የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 12

አገልጋዩና ሴቶች

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

ወጣቱ አገልጋይ ከወጣትና ከመካከለኛ ዕድሜ ካሉት ሴቶች የተለያየ ፈተና ሊደርስበት ይችላል ። በትልልቅ ሰርግ ውስጥ ትንንሽ ሰርግ አለ ይባላል ። በትልቅዋ ቤተ ክርስቲያንም ትንንሽ ቡድኖች ይስተዋላሉ ። ክርስቶስ የሞተው ለቤተ ክርስቲያን እንጂ ለቡድኖች አይደለም ። ክርስቶስ ለኅብረት ሞተ ፣ ሰዎች ለቡድን ይሞታሉ ። ሁሉም ወንዶች ለአገልጋዩ ፈተና እንደማይሆኑ ሁሉ ሁሉም ሴቶች የአገልጋዩ ፈተና አይደሉም ። ኤልያስን በረሀብ ዘመን ተቀብላ ያስተናገደች የሰራፕታዋ መበለት ፣ ኤልሳዕን ላሳርፈው ብላ በቁርጥ የተነሣች የሱነም ሴት ፣ ጌታችንን በገንዘባቸው ያገለገሉ ቅዱሳን አንዕስት ፣ በቤታቸው የተቀበሉት ማርያምና ማርታ ፣ ከሁሉ በላይ አምላክን የወለደች ድንግል ማርያም ታላላቅ ሴቶች ሁነው ተመዝግበዋል ። ወጣቱ አገልጋይ ወጣትነት በሚሰማቸው ሴቶች የሚደርስበት ትግል የጌጥ አምልኮን ለማስለቀቅ በሚነሣበት ጊዜ ነው ። ራስን መጠበቅ መልካም ነው ። ቁንጅናም ኃጢአት አይደለም ። ቁንጅና ትዕቢት ከሆነ ግን ዲያብሎስ በመጀመሪያ በወደቀበት ወጥመድ መያዝ ነው ። ቆንጆ የነበረው ሳጥናኤል ወደ ጥልቁ የተጣለው በቁንጅናው ትምክሕት ነው ። እግዚአብሔር እስከ ዛሬ የፈጠረውን አስቀያሚ ሰው አያውቅም ።

መንፈሳዊነት በጌጥና በልብስ ላይ ውሳኔ ያስተላልፋል ። ክርስቲያናዊ አለባበስ እንዳለ አማኝ ሁሉ ሊያውቀው ይገባል ። የዝሙት ማስታወቂያ መሆን ፣ ዕርቃንን አደባባይ መውጣት ፣ ለአምልኮ ነው የምሄደው እያሉ መገላለጥ ተገቢ አይደለም ። የመታየት ጥማት የመደበቅ ቀንን ይጠራል ። ቁንጅና ይበላሻል ፣ መልክም ይረግፋል ። የሰው ልጅ መልክና ቁመና የሣር ልምላሜ ፣ የአበባ ፍካት ነው ። ለመርገፍ ለመጠውለግ ይቸኩላል ። አሁን የታየው ሰው አሁን ይሰወራል ። ዳግም ላይመጣ ይሄዳል ። ሴቶች በሰው ለመታየት ሳይሆን በእግዚአብሔር ለመታየት ብቻ ወደ በቤተ ክርስቲያን ስለሚመጡ መሸፋፈን አለባቸው ። ቤተ ክርስቲያን የሀብትም ፣ የጌጥም ፣ የወርቅም ማሳያ አይደለችም ። ሁላችን ፍጹም ድሆች ፣ ክርስቶስ ፍጹም ባለጠጋ መሆኑን የምናምንባት ስፍራ ቤተ ክርስቲያን ናት ። የሌላቸውን እንዳናሳቅቅ በቤተ ክርስቲያን መሽቀርቀር ፍጹም ክልክል ነው ። ሁለት ባለጠጋ በአንድ አደባባይ አይቆምም ። ባለጠጋውን ጌታ ለማክበር ፍጹም ድሀ ሆኖ መቅረብ ያስፈልጋል ። ሁለት ቆንጆም በአንድ አደባባይ አይወዳደርም ። የሰው ሁሉ መልክ ክርስቶስ ነውና መልካችንን ብናሳይ እርሱን እንክደዋለን ። በቀራንዮ የሚታየው ያ በደም የተነከረ ገጽ የእኛ መልክ ነው ። የእኛን ፊት ለማለምለም እርሱ መልኩ ጠወለገ ።

ጌጣ ጌጦች ገንዘብን የሚጨርሱ ፣ ሰው በራሱ ተማምኖ እንዳይቆም የሚያስደነብሩ ፣ ራስህን በሸቀጥ አጉላ የሚሉ ፣ ተፈጥሮአዊ ሀብትን የሚነጥቁ ፣ ጤናን የሚጎዱ ፣ ለማንበብ የምናውለውን ጊዜ የሚሻሙ ፣ ራስን የዝሙት ንብረት የሚያደርጉ ፣ ሰው ይየኝ የሚሉ ጣዖታዊ አስተሳሰብ ውስጥ የሚከቱ ናቸው ። ወጣቱ አገልጋይ ይህን ለማስጣል ሲነሣ ብዙ ትግል ውስጥ ይገባል ። ተንኮለኛ በሆኑ ሰዎችና የአገልግሎት ትርጉም ሳይገባቸው አገልጋይ ነን በሚሉ ወገኖች ፣ እነዚህ ቆነጃጅት መጠቀሚያ በመሆን አገልጋዩን ለመጣልና ለማዋረድ መሣሪያ ይሆናሉ ። ብዙ አገልጋዮች በእነዚህ መጠቀሚያ በሆኑ ቆነጃጅት በአደባባይ በሐሰት ተከስሰዋል ።

ደግሞም ጥቂት በእውቀትና በዘመናዊነት ያደጉ ሴቶች አገልጋዩን ለመምራት ይፈልጋሉ ። ከእነርሱ መንገድ ሲወጣ ሰይፋቸውን ይመዝዛሉ ። ብዙዎችን ለማስተባበር አቅም ስላላቸው ጥቂት ተብለው የሚናቁ አይደሉም ። የትዳር አጋራቸውን ፣ ልጃቸውን ፣ የጾታ መሰሎቻቸውን ያስተባብራሉ ። ብዙ ዝርዝር ንግግር አይናገሩም ። “ይህን አገልጋይ ቀልቤ አይወደውም” ይላሉ ። አንድ ንግግር ደጋግሞ ሲነገር የሰዎችን አእምሮ እየተቆጣጠረ ይመጣል ። በዚህ ምክንያት ያ አገልጋይ እስኪነቀል ድረስ ትግል ውስጥ ይገባሉ ። ደግሞም ሌሎች ሴቶች መንፈሳዊነት ተሰማን እያሉ ትዳራቸውን ገሸሽ ማለት ይጀምራሉ ። መንፈሳዊነት ግን ቀድሞ ከሚወድዱት በላይ ትዳራቸውን ስለመውደድ የሚያስተምር ነው ። በዚህ ምክንያት ወንዶቹ ካህናትን መጥላትና መሳደብ ፣ መቃወም ይጀምራሉ ። ይህ ሁሉ ትግል አገልጋዩ ላይ ይመጣል ።

አገልጋዩ በማስተዋል መራመድ አለበት ። ርቀቱን ጠብቆ መሄድ ግዳጁ ነው ። ብዙም መቅረብ ፣ ብዙም መራቅን መከላከል አለበት ። ወጣት ሴቶችንም ሲያነጋግር በአደባባይ ፣ ሁሉም በሚያየው ስፍራ መሆን አለበት ። ቅን አገልጋዮች ሆይ ! የቤተ ክርስቲያን ጉዞ መስቀል የማይለየው ነውና ሁልጊዜ ንቁ ።

ሐዋርያው የጻፈልኝን ጦማረ ጽድቅ አስታወስኩት፡- “እንዲሁም ደግሞ ሴቶች በሚገባ ልብስ ከእፍረትና ራሳቸውን ከመግዛት ጋር ሰውነታቸውን ይሸልሙ፤ እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ፥ መልካም በማድረግ እንጂ በሽሩባና በወርቅ ወይም በዕንቍ ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ።” (1ጢሞ. 2 ፡ 9-10) ።

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 12

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ