መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ደካማነት

የትምህርቱ ርዕስ | ደካማነት

“ደካማነት እውነት የሌለበትን ሰላም መፈለግ ፣ ቆይ እያለ ለነገ የችግር ፍም ማስቀመጥ ነው ።”

ሁላችንም የራሳችን ችግር ፣ የራሳችን ጉድለት ፣ የራሳችን ደካማ ጎን አለን ። የምንማረው ደካማ ጎናችንን ለማጽደቅ ሳይሆን ለመለወጥ ነው ። በትላንት አድራሻው የሚቀመጥ ድንጋይ እንጂ ሰው አይደለም ። ያ ማለት በየሳምንቱ የአቋም ለውጥ ማድረግ ሳይሆን በየዕለቱ የሕይወት ለውጥ ማድረግ ነው ። በየዕለቱ የምናስወግደው የቆየ ጠባይ አለ ፣ በየዕለቱ የምንሠራው መልካም ነገርም አለ ። የማንነቅልባትና የማንተክልባት ዛሬ አልተሰጠችንም ። ሰው ከራሱ ክፉ ጠባይ ጋር ሲታገል የሚኖር ፍጡር ነው ። በራሱ ላይ ድል ያገኘ አገር ከሚገዛ ይበልጣል ። በርግጥ በአንድ ጊዜ ወደዚህ ጠባይ አልገባንምና በቅጽበት ልንወጣ አንችልም ። እያንዳንዱ ቀን ግን የሚነቀለውን የምንነቅልበት ፣ የሚተከለውን የምንተክልበት ሊሆን ይገባዋል ። ትላንት የሞገተን ነገር ዛሬ ስንደግመው እየላላ ይመጣል ። ትላንት በእኛ ላይ የበላይ የመሰለን ነገር ዛሬ ከእኛ የበታች ይሆናል ። ከመቆም ዳዴ ማለት ፣ ልማድን ከማቀፍ ለመላቀቅ ትግል መጀመር መልካም ነው ። ሰማዕትነት እንደ ዘመኑ ነውና የዛሬው ዘመን ሰማዕትነት ፍላጎትን እንቢ ማለት ነው ።

ብዙ ደካማ ሰዎች በምድር ላይ አሉ ። እንደ እኛ ያለ ደካማ ግን የለም ብለን ማመን አለብን ። እንደ እኛ የሚደክም ፣ እንደ እግዚአብሔር የሚምር ማንም የለም ። ደካማነት ባለቤቱ ሳይቀር የሚጠላው ክፉ ጠባዩ ነው ። ደካማ ጠባያችን ድልን ያዘገይብናል ። ከእርሱ ለመላቀቅ ስንሞክር ከሕይወት ጥሪ እየዘገየን እንመጣለን ። ከምጠላው ከዚህ ማንነቴ አድነኝ እያልን እንጸልያለን ። ምናልባት ከምወደው ከዚህ ማንነቴ ገላግለኝ ማለት የተሻለ ይመስላል ። ደካማ ጠባያችን ካልተወገደ አብሮን የሚዞር ፣ አብሮን የሚኖር ነው ። የምናገኘው ማንኛውም ከፍታ ለደካማነታችን መገለጫ ይሆናል ። ከሥልጣን ከፍታ የሞራል ከፍታ የተሻለ ነው ። ደካማ ጠባያችን ራሳችንን ብቻ እያበሳጨ የሚቀር ሳይሆን ጎረቤትን ሲያልፍም አገርን ሊበክል ይችላል ። ትላንት ሰፈር ይቀራሉ ብለን የናቅናቸው ዛሬ አድማ የሚቀሰቅሱ ፣ የአገርና የቤተ ክርስቲያን ምሰሶ ተደርገው የሚታዩ ሆነዋል ። ሰው ቢጤውን ስለማያጣ ብዙ ደጋፊ አላቸው ። መምህር ኤስድሮስ እንዲህ ብለዋል፡- “ከመሃይም አትጣላ ፣ ደጋፊው ብዙ ነው ያሸንፍሃላ ።” አንድን ሰው ይሳደቡ የነበሩ ዛሬ ዘመን ባመጣው ቴክኖሎጂ ተደግፈው አንድን ሰው ለመላው ዓለም ያሙታል ። ሐሜተኛነታቸውንም ዓለም አቀፍ ያደርጉታል ። በደካማነታቸው የሚያዝኑ አሉ ፣ ይህ እንደ ንስሐ ይቆጠርላቸዋል ። በደካማነታቸው የሚኮሩ አሉ ። እነዚህን ሰዎች ለንስሐ ማቅረብ ከባድ ነው። እኔ አድማ ይሰምርልኛል ፣ የተሳደብኩት ስድብ አይለቅም ብለው የሚኮሩ ሰዎች አሉ ። ሰው ጽድቅን ሲሸሽ በኃጢአት እንደ ጽድቅ ይደሰታል ።

በፍርሃት የምንኖረው ፣ የማያስፈራው የሚያስፈራን ደካማ ስለሆንን ነው ። ለችግሮች መፍትሔ ከማበጀት መለያየትን የምንመርጠው ደካማ ስለሆንን ነው ። ሁሉንም ካልጨበጥሁ ምን እሆናለሁ ብለን የምንስገበገበው ደካማ ስለሆንን ነው ። ሃይማኖታችንን ለድርድር የምናቀርበው ፣ ሚስቴ ባሌ ደስ አላላቸውም እያልን ክርስትናን የካድነው ደካማ ስለሆንን ነው ። ደካማ ሰዎች ፍርሃታቸውን ይንከባከቡታል ። ፍርሃታቸውን እየፈሩት ይመጣሉ ። ፍርሃት የሚያዋራ ነውና የሚላቸውን ይሰሙታል ። ፈሪዎችንም እንደ ጴጥሮስ ይፈራሉ ። በብዙ ስጋት ውስጥ ይገባሉ ። ደካማነት ለፍርሃት አሳልፎ ይሰጣል ። ፈሪ ሰው የሁሉም መጫወቻ ይሆናል ።

ግጭት መልካም ባይሆንም አንዳንድ ጊዜ ወደ እውነተኛ ፍቅርና ሰላም ያደርሳል ። ድፍንፍን ያሉ ነገሮች ውስጣችንን እየበሉት ይመጣሉ ። ደካማነታችን ብንወያይ እንጋጫለን ብሎ ይፈራል ። በመነጋገር ውስጥ ግን የግምታችንን ሐሰተኛነት ፣ የሰዎቹንም የልብ አሳብ እናውቃለን ። መነጋገራችን የሚለያየን ከሆነ አለመነጋገራችን አንድ አያደርገንም ። በልብ ተለያይተን በአካል አንድ ላይ ብንኖር ይህ እውነተኛ አንድነት ሳይሆን ጊዜን ማቃጠል ነው ። በመኮራረፍ ውስጥ ፣ ባለመነጋገር ሰላም ያለ ይመስላል ። አዎ ኃይለ ቃላት ላይኖሩ ይችላሉ ። እየቆየ ሲመጣ ግን ውስጣችን እየታወከ ፣ መኖርን እየጠላን እንመጣለን ። ብንነጋገር ሁለት ነገር እንጂ ሦስት ነገር አይኖርም ። ወይ እኛ ወይ እነርሱ ጥፋተኛ ይሆናሉ ። እግዚአብሔር እንዳያልቅ አድርጎ የይቅርታን ውኃ ሰጥቶናልና በዚያ መንጻት ይቻላል ። ባለመነጋገር ውስጥ ያለውን ሰላም መሳይ ነገር የሚፈልገው ደካማነታችን ነው ። መነጋገር ሊደፈር ፣ አለመነጋገር ሊፈራ ይገባዋል ።

ቶሎ ውሳኔ አለመወሰን የደካማነት አንዱ መገለጫ ነው ። ዛሬ ያላስወገድነው ችግር ነገ ላይ ተራራ አህሎ ይመጣል ። ነገ የማንሸከመውን ዛሬ ማባበል ፣ ነገ የማንቀበለውን ዛሬ ላይ እየሳቁ መቀበል ተገቢ አይደለም ። ቶሎ እንዳንወስን የሚያደርገን ስንፍና ነው ። ዳግመኛም እነዚያን ሰዎች ላጣ እችላለሁ የሚል ፍርሃት ነው ። እኔን አልጎዱኝም ብሎ በእኔነት ሒሳብ ማሰብ ቶሎ እንዳንወስን ያደርጋል ። ውሳኔ በራሳችን መጥፎ ጠባይ ላይም ነው ። ሱስና አጉል ባልንጀርነትን ቶሎ መወሰን ያስፈልጋል ። ቶሎ ባለመወሰናችን የምንከፍለውን ዋጋ ቶሎ ብንወስን ኖሮ የማንከፍለው ዋጋ ነው ። በችግኙ ያልነቀልነውን ካደገና ግንድ ከሆነ በኋላ መንቀል ይከብደናል ። ባለበት የሚቆም ነገር የለም ። ክፉም ደጉም ራሱን ያሳድጋል ። ቶሎ መወሰን ግን ችግር በክብሪት እንዲቀር ያደርጋል ። ቶሎ ያልወሰኑት ነገ ላይ ፍም ሆኖ ያቃጥለናል ።

ብዙ ትዳሮችና ኅብረቶች ሰላም በሚመስል ዝምታ ውስጥ አሉ ። ከላይ የማይታይ ቍስል ውስጥ ውስጡን የሚጨርስ ነው ። እነዚህ ወገኖች የሚነቁት ሁሉም ነገር ካለቀ በኋላ ነው ። የላይ ቍስል ቶሎ የመታከም ዕድል አለው ። ማሬና ሆዴ በሚል ቃል የተሸፈነ ቍስል ግን መጨረሻው የማያምር ነው ። ደካማ የሆኑ የትዳር መሪዎች ፣ ደካማ የሆኑ የቤተ ክርስቲያንና የአገር መሪዎች ቶሎ ባለመወሰን ብዙ ዋጋ እንዲከፈል ምክንያት ይሆናሉ ። ደካማ ማለት አቅም የሌለው ሳይሆን አቅሙን በትክክለኛው መንገድና ሰዓት የማይጠቀም ነው ።

አቤቱ እኔም ያንተው ደካማ ነኝ አበርታኝ !

የብርሃን ጠብታ 4

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 29 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም