መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደኅና ነው /7

የትምህርቱ ርዕስ | ደኅና ነው /7

ይህ ዓለም ደስታና ኀዘን ጎን ለጎን የሚሄዱበት ዓለም ነው ። ደስታን ኀዘን ይከተለዋል ፣ ኀዘንንም ደስታ ይተካዋል ። ከቶ የማይጨልም በእግዚአብሔር ዘንድ ብቻ ነው ። ቀን እንዳለ ሌሊት አለ ፣ ብርሃን እንዳለም ጨለማ አለ ። ከደስታው ለኀዘን መዘጋጀት ፣ ከኀዘኑም ለደስታው ትምህርት መውሰድ ተገቢ ነው ። ከደስታው ለኀዘን ዘመን ያልተዘጋጀ ይጎዳል ፣ ከጥጋብ ዘመን ለረሀብ ዘመን ማስቀመጥ ዮሴፋዊ ጥበብ ነው ። ከረሀብ ዘመንም ለቀጣዩ ደስታ ትምህርት መቅሰም ተገቢ ነው ። ከፍ ዝቅ ባይል ይህ ዓለም አሰልቺ ይሆን ነበር ። የወጣው ሲወርድ ፣ የወረደው ሲወጣ ሕይወትን ውብ ፣ ርእሱንም ልዩ ልዩ ያደርገዋል ። መካኒቱ ስትወልድ ፣ ብዙ የወለደችው ሲደክማት ይህን ከፍታና ዝቅታ የሚቆጣጠር እግዚአብሔር ነው ። በደስታው በጣም አለመደሰት ኀዘኑን ለመቻል ይረዳል ፤ በኀዘኑም በጣም አለማዘን የደስታው ዘመን ላይ ጨለምተኛ ፣ የትላንት እስረኛ ከመሆን ያድናል ። ይህ ዓለም የልክ ዓለም ነው ። ጠጣር በኪሎ ፣ ፈሳሽ በሊትር ፣ ርቀት በሜትር የሚለካበት ዓለም ነው ። ነገሮችን በልካቸው መያዝ የኑሮ ጤንነት ነው ።

እግዚአብሔር ሰጥቶ የማይነሣ ነው ። ነሥቶም የሚሰጠው የበለጠ ሊያስደንቀን ነው ። አንዱ ነገር ቀድሞ አልነበረንም ፣ አሁን አለን ፣ ቀጥሎ ይጠፋል ። መልሶም ይገኛል ። መጀመሪያ ስናገኝ እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ ነው ብለን አመሰገንን ። ሲወሰድብን ደግሞ የእኛ አለመሆኑን ተረድተን ለበጎ ነው አልን ፣ ሲመለስልን ደግሞ በማስተዋል መያዝ እንዳለብን ተረዳን ። እግዚአብሔር በአንዱ ነገር ሦስት ጊዜ እንደሚያስደስተን እንረዳለን ። መጀመሪያ ቢሆንልኝ እያልን በተስፋ እንደሰታለን ፣ ሁለተኛ ስንቀበል ፣ ሦስተኛ ሲመለስልን ደስ ይለናል ።

ያቺ የሱነም ሴት ልጇ አደገ ። አንድ ቀንም አጫጆች ወዳሉበት እርሻ ሄደ ። ይህ ልጅ አቅም አግኝቶ ወደ እርሻ ከሄደ ዕድሜው ከፍ እንዳለ እንረዳለን ። የእርሻ ቦታ ራቅ ስለሚል ለመጓዝ አቅም ነበረው ፣ አባቱንና እርሻውን ለማየት ከፈለገ ለማፍቀርና የወደፊት ቦታውን ለማየት ውስጣዊ ብርታት አግኝቷል ። ያለ ጠባቂ ብቻውን የመሄድ መብት ካገኘ ለአካለ መጠን ደርሷል ማለት ነው ።

ሁሉም ቀን አንድ ዓይነት አይደለም ። ታላቅ ዕድል የሚገኝበት ፣ ታላቅ አደጋም የሚደርስበት ቀን አለ ። እንዲህ ያለውን ቀን በጸሎት እንጂ በጉልበት ማሸነፍ አይቻልም ። ያ ልጅ ፣ የማታ ወርቅ ሁኖ የተሰጠው ያ ጎበዝ በአባቱ እርሻ ላይ ሳለ በድንገት ራሴን ፣ ራሴን አለ ። እንኳን ሰው እባብ እንኳ የሚሞተው ራሱን ሲመታ ነው ። ራስ ለክፉው እባብ እንኳ ገዳዩ ነው ። ራሴን ፣ ራሴን ብሎ በድንገት ባረቀ ። አባቱም ሎሌውን ጠራና ቶሎ ብለህ ወደ እናቱ ይዘኸው ሂድ አለው ። አባቱ ጋ የሌለ እናቱ ጋ ያለው ነገር ምንድነው  ካልን ፍቅር ነው ። ያ ፍቅር የሞት መድኃኒት እንደሆነ አባቱ አወቀ ። ያ አባት ጥንካሬ አለው ። ስለዚህ ከቤቱ ርቆ ይሠራል ። ያች እናት ፍቅር አላት ፣ በቤት ሁና ልጅን ታሳድጋለች ። እግዚአብሔር አንዱ ሰው ጥንካሬና ፍቅርን እንዲያገኝ ብሎ ልጅን በአባትና በእናት ፍቅር እንዲያድግ አዘዘ ። አንድ ልጅ በእኩልነት አባትና እናቱን አግኝቶ ማደግ አለበት ። አንዱ ሲጎድል ልጅ ባለ አንድ ክንፍ ይሆንና በሕይወት ሸለቆ ላይ መብረር ያቅተዋል ። አባቱን ሲያጣ ፈሪ ፣ እናቱን ሲያጣ ፍቅር የጎደለው ይሆናል ። ፍቅር አግኝቶ ጥንካሬ ካጣ ፈሪ ፣ ስሜቱ ቶሎ የሚጎዳ ስስ ይሆናል ። በትንሽ ፈተናም ይበረግጋል ። ጥንካሬ አግኝቶ ፍቅር ካጣም ለሰው ዋጋ የማይሰጥ ፣ ቁሳዊ ነገርን ብቻ የሚወድ ይሆናል ። ያ አባት ልኩን በትክክል ያውቀው ነበር ። እርሱ ጋ የሌለውንና ሌላው ጋ የሚገኘውን ያወቀ ሰው ብልህ ነው ። የልጇን ጠባይ በደንብ የምታውቀው ፣ የምታክመው እናቱ ነበረች ። ቆይቶ እንደምናየው እናቱ የሞት መድኃኒትም ፍለጋ የገሰገሰች ሴት ናት ። በርግጥምትልቅ ሴት ናት ።

በእግሩ የሄደው ልጅ በሸክም ወደ እናቱ መጣ ። ሰው ሲሄድና ሲመለስ የተለያየ ነው ። ሲሄድ ጤነኛ ሲመለስ ሬሳ ሊሆን ይችላል ። ራሱን ችሎ የሚቆመው ልጅ በወደቀ ጊዜ አህያና ሎሌ አልቻለውም ። አባቱን ሊያይ እርሻውን ሊመለከት ፣ አጨዳውን ሊያደንቅ የመጣው ልጅ እንዳሰበው አልሆነለትም ። የአጨዳው ስፍራ ጦር ሜዳ ሆነበት ። ቆሞ ሳይሆን ወድቆ ተመለሰ ። በቃሬዛ ወደ እናቱ የመጣውን እናቲቱ ግን ሳይከብዳት እስከ ቀትር ድረስ ተሸከመችው ። ሙቀትን መስጠት የሚሞት ልጅን ይመልሳል ። ሕይወትን እየተጋራን የምንኖርበት ዓለም ነው ። እናቲቱ ያ ጎረምሳ አልከበዳትም ። መቻል የአቅም ሳይሆን የልብ ጉዳይ ነው ። ከፈቀድን የሚበልጠንን መሸከም እንችላለን ። ፍቅር ጉልበታም ያደርጋል ።

ሞት ግን የእናትን እቅፍም ፈልቅቆ ይወስዳል ። የእግዚአብሔር መልእክተኛ ነውና የሰው ዘበኛ አይመልሰውም ። የእናት ፍቅርም ከሞት አያድንም ። ከሞት የሚያድን የእግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ነው ። ይህች ሴት የልጇን ሕይወት ተቀምታ በድኑን እንደ ታቀፈች አወቀች ። ከዚህ በፊት የልጅ ሬሳን ማየትን አታውቅም ። የልጅ መጀመሪያዋ የሞትም መጀመሪያዋ ሆነ ። የማታውቀውን ነገር ዛሬ ልታውቀው ስለሆነ ተረጋጋች ። እውቀት መረጋጋትን ይጠይቃል ። አልጮኸችም ፣ አላፈረችም ፣ ወይኔ ልጄ አላለችም ። ሲታመም የላከውን አባቱን ሙቷል ብላ ለመጥራት ፣ ልጄን ምን አደረጋችሁት ብላ ለመክሰስ አሳብ አልነበራትም ። ዕድር ለመጥራት ፣ ዘመድ ለማሰባሰብ ፣ ንፍሮ ለመልቀም ፣ ድንኳን ለማዘርጋት ፣ አልቃሽ ለመጥራት ፣ ከፈን ግዙልኝ ለማለት አልቸኮለችም ። ከእግዚአብሔር ጋር ለመነጋገር ብቻ ፈለገች ።

ሬሳውንም በእግዚአብሔር ሰው ሰገነት ላይ ፣ በአልጋው ላይ አጋደመችው። በሩንም ቆለፈችና ወደ ባልዋ የምጓዝበት አህያ ላክልኝ ወደ እግዚአብሔር ሰው እሄዳለሁ አለችው ። ባልዋም ልጁ እንደተሻለው አስቧልና አልጠየቃትም ። እናቲቱ ጋ መፍትሔ እንዳለ እርግጠኛ ነበር ። ሥራ ፣ ሥራውን የሚል በሚስቱ እምነት የነበረው ባል ነበረ ። ወደ እግዚአብሔር ሰው ወደ ቀርሜሎስ ለምን ትሄጃለሽ  ለምንስ ታስቸግሪዋለሽ  በዓል ወይም የወር መባቻ ቢሆን ምግብም ይዘሽ ትሄጂ ነበር አላት ። ባሏ የተሸፈነለትን ትልቅ መርዶ አላወቀም ። ተጋርዶ የሚኖር ሰው ነበረ ። ሁለት ሰው ከሚጨነቅ እኔ ብጨነቅ ይሻላል የምትል ፣ እንደ እኔ ሌላው ላያምን ይችላል ብላ የምታስብ ሴት ነበረች ። ለባልዋ የልጇን ሞት ብትነግረው ብዙ ነገሮች ይዘባረቃሉ ። ሬሳ አስቀምጣ እንድትሄድም ማንም አይለቃትም ነበር ። እንደ ታመመች ተቆጥራ ትያዝ ነበረ ። ሰዎች የማይሸከሙት ከሆነ መንገር ጥቅም የለውም ። የት ቦታ መናገር እንዳለባት ታውቃለች ። ለባልዋ ጥያቄ ግን መልስዋ አጭር ነው ። “ደኅና ነው” የሚል ነው ። ሬሳ አስቀምጦ ፣ የልጅ ሞትን አይቶ ደኅና ነው ካለች እኛማ ደኅና ነው ለማለት እንዴት አንደፍርም  አላቃሽ ጋ ሳይሆን የሚጸልይልን የእግዚአብሔር ሰው ጋ መገስገስ እንዴት ያለ መታደል ነው !

ኤልሳዕም በሩቅ ባያት ጊዜ ሎሌውን ሂድ ይህች ሴት ምን ሁናለች  ተቀበላት አለው ። አጠገቡ እስክትደርስ አላስቻለውም ። የእግዚአብሔር ሰዎች ሩኅሩኅ ናቸው ። እርስዋ ግን ግያዝን “ደኅና ነው” አለችው ። የት ቦታ ማልቀስ እንዳለባት ታውቃለችና ዝም አለች ። የእግዚአብሔር ሰውን እግር ይዛ ማለቀስ ጀመረች ። ግያዝ ግን ሊያርቃት ፈለገ ። ኤልሳዕም ነፍስዋ አዝናለችና ተዋት አለው ። ሴቲቱም እንዳትዋሸች ብዬህ አልነበረም ወይ  አለችው ። ኤልሳዕም ልጇ እንደ ሞተ አወቀ ። ግያዝንም በትሬን ያዝ ፣ ወገብህን ታጠቅ ፣ በመንገድ ለእግዜር ሰላምታም ቢሆን እንዳትቆም አለው ። ሴቲቱ ግን ፡- ሕያው እግዚአብሔርን አብረኸኝ ካልሄድህ አልተውህም አለችው ። ግያዝም ቀድሞ ሄደ ልጁ እንደ ሞተ አረጋገጠ ፣ በትሩን ቢያሳርፍበትም ምንም ድምፅ አልነበረም ። የእግዚአብሔር ሰው በትሩ እንኳ ሥራ ይሠራል ። ኤልሳዕም ወደ ቤት ገብቶ ከግያዝ ጋር ሆኖ በሩን ዘጋ ። ጸለየ ። በሕፃኑ ላይ ተጋደመበት ፣ ትንፋሽ ሰጠው ። ሕፃኑ ነቃ ። ከሞትም ተነሣ ። ለእናቲቱም ሰጣት ። እርስዋም ሰግዳ እግዚአብሔርን አከበረች ። ሲሞትም ሲነሣም ባሏ እንኳ አያውቅም ነበር ። “ደህና ነው” አለች ፣ ሁሉም ነገር ደኅና ሆነ ። ደኅና ነው ካልን ደኅንነት ይሆናል ።

ተፈጸመ

ደኅና ነው /7
ሰኔ 27 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም