መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደህና ነው /2/

የትምህርቱ ርዕስ | ደህና ነው /2/

የሱነም ከተማ በተራራ ላይ ከተቆረቆሩ ከተሞች አንዷ ናት ። በቀርሜሎስ የመሸገው ነቢይ ኤልሳዕ በእግር ከዳር እስከ ዳር ያቋርጣታል ። የታመመን በነጻ ይፈውሳል ፣ ያዘነን ያለ ዋጋ ያጽናናል ፣ የበደለን ያለ ምንዳ ስርየትን ይነግረዋል ። ድነሃል ፣ በችግርህ ላይ እግዚአብሔር ትልቅ ነው ፣ ኃጢአትህ ተሰርዮልሃል የሚል ድምፅ በእውነት ውድ ነው ። የእግዚአብሔር ጸጋ የማይከፈልበት ዋጋ ሊገዛው ስለማይችል ነው ። ሕዝቡ ግን ከሚፈውሱት የሚያቆስሉትን ፣ ከሚያጽናኑት በችግሩ የሚያላግጡትን ፣ የኃጢአቱን ስርየት ከሚነግሩት በንስሐው እያስፈራሩ የሚኖሩትን ነቢያተ ሐሰት መርጧል ። የሚያበሉትን ሳይሆን የሚበሉትን ፣ ለእግዚአብሔር ክብር ሳይሆን ለራሳቸው ሰርግ የሚያሰናዱትን ቢጽ ሐሳውያን ያፈቅራል ። ኤልሳዕ በእግዚአብሔር ያረፈ ፣ ለቁራሽ የማይሰግድ በመሆኑ ስውር ዓላማ እንዳለው ሰው ይታይ ነበር ። የሰው ልጅ ጸጋን ትቶ ክፍያን ፣ ቸርነትን ጠልቶ ምንዳን ያከብራል ። ያቺ የሱነም መንደር የሚያልፈውን ነቢይ ጎራ በል ልትለው ያልደፈረች ፣ ሺህዎች ለአንዱ ነቢይ ያላሰቡባት ከተማ ነበረች ። የማያልፈውን ለሚሰጠው የሚያልፈውን ቁራሽ ልስጥህ ያለው ማንም አልነበረም ። ኤልሳዕን ላለማየት በተከናነበችው በሱነም ከተማ አንድ አስገራሚ ክስተት ተፈጸመ ።

ለማኝም ይሰጠዋል ፣ ይለምናልና ወይም ያሳዝናልና ። የእግዚአብሔር እንደራሴ የሆነው ነቢይ ግን አይለምንም ፣ ሕዝቡ እጅ ላይ የእግዚአብሔር ድርሻ አለና የመብቱን ይቀበላል ። ለእግዚአብሔር አገልጋዮች የቱንም ያህል ብናደርግ ምስጋና እንኳ መጠበቅ የለብንም ። ምክንያቱም ስጦታችን ግዴታችን እንጂ ቸርነታችን አይደለምና ። እግዚአብሔር ዋጋ የሚከፍለን በቸርነታችን ሳይሆን የአምላክን ቸርነት ለሰዎች በመግለጣችንና አደራችንን በመወጣታችን ነው ። የአገራችን ሰው ይቅር በለኝ ብለው እግሩ ላይ ሲወድቁ የሚያቀናቸው እንዲህ እያለ ነው፡- “ይቅር የሚል እግዚአብሔር ነው ፣ ሁላችንን እግዚአብሔር ይቅር ይበለን” ይላል ። እንዲሁም ሰዎች ስለሰጠናቸው ስጦታ ጎንበስ ብለው ሲያመሰግኑን፡- “የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው ፣ እኔ አቀባባይ ነኝ ፤ እኔም ከእርሱ ተቀብዬ ነው የምሰጠው” ማለት ይገባናል ። ስጦታ አምልኮ የሚሆነው እግዚአብሔርን ስናከብርበት ነው ።

ሱነም ውሎ ቀርሜሎስ ጫካ ያድራል ። ያ የእግዚአብሔር ነቢይ ለሰማይ ወፎች መሳፈሪያ ፣ ለምድር ቀበሮዎች ጉድጓድ አላቸው ፣ እኔ ግን ራሴን የማስጠጋበት የለኝም እስኪል የእግዚአብሔር ድሀ ሁኖ ነበር ። የሰው አነጋጋሪ ቢያጣ ከዱር አራዊት ጋር ያወራል ፣ ጉባዔ ቢታጠፍበት ከሰማይ ወፎች ጋር ያወጋል ፣ ሰዎች ርቀውት ዛፎች እንደ ሠራዊት ከበውታል ። መንፈስ ቅዱስ ብቸኝነትን ፣ ተፈጥሮ ፀጥታን ይዋጉለታል ። መንፈስ ቅዱስ በምድረ በዳው ዓለም ላይ ከለማ ከተማ በላይ ድፍረት ይሰጣል ። ብቸኝነት ያለ ሰው መሆን ሳይሆን ያለ መንፈስ ቅዱስ መሆን ነው ። ከእኛ ርቀው የሚኖሩ አባቶች ከእግዚአብሔር አልራቁም ። ተፈጥሮ ምላሽ ሳይጠብቅ ስለ እግዚአብሔር ፈጣሪነት ይናገራል ።

የእግዚአብሔር ሰዎች ተፈጥሮን የሚንከባከቡት እንደ ዘመዳቸው አድርገው ስለሚመለከቱት ነው ። ተፈጥሮ አድልኦ የሌለው ቸርነት አለው ። አበባ ለእገሌ ውበቷን ሰጥታ ለእገሌ አትደብቅም ። በሰው እኩልነት የሚያምን ተፈጥሮ ነው ። የእግዚአብሔር ልግስና በሰው ሲታነቅ ተፈጥሮ ግን ያለ መቆጠብ ይሰጣል ። ተፈጥሮን ማድነቅ የማይችል እግዚአብሔርን በቅጡ አላወቀውም ። የሠርክን ውበት ማየት የማይችል የተዘጋ ልብ ያለው ነው ። የእግዚአብሔር ሰዎች ከተፈጥሮ ጋር ስለሚዛመዱ አነጋጋሪ አይቸገሩም ። የምንወደው ሰው የሠራውን ሥዕል ባይገባንም እናደንቃለን ፣ ሙዚቃውንም እናዳምጣለን ። እግዚአብሔር የወጠረው ሸራ ሰማይ ይባላል ። ይህን የሚያህል ሸራ የወጠረ ሠዓሊ የለም ። በዚህ ሰማይ ላይ የማይጠገብ ውበት አርፏል ። የወፎች ዝማሬም የጆሮ ምታችንን አያውክም ። እግዚአብሔርን ስንወድ የፈጠረውን እንንከባከባለን ።

በነቢዩ፡- “እግዚአብሔር ለክብሩ የተከላቸው የጽድቅ ዛፎች እንዲባሉ ለጽዮን አልቃሾች አደርግላቸው ዘንድ ፥ በአመድ ፋንታ አክሊልን ፥ በልቅሶም ፋንታ የደስታን ዘይት ፥ በኀዘንም መንፈስ ፋንታ የምስጋናን መጐናጸፊያ እሰጣቸው ዘንድ ልኮኛል” ይላል ። /ኢሳ. 61፡3 ።/ ተክል ፣ ዛፍ ፣ ዘይት ፣ ቅጠል እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔር ማስተማሪያዎች ናቸው ። ተክል ሲተከል ቦታ ይይዛል ፣ እስራኤልም በምድረ ከነዓን ተተክላለች ። የተተከለ ከሌላ ቦታ የመጣ ነው ፣ እስራኤልም ከግብጽ መጥታለች ፤ የተተከለ ፍሬ ይጠበቅበታል ፣ እስራኤልም መልካም ማድረግ አለባት ። ተፈጥሮን መጉዳት የእግዚአብሔርን የማስተማሪያ ዕቃዎች መጉዳት ነው ። እውቀታችንም እያነሰ ይመጣል ።

ነቢዩ ኤልሳዕ ሁሉ በደጅ እጅ ይነሣዋል ። በቤቱ ግን የሚቀበለው ማንም አልነበረም ። የእግዚአብሔር አገልጋይ እንደሚበላ ፣ ማረፊያ እንደሚያስፈልገው ያወቀች ያች ሴት ብቻ ነበረች ። አሥር ቢወለድ የሚጠቅም አንድ ነው ። ከሺህ ሕዝብ መካከልም አንድ አስተዋይ ይገኛል ። የእግዚአብሔር አገልጋይ ለችግር ቀን የሚፈለግ ለግብዣ ቀን የሚረሳ ነው ። እንደ ቀብር አስፈጻሚ ፣ እንደ ዕድር ጡሩንባ ነፊ ፣ እንደ እሳት አደጋ ሠራተኛ ፣ እንደ አልቃሽ ሙሾ አውራጅ ፣ እንደ ሐኪም በችግር ቀን ውል የሚል ችግሩ ሲያልፍ ከልብ የሚረሳ ነው ። ሰው የችግር ቀን ወዳጁን በደግ ቀን ቢጠራ ችግር በዓለም ላይ አይደጋገምም ነበር ።

በሰራፕታ ብዙ መበለቶች ነበሩ ። ኤልያስን መጀመሪያ ልቧን ቀጥሎ ቤቷን ከፍታ የተቀበለች ግን አንዲት ባልቴት ናት ። በሱነምም ብዙ ሴቶች ነበሩ ። ኤልሳዕን የተቀበለች ግን አንዲት ሴት ናት ። /ሉቃ. 4 ፡ 25-26 ።/ ኤልሳዕ ሳይነግራት ችግሩን ያወቀችለት ፣ ሳያሳስባት ያሰበችለት ፣ የሚበላ አፍ ፣ የሚያርፍ አካል እንዳለው የተገነዘበች አንዲት ትልቅ ሴት ናት ። ይህች ሴት ለአንድ ቀን ለጉራ አልጋበዘችውም ። ሸክሜ ነው ብላ ኃላፊነት ወሰደች ። ፈሪሳዊው ስምዖን ጌታን በር ከፍቶ ልቡን ዘግቶ ተቀበለ ። ይህች ሴት ግን ልቧን ስለከፈተች በሯንም ከፈተች ። ልብ ዘግቶ በር መክፈት ይቻላል ። ልብ ሲከፈት ደግሞ የማይከፈት ደጃፍ የለም ። /ሉቃ. 7 ፡ 36-50 ።/

ይህች ሴት የሀብት ጥያቄዋ ቢመለስም የልጅ ጥያቄዋ ያልተመለሰላት ሴት ናት ። ደስታ ማለት የሁሉም ጥያቄዎች መልስ መገኘት አይደለም ፤  ከጥያቄ በላይ የሆነውን አሸናፊ ጌታ ማየት ነው ። ባልተገኘው ነገር የተገኘውን ነገር ደምስሳ የምታይ ሴት አልነበረችም ። ባላት መደሰትን የመረጠች ፣  ደስታ አጥታ ባሏን ደስታ የምትነሣ ፣ እንደ ሣራ ከእገሌ ውለድ ብላ ወደ ዝሙት የምትመራ አልነበረችም ። “የወለዱ እንጀራ የላቸውም ፣ እኔ እንጀራ ቢኖረኝም ልጅ የለኝም ፤ ሁሉም ቤት ጉድለት አለ ፣ ቢሆንም ደህና ነው” ብላ ታስብ ነበር ።

ያለንን ማየት አቅቶን በሚኖረን ነገር ላይ ደስታችንን ያስቀመጥን ፣ ለደስታ ቀጠሮ የሰጠን ሰዎች ባለን እንደሰት ። እኛ ያለንን ሌሎች የላቸውም ። እግዚአብሔር ያየውን አይቶ በከለከለን ነገር ደስ ይበለን ። ሁኔታዎች በመለወጣቸው ሳይሆን እኛ በመለወጣችን ደስ ይበለን ። ያልተፈጸመ ፣ ያልተሟላ ነገር ፣ ይህ ቢሆን የምንለው ጉዳይ ቢኖረንም ደህና ነው ። ደህና ነው ማለት እግዚአብሔር ትክክል ነው ማለት ነው ። እግዚአብሔር ከአሳቡ ለሚስማሙ በረከት አዝሎ የሚጠብቅ ብሩህ ደመና ነው ። ደህና ነው ።

ይቀጥላል

ደህና ነው /2
ሰኔ 16 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም