የትምህርቱ ርዕስ | ጊዜና ማጣት

“ሰው ከጊዜና ከማጣት ብዙ ይማራል ።”

እግዚአብሔር አስተማሪ ነው ። እግዚአብሔር የሚያስተምረውም በተለያየ መንገድ ነው ። ተማሪው በመረጠው መንገድ ሳይሆን አስተማሪው በመረጠው መንገድ ያስተምራል ። “እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ማን ነው ? በሚመርጠው መንገድ ያስተምረዋል” ይላል ። መዝ. 24 ፡12 ። ለእኛ የመረጠልን ምን ይሆን ? ብለን መጠየቅ መልካም ነው ። ለአንዳንድ ሰው የተመረጠለት ሕመም ሊሆን ይችላል ። አንዳንድ ሰውም የተመረጠለት ስደት ነው ። ለሌላውም የተመረጠለት እስር ቤት ይሆናል ። እግዚአብሔር በመረጠው መንገድ ያስተምራል ። ተግባራዊ የሕይወት ትምህርት የሚገኘው ከእግዚአብሔር ዘንድ ብቻ ነው ። እግዚአብሔር በሕይወት እያሳለፈ የማስተማር ሥልጣን አለው ። እግዚአብሔር የሚያስተምርበት ዓላማ እርሱን እንድናውቀውና ከትዕቢት እስራት እንድንፈታ ነው ። የሰው ልጅ የሌለውን ነገር እንዳለው አድርጎ ማሰቡ ትዕቢት ሲሆን በእርግጥ አለኝ እንዲለው የተፈቀደለትን እግዚአብሔርን አለኝ አለማለቱ ደግሞ አለማመኑ ነው ። እግዚአብሔር የሚያስተምረው ለምስክር ወረቀት ሳይሆን ለሕይወት ለውጥ ነው ። በመስቀል ላይ የተሰቀሉት ሁለት ወንበዴዎችን ስናይ መከራ አንደኛውን እንዲያምን ሲያደርገው ሌላኛውን ደግሞ እንዲክድ አደረገው ። መከራ በራሱ አይለውጥም ። ትሑት ልብ ላላቸው ግን መከራ ሰማይን የሚያዩበት ሽንቁር/ቀዳዳ ነው ።

ራሳችንን የምናውቀው ይመስለናል ፣ ግን አናውቀውም ። ሰዎችን የምናውቃቸው ይመስለናል ፣ ግን አናውቃቸውም ። ዓለሙን የምናውቀው ይመስለናል ፣ ግን አናውቀውም ። እየኖርንበት ያለውን ይህን ቀን የምናውቀው ይመስለናል ፣ ግን አናውቀውም ። ራሳችንን ከፍ አለ ስንል ሲዘቅጥብን እናገኘዋለን ። ሰዎች ገቡ ስንል ሲወጡ እንመለከታለን ። ዓለሙ ተሻሻለ ስንል ወደ ድንጋይ ዘመን ሲጓዝ እናስተውላለን ። ቀኑን በሰላም ጨረስኩት ስንል ምሽት ላይ ጣጣ ይዞ ይመጣብናል ። የዛሬው ስሜታችንም ፣ የሰዎች ተለዋዋጭነትም ፣ የዓለሙ መውረድም ፣ የቀኑ ክፋትም ሁሉም ያልፋሉ ። የማያልፍ አንድ ነገር ቢኖር እግዚአብሔር በዚህ ሁሉ ውስጥ የሚያስቀርልን ትምህርት ነው ። እርዳታ የሚያደርጉልን ሰዎች ስለመስጠታቸው እንጂ ስለ ትምህርታችን አይጨነቁም ። የሚያክሙን ሐኪሞች ስለሕክምናቸው እንጂ ስለ ትምህርታችን አይጨነቁም ። የሚዳኙን ዳኞች ስለ ሕጉ እንጂ ስለትምህርታችን አይጨነቁም ይሆናል ። እግዚአብሔር ግን በደረሰብን ነገር ሁሉ ትምህርቱ እንዳያመልጠን ስለ እኛ ያስባል ። እግዚአብሔር የማይረሳ ትምህርት ፣ በዓለት ላይ የተጻፈ ፊደል የሚቀርጽልን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንድናልፍ በመፍቀድም ነው ። አብርሃም ሁሉን አጥቶ ሁሉን አገኘ ። ሁሉን ለማግኘት ሁሉን ማጣት ያስፈልጋል ። አንድ የአገር መሪ ሲነግሥ የመኖሪያ ቤቱን ፣ ማኅበራዊ እሴቱን … ሁሉን ነገሩን ያጣና ሁሉም የእርሱ ይሆናል ። ሙሴ ከቤተ መንግሥት እየበላ ወደ ድሆች ይውጥ ነበር ። ከባዕድ ሰብስቦ ከዘመድ ጋር ለመብላት ይጨነቅ ነበር ። እግዚአብሔር ግን በልዑልነቱ ሳይሆን በእረኛነቱ ለታላቅ ራእይ አበቃው ። ነቢዩ ዳዊት በብዙ መንከራተት ውስጥ ፣ ነቢዩ ዳንኤል በስደት አገር ፣ ሠለስቱ ደቂቅ በነደ እሳት ፣ ሶስና በረበናት ክስ እግዚአብሔርን ይበልጥ አዩት ።

ከዚህ በፊት የማናውቀውን የእግዚአብሔር ጣት የምናየው ጠመዝማዛ መንገድ ውስጥ በማለፍ ነው ። ራሳችን ብርቱ መስሎ ይሰማን ነበር ። ችግር ሲመጣ ግን ደካማ መሆናችንን አሳወቀን ። እግዚአብሔርን ያሳወቀን ችግር ፣ ቀጥሎ ራሳችንን አሳወቀን ። በሰላም ቀን ካንተ በፊት ያድርገኝ ይሉ የነበሩ ሰዎች ችግር ሲመጣ አላውቀውም ብለው እንደ ጴጥሮስ ሲክዱን ሰዎችን አወቅን ። ስንመነዝረው የማያልቅ የመሰለን ነገር ሲሟጠጥ ገንዘብ ሥር እንደሌለው ተረዳን ። አናታችን ላይ መንበራችሁን ሥሩ ሲሉን የነበሩት ሲያዋርዱን ዓለም ወረተኛ የወረት ቤት መሆኗ ተረዳን ።

ጊዜ ብዙ ያስተምራል ። ጊዜ የተባለውም እግዚአብሔር የሚሰጠው ዘመንና ዕድል ነው ። በጊዜ ውስጥ የእግዚአብሔር ፍርድ ይታያል ። በጊዜ ውስጥ እታች ያለው ሲወጣ ፣ እላይ ያለው ሲወርድ መሐል ላይ ይገናኛል ። በጊዜ ውስጥ ቀዩ ሲጠቁር ፣ ጥቁሩ ሲቀላ ፣ ማሩ ሲመርር ፣ ወተቱ ሲጠቁት ይስተዋላል ። ጊዜ የእግዚአብሔር ባሪያ ነውና ጣል ሲለው ይጥላል ፣ አንሣ ሲለው ያነሣል ። ሰው ግን በዚህ ሁሉ ውስጥ ከመማር ወሬ ያሯሩጣል ። በእነ እገሌ የመሸ ዓለም በእርሱ የሚመሽ አይመስለውም ፣ ወዳጁንና ልጁን ቀብሮ እየተመለሰ እርሱ የሚሞት አይመስለውም ። ዛሬ በሌላው ይስቃል ፣ ነገ በእርሱ እንደሚሳቅበት አይረዳም ። በጊዜ ውስጥ ብርቱ ጉልበታችን ሲደክም ፣ የሰጠ እጃችን ሲነጥፍ ፣ ያማረ መልካችን ሲረግፍ ፣ የከበቡን ሠራዊቶች ሲበተኑ ፣ ያቀፉን እጆች ሲገፈትሩን እናያለን ። ባንኖር ይህን ሁሉ አንማርም ነበርና መኖር ደግ ነው ።

ማጣት የማይለመድ የሰው ልጆች የእሳት ጅራፍ ነው ። ማጣት ቀና ያለውን አንገቱን ይሰብረዋል ። ማጣት የከበረውን ያዋርደዋል ። ማጣት ትላንት በሰጣቸው ሰዎች እንዲሰደብ ያደርገዋል ። ያጣ ሰው ጥበብ ቢናገር አበደ ይባላል ። እውቀት ቢናገር ምነው ዝም ባለ ይባላል ። ሰው የእውነት ሳይሆን የገንዘብ አገልጋይ በሆነበት ዓለም ፣ ያጡት ላይ ድንጋይ መጫን ይቀናዋል ። የመሸው ቀን ይነጋል ፣ የጠፋውም ሀብት ይመጣል ። ወዳጄ ሆይ በሚያልፍ ቀን ውስጥ የማያልፈውን እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ ። “ጊዜ የማይሽረው ቍስል የለም ።

በችግር በመከራ ውስጥ የመትረፉ ነገር ያስፈራው ጸሎተኛ እንዲህ አለ፡-

“አብም ያንተ ስም ነው ፣
ወልድም ያንተ ስም ነው ፣
መንፈስ ቅዱስም ያንተ ስም ነው ፤
ብጠራህ ብጠራህ አቤት አላልህም ምነው ።”

እግዚአብሔር ሦስት ስም ፣ አንድ አምላክነት እንዳለው አወጀ ። ዳግመኛም ዘገየህብኝ ብሎ ጮኸ ። አቤት የሚል ታናሽ ነውና አቤት አላልህም ፣ አንተ ጌታ ነህ ብሎ መሰከረ ።

አዎ በጊዜና በማጣት ውስጥ ያስተማረን እግዚአብሔር ስሙ የተቀደሰ ይሁን ! ያጣ ወዳጃችሁን እስቲ ዛሬ አስቡት ፣ አለሁ በሉት ።

የብርሃን ጠብታ 27

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 25 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም