እንዳያይህ” በሚል ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ውስጥ ወድቀናል ። ጸጋ የሚቀበረው ፣ ተሰጥኦ ፈንቅሎ የማይወጣው ፣ አገር የማያድገው እርስ በርስ በመጠባበቅ ስንኖር ነው ። የሰው ምላስ ሰባሪ ነው ፣ በእነ እገሌ አፍ አትግባ እየተባለ ስለሚነገረን ለአገር የሚበቃ ስጦታ ይዘን እቤት ተቀብረን እንቀራለን ። ፍርሃቱ እያየለ ሲመጣም የገዛ ቤተሰባችንን እንኳ ማነጋገር ፣ በጸጋችን መጥቀም አንችልም ። በርግጥም ቀና ያለውን ሰው በብረት ዘነዘና መትተው የሚፈጠፍጡ ሁልጊዜ በንቃት ላይ ናቸው ። ቀና ያለ ፣ ለዛው ያማረ ፣ እውቀቱ እያሸተ ያለ ሰው ስናይ ከመደሰት እንፈራለታለን ። በአገሩ ላይ ጥቂት ሰዎች ብቻ ሲናገሩ አፈ ማር ፣ ሲሠሩ መልአክ ተብለው ለመወደስ ተደራጅተዋል ። ቅስም ለመስበር ፣ ከመስመር ለማስወጣት ፣ ብለን ነበር የሚለው ትንቢታቸው እንዲሰምር አፋፍ ላይ ያለውን ገፍተው መጣል የሚያስደስታቸው ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ ። ነገር ግን ተሰብረን ካልጠበቅነው ማንም ሊሰብረን አይችልም ። ሰዎች መስበር ሥራቸው ሊሆን ይችላል ፣ አለመሰበር ደግሞ የእኛ ድርሻ ነው ። ሞተን ካልጠበቅነው ማንም አይገድለንም ። የአገራችን ሰው ላለመለወጥ ተጠንቅቆ የሚጓዝ ነው ። በዚህ ውስጥ አሸንፎ መውጣት ፣ በሚያልፍ ዕድሜ የማያልፍ ታሪክ መጻፍ ፣ እግዚአብሔር የመከረው ሰው ጠባይ ነው ።

ንጽሕናችንን እንኳ የምንጠብቀው ከሰዎች ጋር ቀጠሮ ካለን ነው ። ደኅና ልብስ የምንለብሰው ሰርግ ሲገጥመን ነው ። ቤታችንን የምናጸዳው እንግዳ የሚመጣ ከሆነ ነው ። የገዛ ጥርሳችንን የምንቦርሸው ደጅ የምንወጣ ከሆነ ብቻ ነው ። ለራሳችን ክብር ፣ ለሕይወታችን ንጽሕና ያስፈልገናል ። በደጅ ስልክክ ብሎ የሚታየው ጉብል ቤቱ የተዝረከረከ ነው ። መሬት ለመርገጥ የሚጸየፈው ጎበዝ እቤቱ መሬት ላይ የሚተኛ ነው ። ይሉኝታ ጉረኛ ፣ የዛሬ መመኪያ ብናጣ በአያት በቅድመ አያት የምንመካ እያደረገን ነው ፤ ግጥም እየተወራወርን በአፍ ጦር መወጋጋት ፣ ሰውን ሰብሮ መግባት እንደ ድል መቍጠር ጠባያችን ከሆነ ሰንብቷል ። የምንማረውም እውቀት አስፈላጊ ስለሆነ ሳይሆን መሃይም ብለን ሌላውን ለመሳደብ ነው ።

ያለ አቅማችን ሰዎችን መጋበዝ ፣ ተበድረን ሰርግ መደገስ ፣ በር አዘግተን የሁሉንም ሒሳብ መክፈል እንፈልጋለን ። ብዙ ትዳር የድግስ ዕቃው ሳይመለስ ጠብ የሚጀምረው ለይሉኝታ ብለው በገቡበት ዕዳ ነው ። በአቅማችን መኖር አልቻልንም ፣ እውነተኛውን ነገር ከማድረግ ለሰው አፍ ብለን የምንከፍለው ይበዛል ። ባለ ትዳሮቹን ከማቋቋም ፣ ለአሞራ አብልተን ፣ አሞራ በሰማይ ሲያይሽ ዋለ ብለን ዘፍነን እንሸኛለን ። በሚሊየን የተደገሰላቸው አዲስ ሙሽሮች የሚገቡት ኪራይ ቤት ውስጥ ነው ። ለቀጣዩ ወር የኑሮ ጭንቅ ውስጥ ይገባሉ ። ከሚለብሰው ተርፎት የሚከናነበው አለው ለመባል ቀሚስ ሳይኖረን ካባ እንደርባለን ። አስበን የምናደርገው ነገር የለም ፣ ሁሉንም ነገር ትእዛዝ እስኪመጣ እንጠብቃለን ። ሠራተኛው አለቃው እስኪመጣ የወሬ ስፌት ይሰፋል ፣ አለቃውን ሲያይ ይሯሯጣል ። የገዛ ሕሊናው የማያዝዘው ሰው ከቆሙት በታች ፣ ከሞቱት በላይ ነው ። ሽማግሌው ቆሻሻ ሲጠርግ ምነው እኛ እያለን የሚለው ብዙ ነው ፣ እኒያን ሽማግሌ የሚያዳክም እንጂ አስቦ የሚያጸዳ የለም ። እግዚአብሔር ለሠራው ምድር ፣ ለፈጠረውም ወንዝ ያስባል ፤ ስናጎሳቁለው ይቀጣናል ። የምንበክለው ተፈጥሮ ዋጋ ያስከፍለናል ።

ከውጭ አገር በሚላክ ገንዘብ ሰው ሲጋብዙ የሚውሉ ፣ “እርስዋን ያቆይልን” እያሉ የሚያስመርቁ ፣ ለዚያች ልፋተኛ ግን መሬት እንግዛላት የማይሉ ብዙ ጨካኞች አሉ ። ልጆቹን እያስራበ ሲገባበዝ የሚውል ፣ አባ መስጠት ተብሎ ለመጠራት የማይጠቅም መጠጥ የሚራጭ ብዙ ነው ። ይሉኝታ ውዳሴ ከንቱ ምግቡ ነው ። በእውነቱ ስናየው ሥራ ማጣት እንዳለ ሆኖ ሥራ ቢገኝስ የሚሠራ አለ ወይ ( ብለን መጠየቅ ያስፈልጋል ። ቧንቧ ሠራተኛው ቀጥራችሁት የሚመጣው በወሩ ነው ። ሥራ ጠፍቷል ወይስ ሥራን ገፍተናል ( ብለንም መጠየቅ ያሻናል ። የምሠራውንም በመሰልቸት ስለምንሠራው የተሠራለት ሰው ሲረግመን ይኖራል ። ከሰው ጉቦ ተቀብሎ ወይም ቀምቶ ማታ ላይ ሰው ሲጋብዝ የሚውል አለ ። እንዴት ሰው ፣ ሰውን አስለቅሶ ሰውን ለማስደሰት ይሞክራል ( ይሉኝታ ፣ የይሉኝታ ኑሮ የማትሞት የማትድን አገር ይፈጥራል ። አምነንበት የምናደርገው በጎነት ፣ አምነንበት የምንተወዉ ክፋት ከሌለ እውነተኛ ሰዎች አይደለንም ።

ለሚለምነው መስጠት መልካም ነው ። ለሚሠራው ማበረታታት ተገቢ መሆኑን ማመን አልቻልንም ። ለጉራ ወፍራም ቲፕ ስንሰጥ የታክሲ ረዳትን ተከራክረን ድቃቂ ሳንቲም መቀበል ግን እንደ ድል እንቆጥረዋለን ። የሚለምነው እንደሚያሳዝነን የሚሠራው ሰው ሊያስደስተን ፣ በርታ ልንለው ይገባል ።

ይሉኝታ እውነታ አይደለም ። በይሉኝታ የጋበዘ ሰው ሲጸጸት ይውላል ። ይሉኝታ ሰውን ለማትረፍ እግዚአብሔርንና ራስን ማጣት ነው ። ሰዎችን የምንረዳቸው ስለራራን ነው ወይስ ለይሉኝታ ብለን ነው ( ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ። ሰዎች መልካም እንዲሉን የምናደርገው ደግነት በእግዚአብሔር ዘንድ የመጠሪያ ስሙ “ግብዝ” የሚል ነው ። ለወንበራችን ፣ ለስማችን ፣ ለታሪካችን የምንኖር ነገር ግን ለዛሬው ሰው የማንጠቅም መሆን አለመታደል ነው ። ዛሬ ላለው ሰው ምን ይጠቅመዋል ( ለትውልድስ ምን ይተርፋል ( ብሎ ሥራን መሥራት ተገቢ ነው ። የጠገቡትን ከማጥገብ የተራቡትን ማጥገብ ትርጉም ያለው ፣ ሕሊናንም እግዚአብሔርንም ማትረፊያ ነው ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 14 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም