መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ (4)

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ (4)

ልዩ ትምህርት

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

በጎዳናው ሁሉ የአገልግሎት ፈተናዎች ይታወሱኝ ነበር ። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ከበላይ ሁኖ ፍቅር የሚሰጠው አባት ፣ ምክር የሚለግሰው መምህር ፣ የሚያጽናናው ካህን ፣ ከውድቀት የሚያነሣው ሐዋርያ ያስፈልገዋል ። “አባት የሌለው አባት እግዚአብሔር አብ ብቻ ነው ።” ወጣቱ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ አባት ያስፈልገዋል ። ጉልበት ቢኖረው ብልሃት ያጥረዋልና ። ትጋት ቢኖረውም ሁሉም ነገር ዛሬ ካልሆነ ይላል ። ሰዎች የእርሱን የዲሲፕሊን ሕግ ስላልፈጸሙ ያዝናል ፣ ነገር ግን የአምላክን ሕግ መጠበቅ እንዳቃታቸው ይረሳል ። እርሱ ስለተቆጣ ክፉን ጥለው ፣ ደጉን የሚጨብጡ ይመስለዋል ። የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ እንደማይሠራ የሚገባው ዘግይቶ ነው ። የአያያዝ ችግር እንጂ ምእመንን ማቅናት ቀላል ነው ብሎ ያስባል ። በአባቶቹም ይፈርዳል ። አንዳንድ ሥርዓቶች ታሪክና ችግር ለወለደው ጉዳይ የተሠሩ መሆናቸውን ዘንግቶ ቀንበር ላንሣ ብሎ ይነቃቃል ። ሥርዓቱን ላንሣ ከማለት ለምን ተሠራ ? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል ። “ከበሮ በሰው እጅ ያምር ፣ ሲይዙት ያደናግር” እንዲሉ ቀላል የሚመስለው እረኝነት ከባድ መሆኑን የሚረዳው ብዙ ከቆሰለ በኋላ ነው ። እመራዋለሁ የሚለው ሕዝብ ልምራህ ሲለው ፣ አንዳንዴም የምእመናን አቅም ሙሴን ያህል መሪ ከምድረ በዳ ያስቀረ መሆኑን ቶሎ ላይረዳ ይችላል ። በመሪ የተሰናከለ ምእመን ሊኖር ይችላል ፣ በምእመን የተሰናከለ መሪም ብዙ አለ ።

ወጣት የቤተ ክርስቲያን መሪ ብዙ በመናገር ያምናል ። ለጥበበኛ ሰው አንዲት ቃል እንደምትበቃው ይዘነጋል ። ብዙ ንግግር የፊቱን እየጣሉ የኋላውን የሚረሱበት ነው ። “ብዙ ቢያወጉ ይዘነጉ ፣ ብዙ ቢተቹ ይሰለቹ” ነው ። ወጣቱ አገልጋይ ሁሉንም ነገር ወደ ቅኔና ትርጓሜ መውሰድ ይሻል ። በሁሉም ክስተት ካልሰበክሁ ይላል ። ቍጡና ፊት ለፊት ከሁሉ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ በቀላሉ ጠላት ያተርፋል ።

ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ልዩ ትምህርት የሚያስተምሩ ሰዎች ይገጥሙታል ። እነዚህ ሰግደው የገቡ ፣ አንገት ደፍተው የከረሙ ናቸው ። ተናጋሪ ምእመን ያፈራሉ እንጂ እነርሱ አይናገሩም ፤ በድብቅ እየሞሉአቸው ምእመናን በግልጽ ማውራት ይጀምራሉ ። ልዩ ትምህርት መባሉ አዲስ ነገርን ሁሉ እንደ መገለጥ ለሚያየው ትውልድ ነው ። ኑፋቄ የጀመረው በዓለመ መላእክት ሲሆን ጀማሪውም ሰይጣን ነው ። ሰይጣን በገዛ ኑፋቄው ተሰናክሎ ብዙዎችን ያሰናከለ ነው ። ኑፋቄ ክህደት አይደለም ። ግማሽ እውነት ፣ ግማሽ ምግባር ፣ ግማሽ እምነት ነው ። ውሸታም እንዳይባል የተወሰነ እውነት አለው ። ዓመፀኛ እንዳይባል ከፊል ምግባር ይታይበታል ። ከሀዲ እንዳይሉት ስመ እግዚአብሔርን ይጠራል ። ሰይጣን ከሙሉ ውሸት ይልቅ ከፊል እውነት ሥራውን ያስፈጽምለታል ። ሰይጣን የተሳካለት ክርስቲያኖችን በመግደል ሳይሆን ክርስቲያኖችን በማጋደል ነው ።

ኑፋቄ አንዳንዶች በጥመት ሲይዙት ሌሎች ግን ፈተና ሆኖባቸው ይቆራኛቸዋል ። ኑፋቄ ነቃፊ ስለሚያደርግ እኔ ብቻ ድኜ ሌላው ጠፋ ያሰኛል ። የራስን ችግር ላለማየት በሌላው ስህተት ውስጥ ይደብቃል። ኑፋቄ ፈሪሳዊ ጠባይ ያላብሳል ። የራሱን ትቶ የሌላውን ኃጢአት ይናዘዛል ። እግዚአብሔር ስላደረገለት ነገር ከማመስገን እንደ እገሌ ስላላደረግኸኝ አመሰግንሃለሁ ያሰኛል ። ራሱን ትንሽ አምላክ አድርጎ ይቆጥራል ። ራስ ተኮር የሆኑ ወሬዎችን ይወዳል ። እኔ ፣ እኔ ያበዛል ። ውስጣዊ ቅንነትን በውጫዊ ጌጥ ለመሸፈን ይሞክራል ። የማስተዳድራት የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ልዩ ትምህርት ይዘው የገቡ ሰዎች ነበሩባት (1ጢሞ. 1 ፡ 3) ።

እነዚህ ሰዎች እኛ በአደባባይ ስናገለግል እነርሱ በጸሎትና በጽሞና ስም በየቤቱ ምእመናንን ይዘው እንክርዳድ ይዘሩባቸው ነበር ። “እንዲህ ብላችሁ ጠይቁ” በማለት ከአስተማሪዎቻቸው ጋር ትግል ውስጥ እንዲገቡ የዋሆችን ያሰለጥናሉ ። ምእመናንም አብረዋቸው ያለቀሱትን ፣ ለታላቅ ዕድል ያበቁአቸውን አባቶች ጠልተው በቤተ ክርስቲያን በተቃዋሚነት ይቀመጣሉ ። አገልጋዮች የሚኖሩት እኛ በምንሰጠው ገንዘብ ነው በማለት ካህናተ እግዚአብሔርን እንደ ቤት ሠራተኛቸው ማየትና ማዘዝ ይጀምራሉ ። በዚህ ምክንያት በመንጋውና በእረኛው መካከል ጠላትነት ይፈጠራል ። ተኩላው ወዳጅ ፣ እረኛው ጠላት ይደረጋል ። ተኩላው ሊያርድ እያሰባ መሆኑን የሚያውቁት ከወጡና ሜዳ ላይ ከወደቁ በኋላ ነው ።

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 4

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 18 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም