መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ጎበዞችም ይራባሉ

የትምህርቱ ርዕስ | ጎበዞችም ይራባሉ

 

ጊዜው ራቅ ይላል ። ምናልባት16 ዓመት ሊያልፈው ይችላል ። ትዝ የሚለኝ እንደ ሕልም ነው ። ድምፁ ግን እንደ ነጎድጓድ ዛሬም ይሰማኛል ። ዕድሜው አርባዎቹን እያጋመሰ ያለ ነው ። ከአሜሪካ አገር ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ በሀብቱና በእውቀቱ አገሬን አገለግላለሁ ብሎ መውተርተር ጀምሯል ። ደኅና ቤት ተከራይቶ ፣ ከአሜሪካ አገር ይዞት የመጣውን ምቹና ግዙፍ መኪና ይዞ ይንቀሳቀሳል ። ነገር ግን እንዳሰበው አልሆነለትም ። ያለው ሀብት የሚነሣለት እንጂ የሚጨመርበት አልሆነምና ገንዘቡን ጨረሰ ። እንጥፍጣፊ ላይ ደርሶአል ። ቁመናው ፣ ቁፍጥናው ፣ ጉብዝናው በፊቴ ላይ አለ ። አንድ ቀን ማለዳ ላይ ስልክ ደወለና ልመጣ ነው አለኝ ። እኔም ሳመነታና ሌላ ቀን ስለው እርሱ ግን “እሺ መጣሁ” ብሎ የሚያስበውን ሰምቶ ስልኩን ዘጋው ። እኔም ቁጭ ብዬ እየጠበቅሁት ነው ። በተወሰኑ ደቂቃዎች ውስጥ ደረሰ ። እንደ መጣ ሲያየኝ አለቀሰ ። “እህል ከቀመስኩ ሦስት ቀኔ ነው ፣ መኪናውን የምነዳው ነዳጁ እስኪያልቅ ድረስ ነው ፤ ከዚህ አገር መጣሁ ብዬ ይህን መኪና ይዤ ማንን ልለምን” ሲለኝ ተያይዘን ተላቀስን ። ያን ቀን አብረን ዋልን ። ከዚያ ቀን በኋላ አላየሁትም ፣ ላገኘውም አልቻልኩም ። ከዚያ ቀን ጀምሮ ግን ጥሩ የለበሰም ፣ ከፈረንጅ አገር የመጣም ፣ መኪና የያዘም ሊርበው ይችላል ወደሚል አስተሳሰብ ውስጥ ገባሁ ። ጌታችን ምስጋና ይድረሰውና “እንግዳ ተቀበሉ” ያለው ለዚህ ነው ። እኛ የምናነበውን ወንጌል የሚተረጉሙት እናቶቻችን ናቸው ። 

እንግዳን በር ከፍቶ ፣ ጥርስ አሳይቶ መቀበል ብቻውን በቂ አይደለም ። “ከፍትፍቱ ፊቱ” ማለት ፊት ይቀድማል ፣ ፍትፍት ይከተላል ማለት እንጂ ይቀራል ማለት አይደለም ። ሰው እንግዳን የማይቀበለው ገንዘብ ስለሌለው አይደለም ። ባለጠጎች ትልቁ ፈተናቸው ይህ ነው ። ብዙ ባለጠጎች ሰሐኑ እንጂ እንጀራው የላቸውም ። ቤታቸውን ያስጎበኛሉ እንጂ ቁራሽ አያቀርቡም ። ለወትሮም ቢሆን በበረከት የበለጸገና በስስት የበለጸገ ልዩነት አለው ። ለእንግዳ ምግብና መጠጥ አለማቅረብ እግዚአብሔር አልሰጠኝም ብሎ መካድ ነው ። እኛ ጋ እስኪደርስ የበላውን ምግብና የነበረውን አቅም ጨርሷል ። በባዶ ማጫወት በባዶ መሸኘት ሊሰቅቀን ይገባል ። እያለን ካልሰጠን እየሌለን እንሰጣለን ወይ ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ። ካለን ነገር ላይ ካልሰጠን ከሌለን ነገር ላይ መስጠት አንችልም ። ብዙ ትዳር የሚታወከው ለእንግዳ የሚሆን ልብ ስለሌለው ነው ። በአንዳንድ ቤት እንግዳ ሲመጣ ሚስት ታኮርፋለች ፣ ወይም ባል ቤት ለቅቆ ይወጣል ። ከሰው ጋር ያልበሉት በሽታ እንደሚሆን አልገባንም ። ብዙ ባሎች ደጅ የሚያመሹት ትዳራቸው እንግዳን መቀበል ስለማይችል ፣ ቤት እንደሌለው ሰው እየተሰማቸው ጓደኞቻቸውን በደጅ እየሸኙ ነው ። ብዙ ሚስቶች በኑሮአቸው ኀዘነተኛ የሚሆኑት ከሰው ተፈጥረው ብቻቸውን ተዘግቶባቸው ሲኖሩ ነው ። 

ሌላም ወጣት ትዝ አለኝ ። ነገርን ነገር ያነሣዋልና ። ይህ ወጣት ደኅና የለበሰ ፣ ዘመናዊነት የሚታይበት ነው ። ወደ እኔ የመጣው ድንገት ነው ። እኔ ጋ ሲደርስ ሳይቀመጥ አንድ ነገር አለኝ፡- “ወደ አንተ ስመጣ እየጸለይኩ ነበር ። እርቦኛልና ምግብ ብላ ባለኝ ፣ ሻይ ጠጣ ባለኝ እያልኩ ነበር” ብሎ ስላልቻለ አለቀሰ ። ነጭ ለብሰው የተራቡ እንዳሉ እኔ ምስክር ነኝ ። ሆድን በልብስ አትለኩት ። ልብሱ የዛሬ ሦስት ዓመት የተገዛ ነው ። ሆድ ግን የአሁን ነው ። አንድ ችግረኛ ምግብ ከበላ በኋላ እንዲህ አለኝ፡- “ይህን ሆዴን ምን ላድርገው ? አሁን በልቼ ጠግቤአለሁ ምሳ ሰዓት ደግሞ ይክደኛል” ሲል አሳዘነኝ ። አዎ ሆድ ከሀዲ ነው ። መለመን ያፈሩ ፣ ከረሀባቸው ጋር የሚውሉና የሚያድሩ ስንቶች እንደ ሆኑ የፈጠረው ይወቀው ። ጌታችን “እንግዳ ተቀበሉ” ሲለን እንግዳ ስድስቱን ቃላተ ወንጌል ስለሚያሟላ ነው ። እንግዳ ረሀብተኛ ፣ ጥማተኛ ፣ ልብሱ የቆሸሸበት እርዝተኛ ፣ መንቀሳቀስ የማይችል እስረኛ ፣ የአሳብ ሕመምተኛ ነው ። ከዚህ ቀን ጀምራችሁ ቃል ግቡ ። እቤቴ የመጣውን ማንኛውንም እንግዳ እህል ውኃ ሳይቀመስ አይወጣም በሉ ። ትእዛዙን የሰጠ እግዚአብሔር በጀቱንም ይልካል ። 

እርቦት መጥቶ የፖለቲካ ወሬ ጋብዘነው የሄደው ሰው መንገድ ላይ ወድቆ ሊሆን ይችላል ። ቤታችን ቤቱ እስኪመስለው ድረስ ፍቅር አልሰጠነውምና አልነገረንም ። አንድ ቀን ሰማይ የሚባል ሩቅ ሀገር በእንግድነት እንሄዳለንና እንግዳን መቀበል አንርሳ ። መድኃኔ ዓለምን በቤታችን ከተቀበልነው በቤቱ ይቀበለናል ። ለድሮ ከባልንጀሮቻችን ጋር ልንለያይ ስንል መሣፈሪያ አለህ ወይ ብለን እንጠያየቅ ነበር ። አፍሮ ካልጠየቀ አሁን አምጡ ይላል ። በእግሩ ሲሄድ መሽቶበት በወንበዴ እጅ ሊወድቅ ይችላል ። የስሌት ኑሮ ውስጥ ስለገባን ይህን ለመቀበል ይተናነቀናል ። በሃይማኖት የቆመውን አገር በአስኳላ ትምህርት ማፍረሳችን የሚገርም ነው ። የፈረሱ ከተሞችን በማየት የምንሳሳለት ቤትና ገንዘባችን ከንቱ መሆኑን እንማር ። እንኳን ስለ ቤታችን ስለ ከተማችንም ዋስትና በሌለን ዘመን ላይ ደርሰናል ። ትዳር የእንግዶች መቀበያ መሆኑን አትዘንጉ ። እንግዳን የምንጠላው የመጀመሪያው እምነት ስለሌለን ፤ ሁለተኛው ሙያ ስለሌለን ነው ። ሁለቱንም ግን ዛሬ መማር ይቻላል ። ስንፍናም እንግዳን ትጠላለች ። 

ጌታ እግዚአብሔር፡- “ላልጠየቁኝ ተገለጥሁ” ይላል ። ኢሳ. 65፡1 ። እንግዶች ሳይጠይቁን በበረከት ልንገለጥላቸው ይገባል ። አምጡ ሳንባል የቤት ወጪን መስጠት መልመድ ያሻል ። ለቤታችን ማሰብ እንጂ መጠየቅ የለብንምና ። ለለመኑን ብቻ ሳይሆን ላለመኑን መስጠትም መለማመድ ያስፈልጋል ። ወንጌልን ያህል ሀብት ያገኘነው ፈልገነው ሳይሆን እግዚአብሔር ላልጠየቁት በሚገለጥበት ቸርነቱ ነው ። ጴጥሮስ ዓሣ እየፈለገ ፣ ጳውሎስ ወንጌልን ሊያጠፋ እየተፋጠነ ብርሃን በራላቸው ። የምሥራች ላልጠየቁ የሚገለጥ ነው ። የሞላ ነገር ይፈስሳልና የምሥራች ከእኛ ተርፎ የሚፈስስ ነው ። ለዓለሙ የሚሆንን ነገር ለግላችን ብንይዘው ትርፉ መጨነቅ ብቻ ነው ። ወንጌልም ለሰው ልጆች ሁሉ ነው ። ሰዎች ባይጠይቁንም ልንሰጣቸው ይገባል ። “ወንጌል እንግዳ ብሆን ተቀብላችኁኛል” ትላለች ። ማቴ. 25 ፡ 35 ። 

“ላልጠየቁኝ ተገለጥሁ ፣ ላልፈለጉኝ ተገኘሁ” ያለው ለአሕዛብ ስለደረሰው የወንጌል በረከት ነው ።

እግዚአብሔር ሆይ እንደ ዘመኑ ሳይሆን እንደ ቃልህ እንድኖር እርዳኝ  ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሰኔ 27 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም