መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደህና ነው /4

የትምህርቱ ርዕስ | ደህና ነው /4

ባልና ሚስት ለአንድ አካል የሚሠሩ ሁለት እግሮች ናቸው  ። አንደኛው ሲራመድ አንደኛው የሚጠልፍበት ፣ አንደኛው ሲጽናና ሌላው የሚረበሽበት ፣ አንዱ ሲያድግ ሁለተኛው የሚቀናበት ኅብረት አይደለም ። ባልና ሚስት ለእግዚአብሔር ሥራ አንድ ሲሆኑ ኑሮአቸው መባረክ ይጀምራል ። የሱነም ሴት ባሏ እንዳልሽ የሚላት ፣ ተማምኖባት ቤቱን የለቀቀላት ብትሆንም እርስዋ ግን ባሏን ታማክረው ነበር ። ወስና ሳይሆን አስቀድማ አሳብ ትጠይቀው ነበር ። ትዳርን ረጅም ጉዞ የሚያስኬደው የጋራ ምክክር ሲኖር ነው ። እንዳልሽ ቢልም ማማከር መልካም ነው ። ሕዝባቸውን የማያማክሩ መሪዎች መልካም ሠርተውም ይነቀፋሉ ። መሪ ማለት የአገር ባል ነው ። ልዩነቱ ትዳሩን ሲፈታ “መፋታትን እጠላለሁ” የሚለው የእግዚአብሔር ቃል የማይመለከተው ባል መሆኑ ነው ። ባልና ሚስት በትዳራቸው ወደ ብቃት ሲደርሱ አንዱ ያሰበውን ሌላኛው ያስበዋል ። እንደ መንቶች ስሜታቸው እየተቀራረበ ይመጣል ። የመንቶች በተፈጥሮ ሲሆን የባልና የሚስት ግን በመሞራረድ ፣ ቢያንስ ከሃያ ዓመት በኋላ ነው ። የሱነም ሴት ለኤልሳዕ ቤት ብቻ ሳይሆን የቤቱንም ዕቃ አሟላችለት ።

“ትንሽ ቤት እንሥራለት” አለች ። ይህ የሚያሳየው ትልቅ ስጦታዋንም ትንሽ አድርጋ የምታይ ትልቅ ሴት መሆኗን ነው ። ትልቅ ሰው የሚቀበለውን ትንሽ ትልቅ አድርጎ የሚመለከት ሲሆን እርሱ ለሌላው የሚሰጠውን ትልቅ ደግሞ ትንሽ አድርጎ ይመለከታል ። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አንድ አበባ የሰጣቸውን ሰው ብድግ ብለው እጅ ነሥተው ይቀበሉ ነበር ። የሱነም ሴት ትንሽ ቤት እንሥራለት አለች ። የቤት ትንሽ እንደሌለው የሠራ ሰው ያውቀዋል ። ቤት ማለት ጣራና ግድግዳ ብቻ አይደለም ። በሚታየው ነገር ውስጥ ብዙ የማይታይ ፣ በሚታወቅ ነገር ውስጥ ብዙ ምሥጢር ያለበት ነው ። የሱነም ሴት ለኤልሳዕ የሚያስፈልጉትን የቤት ዕቃዎች እንዲታዘዝ ባልዋን አሳመነች ። አልጋ ለማረፊያ ያስፈልገዋል አለች ። በዚህ ዓለም ላይ ሰው በትክክል የሚጠቀመው ንብረቱ አልጋው ነው ። ወንበሩን ሳይቀመጥበት ሊከርም ይችላል ። አልጋውን ግን ሳይተኛበት አይቀርም ። ጠረጴዛና ወንበር ይገዛለት አለች ። ለመመገቢያ ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ሲያነብ ፣ ሲጽፍ እንዲመቸው ነው ። ይህች ሴት ለሥጋው ብቻ ሳይሆን ለአእምሮውም ታስብ ነበር ። ስጦታ ሥጋን ፣ አእምሮንና መንፈስን ታሳቢ ማድረግ አለበት ። ለሥጋ እንጀራ ፣ ለአእምሮ እውቀት ፣ ለመንፈስ ቃለ እግዚአብሔር ሲኖረው ስጦታ ያማረ ነው ። ለሥጋው ስንሰጠው በርታ ብለን አእምሮውን ማጎልመስ አለብን ። ወይም በስጦታው ልክ ሥራ ፈጥረንለት መስጠት ፣ ለምኜ ሳይሆን ሠርቼ አገኘሁ እንዲል እናደርገዋለን ። የሰጠህ እግዚአብሔር ነው ማለትም መንፈሱን ያረካል ። የሱነም ሴት መቅረዝም እናኑርለት አለች ። እንዳይጨልመው ፣ ሌሊት ለጸሎትና ለንባብ ሲነሣ እንዳይቸገር ነው ። ለቀን እንጀራውን ፣ ለሌሊት መብራቱን አሰበችለት ። እውቀት ያለው እናትነት ነበራት ። ስለዚህም ትልቅ ሴት ተባለች ።

የኤልሳዕ የቤቱ ምርቃት ደረሰ ። ኤልያስን የተከተለው ቤት ጥሎ ነበር ፣ ዛሬ የኤልያስ አምላክ ቤት ሠራለት ። እርሱ የአምላኩን ቤት ሲሠራ አምላኩ የእርሱን ቤት ሠራለት ። የቤቱ ምርቃት ቀን ታላቅ ደስታ የነበረበት ፣ ኤልሳዕም አምላኩን ስለዚህች ሴት ያመሰገነበት ዕለት ነው ። አገልጋዮች የሚያመሰግኑብን ወይ የሚያለቅሱብን እንሆን ይሆን  ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ። አገልጋዮች ያዘኑበት ምእመን መንገዱ እሾህና ጋሬጣ ያለበት ነው ። ሙሴ የሚመራው ሕዝብ አሰናክሎት ከበረሃ የቀረ አገልጋይ ነው ። ኢያሱ ግን ሸክሙን ተቀበለው ። የሱነም ሰዎችም ችላ ያሉትን ነቢይ ፣ ለገዛ ጉዳዩ እንደሚጮህ ሰው የተቆጠረውን ኤልሳዕን ይህች ሴት አሰበችለት ። የእግዚአብሔርን ሥራና የእግዚአብሔርን አገልጋዮች ብዙ ጊዜ የሚያስቡት ሴቶች ናቸው ። የእግዚአብሔር ደጃፍ ክፍት መሆን ለእነርሱ ልዩ ትርጉም አለው ። ማልቀሻቸውም መጽናኛቸውም የእግዚአብሔር ቤት ነው ። ወንዶች እስከ ዘጠና ዓመት መሞሸር የሚፈልጉ ፣ ምድራዊ ደስታን የማይጠግቡ እንደሆነ ብዙ ጊዜ ይታያል ። የቤቱ ምርቃት ቀን የሱነም ሰዎች ተገኝተው ከሆነ የሚሉት ነገር ይገርመናል፡-

ድሮም አንቺ ጸጋሽ ይህ ነው ።
ችግረኛ ዘመዷን ብታደርግለት አይሻም ነበር ?
ምነው ብትነግሪን እኛም እንተባበር ነበር ።
ለመንፈሳዊ ሰው እንዲህ ያለ ቅንጦት ማድረግ ያሰናክለዋል ።
ኤልሳዕ ብዙ ሹማምንትን ያውቃል መች ይቸግረዋል ።

አንዱ ለሰጠ ብዙ ዓይነት ስሜቶች ይንጸባረቃሉ ። መልካም ሥራ ፍሬ መሆኑን ረስተው ጸጋ የሚያደርጉት አሉ ። መልካም መሥራት የእነ እገሌ እንጂ የእኛ አይደለም ብለው የድንጋይ ብርድ ልብስ ለብሰው የተኙ አያሌ ናቸው ። ለራስ ቤተሰብ እንጂ ለሌላው መልካም ማድረግ ተገቢ እንደሆነ የማያስቡ ሞልተዋል ። አራዊትም ለልጆቻቸው ደግ መሆናቸውን እነዚህ ሰዎች አያውቁም ይሆናል ። ደግነት የእኔ ለማይሉት ሰው ሲደረግ ደግነት ይባላል ። ሥራው ሲሠራ የጠፉ ሰዎች ካለቀ በኋላ “ምነው ሳትነግሩን” ይላሉ ። መንፈሰ ጕንድሽ ወይም ስስታም ኪሱ ውስጥ አሥር ጊዜ እየገባ ይግደረደራል ፣ አንድ ጊዜ ግን አይሰጥም ። መንፈሳዊ ሰው ሲራብና ሲጎሳቆል ማየት የሚያስደስታቸው የድህነት ዘበኞች አሉ ። ላለመስጠት ብለው እንኳን የአገልጋይ የለማኝ ገቢ የሚያጠኑና የሚያስጠኑ አሉ ። አንድ ሰው ዬኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ከፍሎ የለማኝ ገቢ ያስጠና ነበር ፣ ጥናቱ ካላቀ በኋላ አትስጡ ይል ነበር ። ይህ ሰው እንዳይሰጥ ስስቱ ፣ እንዳይተው ስብከቱ አስጨንቆት ነው ። የሰጪዎች መስጠት ንፉጎችን ምክንያተ ብዙ ያደርጋቸዋል ። ይህ የሚያሳየው ደጎች ንፉጎችን በተግባር  እንደሚገሥጹ ነው ።

ኤልሳዕ በቤቱ ምርቃት ቀን ደስታው ትልቅ ሆነ ። ለካ አገልግሎታችን ሁሉም የገፋው አይደለም ፤ እንዲህ ያሉ ደጎችንም አፍርቷል ብሎ ተስፋው ከፍ አለ ። የዚህች ሴት ውለታ ከበደው ። አገልጋዩን ግያዝን ጠራውና “ይህችን ሱነማዊት ጥራ አለው ።” የእግዚአብሔር አገልጋዮች ሲደረግላቸው የሚያውቁና የሚያመሰግኑ መሆን አለባቸው ። ውጦ ዝም መሆን ፣ ከዚህኛው የእገሌ ወጥ ይሻላል ብለው እንደ ቀላዋጭ ምስጋና ቢስ መሆን አይገባቸውም ። ዘርፈን እንጥፋ ብለው ሕዝቡን በጭካኔ የሚበዘብዙም መሆን አይገባቸውም ። ምስጋናን ማወቅ አለባቸው ። ይልቁንም ዛሬ እየቀለዱበት እንኳ የሚከተላቸውን ሕዝብ ሊራሩለት ይገባ ነበር ። ዛሬ የሌለበትን በሽታ ሲፈውሱት ከርመው የሚፈወስ እርግጠኛ በሽታ ሲመጣ ጥለውት ጠፉ ። እነ አባ ቁጭ ይበሉ ክፉ ቀንን አይወዱም ፣ ደጉን ቀን እያከፉ ይዘርፋሉ እንጂ ። በሽታን ሁሉ “መንፈስ ነው” የሚሉ ይኸው ዛሬ መንፈሱን ከዓለም ላይ ያስወጡልን ። ለአጉል ፈዋሽ ለንስሐ የሚያበቃ በሽታ ይሻላል ። በሽተኛ ለመፈወስ/ለመዳን ማመን ላያስፈልገው ይችላል ። በወንጌል ላይ በቤተሰብና በአገልጋዩ እምነት የተፈወሱ ብዙ በሽተኞች አሉና ። እምነት የሚያስፈልገው ለነፍስ ፈውስ ነው ። አላመንክም እያሉ በበሽታው ላይ ከሀዲ ነህ የሚሉት ፈዋሽ ነን ባዮች ጸጋችን አይደለም ብለው መድረኩን ቢለቁ ያማረ ነበር ። እነዚህም ዜጎች ናቸውና ቤተ ክርስቲያን አደራጅታ ፋብሪካ ብትከፍትላቸው ከብዙ ጥፋት ትድናለች ። መጋዝ ሲሄድም ሲመለስም እየቆረጠ ነው ። ሲክዱም ሲያምኑም ፣ ሲዋሹም ጌታ ጌታ ሲሉም የሚቆርጡ ሰዎችን ቤተ ክርስቲያን መከላከል አለባት ።

“በጠራትም ጊዜ በፊቱ ቆመች ። እርሱም፦ እነሆ ፥ ይህን ሁሉ አሳብ አሰብሽልኝ አሁንስ ምን ላድርግልሽ ? ለንጉሥ ወይስ ለሠራዊት አለቃ ልንገርልሽን ? በላት አለው እርስዋም፦ እኔ በወገኔ መካከል ተቀምጫለሁ ብላ መለሰች ።”

ኤልሳዕ አሳቧን አደነቀ ። የተግባር መነሻ አሳብ ነውና ። ማድረግ ቢያቅታቸውም ያሰቡልን የተባረኩ ናቸው ። ኤልሳዕ ተቀባይ ብቻ አይደለም የሚሰጠው አለው ። የማይሰጥ ድሀ ፣ የማይቀበል ባለጠጋ የለም ። እንዲሁ የሚሰጥ እንዲሁም የሚቀበል የለም ። ለድሀ ሣንቲም ስንሰጠው እርሱ ደግሞ ደስታ ይሰጠናል ። የእግዚአብሔር አገልጋይ ግን ከዚህ በላይ ነው ። ኤልሳዕ እንኳን የአገሩን የሶሪያን የመከላከያ ሚኒስትር ንዕማንን ማዘዝ የሚችል ነው ። ቤት አልባ ሁኖ አህጉርን ማዘዝ ይቻላል ለካ ! ለሠራዊት አለቃ የሚነግርላት ማንም እንዳይነካት ነው ፣ ለንጉሥ የሚነግርላት ርስት እንዲሰጣት ነው ። ይህች ሴት ግን ከምድር ተቀብላ የሰማዩ እንዳይቀርባት የምታስብ ሴት ናት ። አይሆንም አለች ። በኑሮዋ የረካች ሴት ናትና ። የሠራዊት አለቃ አያስፈልገኝም በዙሪያዬ ያለው ወገኔ ነው ይጠብቀኛል አለች ። በርግጥም ትልቅ ሴት ነበረች ። ሕዝቡን እንደ ጠላት ሳይሆን እንደ ጠባቂ ታየው ነበር ። በርግጥም እንዳመነው ይሆናል ። ርስትም አልሻም አለች ። ያለኝንም በቅጡ ከበላሁት ዕድለኛ ነኝ ማለቷ ነው ። የተረጋጋ ኑሮ የምትኖረው ፣ በረጋ አሳብም የጠራ ምክር የምትፈጽመው በመጠን በመኖሯ ነው ።

ኤልሳዕ ደስታውን መቆጣጠር ስላልቻለ ፣ የሚያደርገው ስለጨነቀው ምን ላድርግልሽ ? ለንጉሥ ወይስ ለሠራዊት አለቃ ልንገርልሽን ? አላት ። እንደዚህ የሚያስደስት ተግባር የፈጸመች ሴት ስሟ ማን እንደሆነ አልተጻፈልንም ። ስም የላትም ፤ ስም ካላቸው በላይ ግን ትሠራለች ። ዛሬም ስሙን ያንጠለጠሉት የማይሠሩትን ስም የለሾች ይሠሩታል ። ስም ብቻ ሆኖ ከመቅረት እግዚአብሔር ይጠብቀን ።

ሁሉም ሰው ይወደኛል ማለት ሞኝነት ፣ ሁሉም ይቀበለኛል ማለት ዓለምን አለማወቅ ነው ። ድካማችን አንድ ሰውም ካተረፈ ትልቅ ነገር ነው ። እንዳሰብነው አገር ባያምን ፣ ሕዝቦች በአንድ ዜማ ለኅብረት ባያዜሙ ደህና ነው ። የቆሮንቶስ ሰዎች በሀብታቸው ሳይባረኩበት የፊልጵስዩስ ሰዎች ከድህነታቸው ቀንሰው እስረኛውን ጳውሎስን በማሰባቸው ተባረኩ ። የጳውሎስ አምላክ እንደ ባለጠግነቱ መጠን በክብር በክርስቶስ ኢየሱስ ሞላባቸው ። ልጅ እንደ ራሱ እንጂ እንደ ወላጁ አይደለም ። እንደ እኛ የሚያስቡ ልጆችን ባንወልድ ፣ እንደ እኛ የሚሮጡ ደቀ መዛሙርትን ባናፈራም ደህና ነው ። ደህና ነው ማለት የሰውን ትቶ የእግዚአብሔርን ማሰብ ነው ። አዎ ደህና ነው ።

ደህና /4
ሰኔ 20 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም