የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ድፍርስ ስሜት

ጌታችን በቤተ ልሔም ሲወለድ ክስተቶች ታይተዋል ። በ12 ዓመቱም ወደ ቤተ መቅደስ ሲመጣ አንዳንድ ወሬዎች ወጥተዋል ። እስከ ሠላሳ ዓመቱ ግን በጫካ ሳይሆን ችምችም ባለው በናዝሬት የድሆች መንደር ኖሯል ። በናዝሬት የኑሮ ጫና አለ ፣ ሕዝቦችዋ ግን ጠንካሮች ናቸው ። በሽተኛቸውን ሐኪም ዘንድ ለመውሰድ ይቸገሩ ይሆናል ። ዙሪያውን ከብቦ ለማስታመም ፣ ሳይጸየፉ ለማገላበጥ ግን ይቀላቸው ነበር ። የንጽሕና ዕቃዎች ላይኖሩ ይችላሉ ፤ በናዝሬት ግን ሳይጸየፉ ወገንን መርዳት ይታያል ። ድሆች የገንዘብ እንጂ የፍቅር ችግረኞች አይደሉም ። የሚሰጡት ንብረት ላይኖራቸው ይችላል ። ራሳቸውን ሰጥተው የሚያፈቅሩ ናቸው ። ራሱን ሊሰጥ የመጣው መሢሕ ራሳቸውን ለመስጠት በማይሳሱት በድሆች መንደር አደገ ። በድሆች ሰፈር በትንሹ በረከት መደሰት ይዘወተራል ። በትንሽ ችግር ግን አይበገሩም ። ሁልጊዜ ጫጫታ ስላለ እንደ ባለጠጎች ሰፈር ጭው ያለ ፣ ፍርሃት ያጠላበት አይደለም ። ለሰርጋቸው ባንድ አይቀጥሩም ፣ ከሰርጉ ቀን በፊት ለሦስት ወራት ከበሮ ተከራይተው ይጨፍራሉ ። የአንዱ ሰርግና ልቅሶ የሁሉም ነው ። ሚዜ አይከራዩም ፣ የሬሳ ተሸካሚ አይቀጥሩም ።

የድሀ ልጆች ተጠጋግተው ይተኛሉ ፣ እስከ ሞት ድረስም ይዋደዳሉ ። የባለጠጋ ልጆች ግን በየክፍላቸው ቆልፈው ከስልካቸው በቀር ዘመድ የላቸውም ። በድሆች ሰፈር በር አይቆለፍም ። የአንዱ እንግዳ የሁሉ ነውና ዘው ብሎ ገብቶ እንጀራ አጥፎ መውሰድ የተለመደ ነው ። የባለጠጎች ሰፈር የአካባቢ ጥበቃ ፣ የቤት ዘበኛ ፣ የኤሌክትሪክ ሽቦ ፣ አደገኛ አጥር ፣ ካሜራ ፣ ጽኑ በር ፣ የጦር መሣሪያ አለው ። ቅዠቱ ግን ተመን የለውም ። መዋኛ ያለው ቤት ቢሠሩም ዋኝተው አያውቁም ። እስከ ዛሬ ድረስ ገብተው የማያውቁበት ክፍል አላቸው ። ቅቤና ማሩ ለቤቱ ክብር ቢገባም አይበሉትም ። “ታየዋለህ እንጂ አትበላውም” የተባለው ተፈጽሟል ። አብዛኛው ባለጠጋ የንብረቱ ዘበኛ ነው ። የጥንት ሰው ምርቃት የሚመስል እርግማን ነበረው፡- “ቤትህ አይቆሽሽ” ይላል ። ሰው የማይመጣበት ቤት አይቆሽሽም ፣ ግን ቆንጆ መቃብር ነው ። ሰው የሚመጣበት ግን ይቆሽሻል ፣ ሕይወት ያለበት ነው ። “ሰው ከነክፋቱ መልካም ነው” ይባላል ። ከሰው ርቆ ፣ ከቢጤ ጋር ተቧድኖ ቢኖሩት የሚያገፋፋ እንጂ የሚያቀራርብ ነገር የለም ።

ማግኔት የሚስበው ተቃራኒውን ነው ። ሰውም ከእርሱ ከሚያንሰው ጋር ቢኖር መደጋገፍ ይኖራል ። እግዚአብሔር ላንዱ ጤናን ፣ ላንዱ ገንዘብን ፤ ለአንዱ ሙያን ለሌላው አቅምን ሰጥቷል ። ድሆችና ባለጠጎች ተፈላላጊ ናቸውና ተደባልቀው ቢኖሩ ሕይወት ጣዕም ይኖረዋል ። “ድሀ ፒያሳ ምን ይሠራል ? ባሕር ዳር ሄዶ አይኖርም ወይ ?” ብለዋል ያለፉት መሪ ። ከተማይቱን እንደ ቅኝ ገዥዎች የባለጠጋና የሕጋዊ ዘራፊ ለማድረግ ፣ ድሀውን ጎርፍ እንደ ተፋው ደለል ዳር ለማውጣት ብዙ ተሞክሯል ። የሚገርመው የድሀ ልጆች የሆኑት ድሀን መጥላታቸው ነው ። ድሆችና ባለጠጎች ተመጋጋቢ ናቸው ። ባለጠጎች የድሆችን የሆድ ክፍተት ይሞላሉ ፣ ድሆች የባለጠጎችን የደስታ ክፍተት ይሞላሉ ። ጌታችን ከድሀ ተወለደ ። ከድሆች ከተማ ከቤተ ልሔም ልደቱን አደረገ ። ከድሆች መንደር ከናዝሬት አደገ ። ከብርጭቆ ይልቅ በጠራው ውኃ በአባናና በፋርፋ ሳይሆን በድፍርሱ በዮርዳኖስ ተጠመቀ ። ንዕማን በናቀው ወንዝ ጌታችን ተጠመቀ (2ነገሥ. 5 ፡ 12) ።

እርሱ ድፍርሶችን ይወዳል ። ቶሎ የሚደሰቱ ፣ ቶሎ የሚከፉትን ስንጥቅ ልባቸውን ገጥሞ ይዟል ። ጨርሶም በደስታ እንዳይጠፉ ፣ ጨርሶም በኀዘን እንዳይሞቱ ሚዛኑን ይቆጣጠራል ። እርሱ ስሜቱ ቶሎ የሚነካውን ፣ ሆደ ባሻውን ፣ ጀውጃዋውን ጴጥሮስን መርጧል ። ድፍርሶች ሁልጊዜ በተጠንቀቅ የሚኖሩ ናቸው ። መከራን ሦስት ጊዜ ይቀበሉታል ። መጀመሪያ፡- በስጋት ፣ ሁለተኛ፡- በቀጥታ ፣ ሦስተኛ፡- በትዝታ ይጎዱበታል ። ድፍርሶች ስሜታቸው ቶሎ የሚታወቅ ፣ አድብተው መግደል የማያውቁ ፣ አፋቸውና ልባቸው አንድ የሆነ ፣ ቶሎ የሚያለቅሱ ፣ ለወደቀ የሚንሰፈሰፉ ፣ ያላቸውን ሲበትኑ ለነገ የማይሉ ፣ የተጎዳ እየፈለጉ አብረው የሚውሉ ፣ ዙፋን ሲዘረጉላቸው መሬት የሚመርጡ ፣ ዓለም ከንቱ ሥጋም ፈራሽ መሆኑ የገባቸው እንደሆኑ ጌታ ያውቃል ።

ዮርዳኖስ ድፍርሱ እስከ ዛሬ ድረስ ይፈስሳል ። ሆደ ባሾች ዛሬም አሉ ። ሆደ ባሾች ፣ ቶሎ የሚከፉ ፣ ሰው የለኝም የሚሉ ፣ የራሳቸውን ብዙ ስጦታ አሳንሰው የሌላውን ጥቂት ስጦታ አተልቀው የሚያዩ ፣ ከሰው የሰውነትን ግብር ፈልገው ባጡ ቀን የሚያለቅሱ ናቸው ። ክፉዎች ፣ ሁሉ ሰው እንደ እነርሱ ስለሚመስላቸው ፣ ከሰው ቀርቶ ከመልአክም መልካም ነገር አይጠብቁም ። ሰውን ለመጠቀሚያነት ብቻ ይፈልጉታል ። የጠራ ውኃ ናቸው ። ፊታቸው ብርሃን ፣ ጥርሳቸው በረዶ ነው ። ልባቸው ግን የአረም እርሻ ነው ። እግዚአብሔር ጉዳዩ ከስሜተ ስስ ሰዎች ጋር ነው ። ቃል ኪዳኑም የድንጋዩን ልብ ፣ ቶሎ የማይነካውን ከውስጣችሁ አውጥቼ ፣ በጣት ሲነኩት ስርጉድ የሚለውን ፣ በቀላሉ የሚነካውን የሥጋ ልብ እሰጣችኋለሁ የሚል ነው (ሕዝ. 36 ፡ 26) ። ይህ ቃል ኪዳን ነውና በእግዚአብሔር ቤት ገና በስሌት ፣ በሽምቅነት ፣ በሽንገላ ፣ ሌላውን በማደንዘዝ የምንኖር “ጌታ ሆይ ደንዳናውን ልቤን ፣ ስሜት አልባውን በድንነቴን ከእኔ አውጣልኝ” ብለን መጸለይ ይገባናል ። ድፍርስነት ቋሚ ጠባያችን እንዲሆን የማይፈቅደው ፣ ስሜታችንን ተረድቶ ሊያግዘን ከእኛ ጋር ነው !

ጌታችን ከድሀ ሰፈር አደገ ፣ ከድሆች ወንዝ ከድፍርሱ ዮርዳኖስ ተጠመቀ ። በማር በቅቤ ሳይሆን በርካሹ ውኃ ተጠመቁ አለ ። ባለጠጎችና ድሆች በጥምቀት አንድ ይሆናሉ ። በውኃና በዕራቁትነት።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 30 ቀን 2016 ዓ. ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ