መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደህና ነው /6

የትምህርቱ ርዕስ | ደህና ነው /6

የሌሎችን ጉድለት ስንሞላ እግዚአብሔር የእኛን ጉድለት ይሞላል ። እኛ ጋ ያለው ከእኛ ይልቅ እዚያ ጋ ጥቅም ይሰጣል ። ሌሎች ጋ ያለው በረከትም ለእኛ ጥያቄ መልስ ይሆናል ። እግዚአብሔር አንዱን ላንዱ መልስ እንጂ ጥያቄ አድርጎ አልፈጠረውም ። ያቺ የሱነም ሴት ካላት ነገር ላይ ለኤልሳዕ ቤትን ሠራች ፣ የኤልሳዕ አምላክ ደግሞ የሌላትን ልጅ ሰጣት ። እርስዋ ያደረገችው ገንዘብ የሚገዛውን ነው ። በኤልሳዕ ምክንያት ያገኘችው ደግሞ ገንዘብ የማይገዛውን የልጅ ስጦታ ነው ። ኤልሳዕ ወደ ቤቷ ሲገባ የዘመናት ጸሎቷ መልስ አገኘ ። አገልጋዮች ዕዳ አይደሉም ፣ በረከት ናቸው ። የሱነም ሴት እንጀራ ስትጋብዝ የማንም ውለታ የማያልፍበት እግዚአብሔር ልጅ ሰጣት ። የእግዚአብሔርን አገልጋዮች በመቀበል የምናገኘው በረከት አለ ። ለእግዚአብሐር ሠራዊት መንገድ በመዝጋት ደግሞ እንደ አማሌቅ ለዘላለም መረገም አለ ።

ነቢዩ አልሳዕ ለንጉሥ ነግሮ ርስትን ፣ ለሠራዊት ነግሮ ጥበቃን ሊያሰጣት ቢፈልግም ይህች ሴት ግን በኑሮዋ የረካች በድሀ ወገንዋ የተማመነች ነበረች ። ኤልሳዕም ተጨነቀ ። ወደ አገልጋዩ ወደ ግያዝ ዘወር አለና፡- “እንግዲህ ምን እናድርግላት ? አለ ። ግያዝም፡- ልጅ የላትም ባልዋም ሸምግሎአል ብሎ መለሰ ።” /2ነገሥ. 4፡14 ።/ ይህች ሴት ለኤልሳዕ በሠራቸው ቤት እንኳ ለመግባት ድፍረት አልነበራትም ። ፈርታ በደጅ ቆማ ታናግረዋለች ። ችሮታዋ ፣ ቤት ሠርታ መስጠቷ እንድትዳፈር አላደረጋትም ። ግያዝ በእርስዋና በነቢዩ መካከል ሁኖ ቃል ያስተላልፍ ነበር ። አገልጋዮች  ራእያቸውን የሚያካፍሉት ፣ ደግሞም የሚያግዛቸው አንድ ደቀ መዝሙር ያስፈልጋቸዋል ። እነርሱ ሲርቁ ደግሞ ወንበሩን የሚወርስ ፣ ቃሉን የሚያስተላልፍ ረድእ በግድ ያሻቸዋል ። ግያዝ አገልጋይነቱ ለኤልሳዕ እንደ አጥርም ነው ። ነቢዩን እንዳይጋፉና እንዳይዳፈሩ ይከለክላል ። ነቢዩ በሚፈልጋቸው ምድራዊ ነገርም ግያዝ ይሯሯጣል ። አሁንም ይህች ሴት ልጅ እንደሌላት ለኤልሳዕ ነገረው ። ግያዝ እህ ብሎ ነገር የሚመጠምጥ ሰው ነበር ። ማን ምን እንደሆነ ያውቃል ። ነቢዩ ብዙ ነገሮችን ቢያውቅም የሰውን ገመናና ጉድለት ግን ላያውቅ ይችላል ። በነቢይነቱም በማንነቱም የሰውን ምሥጢር ላያውቅ ይችላል ። ግያዝ ወሬውን አጣርቷል ። መፍትሔ ግን የለውም ። ቢሆን ወረኞች ሁልጊዜ መጥፎ አይደሉም ፣ ለጥንቃቄ ይረዳሉ፤  ከዕይታችንና ከጆሮአችን ለራቁ ነገሮች እንደ መነጽር ፣ እንደ ጆሮ ሁነው ያገለግላሉ ። ወረኞች ሁልጊዜ ምንጫችን መሆን ግን አይችሉም ። ነቢዩ የማያውቀውን የዚያን ቤት ምሥጢር ግያዝ ግን አውቆ ጨርሶ ነበር ። ነቢይነት የሰውን ጓዳ ማወቅ አይደለም ። ለመፍትሔ እግዚአብሔር ችግሩንና መልሱን የሚገልጥበት ጸጋ ነው ። ግያዝ በወሬ አነፍናፊነቱ ችግሩን ያውቃል ፣ ኤልሳዕ ግን መፍትሔውን ያውቃል ። ያች ሴት ቤትን ሠርታ በሰጠች ቀን ነቢዩ ደግሞ ያላሰበችውን ፣ ተስፋ የቆረጠችበትን ፣ እንደ ሙላት የቆጠረችውን ጉድለት ፣ የማኅበረሰቡን ነቀፌታ የተቋቋመችበት ቋጠሮ ፈታላት ። በዚያ ዘመን አስተሳሰብ ባልዋ ልጅ ፍለጋ ወደ ሌላ ሴት አልሄደም ። ልጅን የትዳር በረከት እንጂ መሠረት አላደረጉትም ነበር ። በጊዜው ሊሆን ከአምላክ አልተቆራረጡም ፣ በአቋራጭ መንገድ አልሄዱም ። በዚህም ሰላማቸውንና በረከታቸውን ከማባከን ጠብቀዋል ።

ነቢዩ ከግያዝ ባገኘው መረጃ፡- “በሚመጣው ዓመት በዚህ ወራት ወንድ ልጅ ትታቀፊአለሽ አለ እርስዋም፦ አይደለም ጌታዬ ፥ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ፥ ባሪያህን እንዳትዋሻት እለምንሃለሁ አለች ።” ነቢዩ የእግዚአብሔር አፍ ነውና ልጅ እንደምትወልድ ተናገረ ። እግዚአብሔር ለእርሱ ስላደረገችው መልካምነት በልጅ በረከት ይባርካታል ። ኤልሳዕ ምንም ዕዳ የለበትም ። ቤት ተቀበለ ፣ አምላኩ ደግሞ ልጅ ሰጠ ። ለእግዚአብሔር ሰዎች መስጠት ማትረፍ እንጂ መክሰር አይደለም ። የነቢዩ የኤልያስ መንፈስ በእጥፍ ያረፈበት ሰው ነበር ። ኤልያስ የሰራፕታዋን መበለት ልጅ ከሞት ቢያስነሣም ልጅ እንድታገኝ ግን አልጸለየላትም ። ኤልሳዕ ግን የሱነም ሴት ፣ ልጅ እንድታገኝ ደግሞም ልጇ ከሞት እንዲነሣ ምክንያት ሁኗል ። ይህች ሴት የሰማቸውን ዜና ማመን አቅቷት በደስታ ሰከረች ። ከአእምሮ በላይ ሆነባትና እንዳትዋሸኝ አለች ። ነቢዩን ውሸታም ማለቷ ሳይሆን ታላቅ መደነቋን የገለጠችበት ቃል ነው ።

የሱነም ሴት ልጅ ባይኖራትም ሁሉም ነገር የለኝም ብላ የምታስብ ፣ በአንድ ጉድለት ያላትን ነገር ማየት የምትቸገር ሴት አልነበረችም ። አለመውለዷንም እንደ በጎ አይታ በደስታ የምትኖር ሴት ናት ። የምሥራቹ ሲመጣም በልጅ ነገር እኔ አርፌአለሁ የእግዚአብሔር ሰው በዚህ ነገር አትጨነቅ ማለቷ ነው ። ኤልሳዕን የጠራችበት “የእግዚአብሔር ሰው” የሚል አጠራሯ የሚደንቅ ነው ። ቤት ሠርቼ ብሰጥህም አንተ የእኔ ሎሌ ሳይሆን የእግዚአብሔር ሰው ነህ ። ነገሮችን ከዘመኑና ከባሕሉ አንጻር ሳይሆን ከእግዚአብሔር ቃል የተነሣ የምትተረጉም ነህ ማለቷ ነው ። በትንሽ ገመድ ትልቁን ነቢይ የማሰር ፍላጎት አልነበራትም ። ስጦታ ማስገደጃ ፣ የአሳብ ማስፈጸሚያ ፣ ይሉኝታ ማስያዣ ከሆነ የሚቆጠረው ከጉቦ ነው ። ጉቦ ደግሞ ፍቅር የለሽ ስጦታ በመሆኑ ሰጪውንም ተቀባዩንም የሚያስጠይቅ ነው ።

“ሴቲቱም ፀነሰች፥ በዚያም ወራት በአዲሱ ዓመት ኤልሳዕ እንዳላት ወንድ ልጅ ወለደች።” ። እግዚአብሔር በነቢዩ አፍ ተናግሯልና አይዋሽም ። ልጅ የሀብት ውጤት አይደለም ። ሲሰጠን የምንቀበለው ፣ ከከለከለን አመስግነን የምንቀመጥበት ነው ። የወለደ ሁሉ የተደሰተ ፣ ያልወለደ ሁሉ ያዘነ አይደለም ። ክረምትና ማኅፀን የማያበቅለው የለም እንደሚባለው ይሁዳም ልጅ ነው ። አባቱን የሚገድል ፣ እናቱን የሚዋርድ ፣ ጌታውን የሚሸጥ ልጅም አለና እግዚአብሔር ሲከለክልም ማመስገን ይገባል ።

እግዚአብሔር የረሱትን የጸሎት መልስ አስቦ ይሰጣል ። አንዳንድ ጸሎቶች እንዲፈጸሙ ልናደርጋቸው የሚገቡ ተግባራት አሉ ። ይህች ሴት እግዚአብሔር ጸሎቷን የመለሰው ነቢዩን በማስተናገዷ ነው ። ጸሎት ተግባር ከሌለው አያርግም ። በአዲስ ዓመት አዲስ ስጦታ አገኘች ። ፀንሰው እስኪወልዱ ብዙ የእግዚአብሔር ጥበቃና ከለላ አለ ። ይህች ሴት አለመውለድን ተሻግራ ፣ ፀንሳ እስክትወልድ የእግዚአብሔር ጥበቃ አልተለያትም ።

እግዚአብሔር የረሱትን የጸሎት ዘር ፍሬ አድርጎ ያበላል ። የተቀበሉትን ችግር የሙላቱ አደባባይ ያደርገዋል ። በጌትነቱ ለሚታመኑ የጌትነቱን ሥራ ይሠራል ። እግዚአብሔር አለኝ ለሚሉ አለሁ ብሎ ይገለጣል ። አዎ ያልተመለሱ ጥያቄዎች ቢኖሩም ሕይወት ይቀጥላል ። ስጦታ መጪና ሂያጅ ነው ። ሰጪው እግዚአብሔር ግን ከሞላ የማይጎድል ነው ። ባይኖረንም የመኖር መብት አለን ። ቢኖረንም እንኖራለን ማለት አይደለም ። መኖር በእግዚአብሔር ነውና ደህና ነው ።

ይቀጥላል

ደህና / 6
ሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም