መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደህና ነው /3

የትምህርቱ ርዕስ | ደህና ነው /3

ብዙ ሰው እግዚአብሔር ወደ ቤቴ ቢመጣ እቀበለዋለሁ ብሎ ያስባል ። እግዚአብሔር ግን በፍቅሩ ወደ ልቡ ፣ በአገልጋዮቹ ወደ ቤቱ ሲመጣ እየገፋ የሚኖር ነው ። በአገልጋዮቹ በኩል የልባችንና የቤታችንን ደጃፍ ሲፀፋ የከፈተ የለም ። አንዳንዱ ሃምሳ ዓመት ፣ ሌላውም ሃያ ዓመት እግዚአብሔርን በደጁ አቁሞታል ። ግን እግዚአብሔር መጥቶ እግዚአብሔርን ይጠብቃል ። እግዚአብሔር በክብሩ ቢመጣ እንኳን የእኛ ቤት የሰሎሞን መቅደስም አይችለውም ፣ እንኳን የሰሎሞን መቅደስ ሰማየ ሰማያትም አይችሉትም /1ነገሥ. 8 ፡ 27/ ። እግዚአብሔር ግርማዊ ሁኖ ሳይሆን በግፍ ባዘነ ሰው አምሳያ ይመጣል ። በእውነት ዳኛው ክርስቶስ ከፍትሕ ፈላጊው ጋር መጥቶ ፈርዶበታል ። ሐኪሙ ክርስቶስ እያቃሰተ በቸልታ አልፎታል ። እግዚአብሔር ወርቀ ዘቦ ግምጃ በሚነጠፍላቸው ሳይሆን የክረምቱ ብርድ ፣ የሌሊቱ ቁር በሚያሰቃያቸው ሰዎች መልክ ይመጣል ። ያቺ የሱነም ሴት እግዚአብሔር ከአገልጋዮቹ ጋር እንዳለ ፣ በሰማይ እንዲቀበላት እርስዋም በምድር ልትቀበለው እንዲገባት ተረድታለች ። ነቢይን መቀበል የነቢይን ዋጋ ማግኘት እንደሆነ አውቃለች ።

አንድ ቤት በአንድ ባለሙያ ብቻ አይሠራም ። ንድፍ ነዳፊ ፣ ቀያሽ ፣ ቆፋሪ ፣ ግንበኛ ፣ አናጢ ፣ ለሳኝ ፣ ቀለም ቀቢ ፣ የመብራትና የውኃ መስመር ዘርጊ ፣ የጽዳት ሠራተኛ ፣ የእንጨትና የብረት ባለሙያ ፣ የዕቃ ተሸካሚ … ትብብር አንድን ቤት ፣ ቤት ያሰኙታል ። የእግዚአብሔር ቤትም በአንድ አገልጋይ ምኞትና ጥረት ብቻ አይገነባም ። በሁሉም ትብብር የእግዚአብሔር ቤት ይታነጻል ።

ያቺ የሱነም ሴት ልቧ ባላጋራ ሁኖባት በልቧ አደባባይ ከሰሳት ። ልቧም ዳኛ ሁኖ ፈረደባት ። ልቧን ተጋፍታ ከልቧ ጋር መኖር እንደማትችል ገባት ። ያልተሠሩ ሥራዎች ፣ ያልተከወኑ በጎ አድራጎቶች ሁሉንም የሕይወት ክፍል ይዋጋሉ ። ስለዚህ ለእግዚአብሔር ሰው በቋሚነት የሚያርፍበት ቤት ለመሥራት ፣ ሙሉ ዕቃ ለማስገባት ወሰነች ። በዘመኑ ሁሉ ቀለብ ልትሰፍርለት በልቧ ቃል ገባች ። የእግዚአብሔር አገልጋይ የሆነው ነቢይ ኤልሳዕ ደወል ሳይደወል የሚነቃ ፣ የሰዓት ፊርማ ሳይኖር የሚሠማራ ፣ የተከለለ ቦታ ሳይኖር መላውን አገር የሚያገለግል ነው ። ወደ ሥራ ለመሄድ አንዳንድ ሰው ደወል ያነቃዋል ፣ ሌላውንም ቤተሰቡ ይቀሰቅሰዋል ። አንዳንዱን የአለቃው ቍጣ ፣ የሰዓት ፊርማ ፣ ቀሪውን ቅጣት ያነቃዋል ። የእግዚአብሔር አገልጋዮች ግን የእርሱ ፍቅር ብቻ ያነቃቸዋል ። ይህች የሱነም ሴት ሰገነቷ ላይ ቆማ የእግዚአብሔርን ሰው ስትጠብቅ የዛሬ ሥራዋ አልተከናወነም ። ልብ በአሳብ ከተያዘ ሥራ መሥራት አይቻልም ። ለውጤታማ ሥራ ልብ መፈታት አለበት ። ሲመጣ እንዴት ወደ ቤቴ ግባ እለዋለሁ ብላ ናፍቆት ፣ ጉጉት ፣ ፍቅር ወጥሮ ይዟታል ። ርስትን እንደ ልጇ ልትሰጠው ፣ ቤት ሠርታ ልታሳርፈው ፣ ቀለብ ሠርታ ልትንከባከበው ወስናለች ። ይህን ውሳኔዋን የምታሳውቀው ዛሬ ነው ። ይህች ቀን እንዳለፉት ዘመናት በከንቱ አታልፍም ። የእግዚአብሔርን ቤት ለሚሠራው ቤት ልትሠራለት ቆርጣለች ።

ይህች የሱነም ሴት የአሳብ ልዕልናዋ የተደነቀላት ሴት ነች ። ሁሉም ዝም ብሎ እኔ ምን አገባኝ  የአገር ዕዳን ብቻዬን እንዴት እሸከማለሁ  ብላ ከራስዋ ጋር አልተማከረችም ። ከአመክንዮ እምነት እንደሚበልጥ አውቃለች ። ሌሎችንም ላስተባብር አላለችም ። ማስተባበር ብትጀምር እስከ ዛሬ አሳምና አትጨርስም ነበር ። ዛሬ በደረቁ የሚላጩ ፣ ሳያበሉ አገልጋዮች ላይ የረሀብ ሰይፍ የሚስሉ ፣ እኔ ጠልቻለሁ እናንተም ጥሉ ለማለት የሚተጉ ብዙዎች ናቸው ። ፍጻሜአቸው ግን ያማረ አይደለም ።

የእግዚአብሔር ሰው ኤልሳዕ ነገሮች እንደ ትላንቱ ቢሆኑም እግዚአብሔር ግን አዲስ ነው እያለ በሰማይ ዝማሬ ተመስጧል ። የሚያስደስት ነገር ሳይሆን ራሱ ደስታ ተቆጣጥሮታል ። እርሱ ተኝቶ የሚያስብለት እንዳለ ቢያምንም ዛሬ እንዲህ ይሆናል ብሎ አላሰበም ። ትላንት ቤት ጥሎ የወጣ ስለ እግዚአብሔር ቤት አልባ የሆነ ፣ ባለጠግነትን ትቶ በፈቃዱ ድሀ የሆነ ሰው ነው ። ነገሮች አልሳካ ስላሉት ሳይሆን ስኬትን ሠውቶ እግዚአብሔርን የሚያገለግል ነው ። ይህች ሴት መላውን ሱነምን ወክላ ተቀበለችው ። ሱነማውያን አልወከሏትም ። በእርስዋ ደግነት ግን አገሩም ሲወደስ ፣ ሲሰበክ ይኖራል ። በአንድ ቅዱስ አገር ይከበራል ። በሱነም አንዲት ታላቅ ሴት ነበረች ይላል ። /2ነገሥ. 4፡8 /። ታላቅነት ብዙ መስፈርቶች አሉት ። ይህች ሴት ግን በመንፈሳዊ መመዘኛ ትልቅ ሴት ነበረች ። የመጀመሪያው ትልቅነቷ በዚያ ምስኪን አገልጋይ ውስጥ ትልቁን እግዚአብሔር ማየቷ ነው ። ኤልሳዕ ወደ ቤቷ ደጃፍ ሲቃረብ በጎዳናው ላይ ወጥታ እንጀራ ይበላ ዘንድ ግድ አለችው ። ኤልሳዕ በብዙ ታገላት ፣ የሚጽናኑ ብዙ ሰዎች እየጠበቁኝ ነው ። መቸገራቸውን እንኳ የማያውቁ ሰዎች ከፊት ባለው መንደር አሉ ተይኝ ቢላት እርስዋ ግን እኔን ረግጠህ ሂድ እንጂ በጅ አልልህም አለችው ። ኤልሳዕ የምትናገረው በስሜት ፣ ደግሞም ለዝና ሳይሆን በእምነት መሆኑን አስተዋለ ። እንደ እግዚአብሔር ግብዣም ተቀበለው ። ሰው አልቋል ፣ ክብራችንም ቀርቷል የሚለውን መደምደሚያ እንደገና አሰበው ። ይህች ሴት እንጀራን ብቻ ሳይሆን ተስፋንም ዘርግታ የተቀበለችው ሴት ናት ። ገና ሰው አለ እንዲል ያደረገችው ፣ ሞቶ ከማገልገል የጠበቀችው ሴት ናት ። እግዚአብሔር አንዱን ላንዱ መጽናኛ አድርጎታል ። ይህች ሴት የብዙ ጥያቄዎች መልስ ናት ። ጥያቄ የሚፈጥሩ ሰዎች ባሉበት ዓለም መልስ ሆኖ መዘጋጀት እንዴት ድንቅ ነው ። ሰዎች ስለ እኛ እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ በረከታችን ፣ ተስፋቸውን ሲቀጥሉ ሕይወታችን ይለመልማል ።

ኤልሳዕን ቤት ልሥራልህ ብላ አልጀመረችም ። መጀመሪያ አክብሮቷን ገለጠች ። በአክብሮቷ ሲተማመን እንጀራ አቀረበች ። ይህች ሴት ግን በዚህ የምትረካ ሴት አልነበረችም ። ጥቂት ሰጥታ ብዙ የምታወራ ፣ አደረግሁ ለማለትም የምትቸር አልነበረችም ። ውዳሴ ከንቱ የተገረዘላት ፣ የእስራኤል አምላክ የሰጠኝን የምሰጥ ነኝ ብላ የምታምን ሴት ናት ። እግዚአብሔርን የማይፈራ ሰው ሲሰጥ ያሳቅቃል ። ሣንቲም ሰጥቶ ሰብእናን ይወስዳል ። ስጦታዋ እንደ እግዚአብሔር ወንዝ በቀስታ ፣ በውበት የሚወርድ ነበር ። ሆድ ሞልቶ ሕሊናን ማራቆት እንዳይኖር ትጠነቀቅ ነበር ።

የሱነም ሴት ለኤልሳዕ ያሰበችውን አሳብ መጀመሪያ ከባሏ ጋር መምከር ነበረባት ። በዚህም ትዳሯን ያሳመነች ፣ ባሏን በበጎ ተግባር ያሰለጠነች ናትና ትልቅነቷ የታወቀ ነው ። ባሏ የሚተማመንባት ፣ ምንም ብታደርግ ትክክል ናት ብሎ የሚያምናት ቢሆንም እርሱም ይባረክ ዘንድ አማከረችው ። “ይህ በእኛ ዘንድ ሁልጊዜ የሚያልፈው ቅዱስ የእግዚአብሔር ሰው እንደ ሆነ አውቃለሁ ። ትንሽ ቤት በሰገነቱ ላይ እንሥራ በዚያም አልጋ ጠረጴዛ ወንበርና መቅረዝ እናኑርለት ወደ እኛም ሲመጣ ወደዚያ ይገባል አለችው ።” ይህች ሴት ጠልቃ የማየት አቅም የነበራት ሴት ናት ። ኤልሳዕ ቅዱስ ሰው መሆኑን ደግሞም ርካሽ ዓላማ የሌለው የእግዚአብሔር ሰው መሆኑን ተገንዝባለች ። ትልቅነቷ አርቃ ማየቷ ፣ ትልቅነቷ ለእግዚአብሔር ያደረውን ሰው መለየቷ ነው  ። ይህች ሴት የስጦታ ልቡ አላት ፣ አቅምም አላት ። አቅም ኖሯቸው ልቡ የሌላቸው ብዙዎች ናቸው ። ልቡ እያላቸው አቅም ያጠራቸውም አሉ ። ይህች ሴት ትልቅ ሴት ናትና ሰገነት ላይ ቤት ለመሥራት አሰበች ። ከፍ ያለ ቅዱስ ሰው ነውና ከፍ ያለ ቤት ተመኘች ። ታች ከሆነ በእኛ ድምፅ ይረበሻል ብላ አሰበች ። ቤታችን ብናስገባው በእኛ ላይደሰት ይችላል ፣ ሁከታችን ያውከዋል በማለት አጤነች ። በርግጥም ትልቅ ሰው ነበረች ። ዛሬ አንድ ሰገነት ላይ ትንሽ ቤት ለመግዛት በሚሊየን የሚቆጠር ብር ይፈስሳል ። ይህች ሴት ለእግዚአብሔር ሰው ለኤልሳዕ አሰበችለት ።

ቤት አልባ ብንሆንም ደህና ነው ። ቤት የሌለው ዜጋ ነኝ ማለት አይችልም የሚል ወሬ ቢወራም የማይፈርስ ቤት በሰማይ ይጠብቀናል ። እግዚአብሔርን ብቻ እንደ ተሰጠን ጸጋ ስናገለግል የእኛን ሸክም የሚሸከሙ ሰዎች ይዘጋጃሉ ። በእውነት ካለፈው የተሻለ ነው ። የዛሬም ቀን አዲስ ነው ። አዎ ደህና ነው ። ደህና ነው ስንል ማመስገናችን ነውና ይጨመርልናል ። በትንሹ ስንታመን በብዙ ይሰጠናል ። እኛ ብንተኛም እግዚአብሔር ለአገልጋዮቹ ይነቃል ። አዎ ደህና ነው ።

ይቀጥላል

ደህና ነው /3
ሰኔ 17 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም