መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት

 

ሥጋ እንደ ልብስ ፣ ነፍስ እንደ አካል ፤ ሥጋ እንደ ታቦት ፣ ነፍስ እንደ ጽላት ፤ ሥጋ እንደ ሰገባ ፣ ነፍስ እንደ ሰይፍ ፤ ሥጋ እንደ ገበታ ፣ ነፍስ እንደ እንጀራ ፤ ሥጋ እንደ አደባባይ ፣ ነፍስ እንደ ቃል መሆኗን ያወቅሁት ዘግይቶ ነው ። ሥጋ የነፍስ መጎናጸፊያ ናት ፣ ምድር የሥጋ አገር ናትና በአገርዋ ነፍስን የምታላምድ ናት ። ሥጋ እንደ ምላስ ስትሆን ነፍስ ደግሞ በምላስ ውስጥ እንዳለ ቃል ናት ። ሥጋ እንደ አረጀ ልብስና እንደ ቆሸሸ ሰገባ ናት ። ነፍስ ግን ሰይፍ ናት ። በቀላሉ የምትወለወል ፣ የክፉውን አሳብ ለመጣል የምትታገል ናት ። ሁልጊዜ ነፍስ ወደ ላይ ፣ ሥጋ ወደ ታች ይሳሳባሉ ። የመሳሳቡ ሜዳ “መኖር” ሲባል ሲላቀቁ ሥጋ “አፈር” ፣ ነፍስም “መንፈስ” ይሆናሉ ። ሥጋ እንደ ልባሽ ጨርቅ ፣ እንደ አረጀ ሰገባ ፣ እንደ ድሮ ዕቃ ፣ እንደ ቆሸሸ ገበታ ፣ እንደ ፈረሰ አደባባይ መሆኗን ያ ቀን ነገረኝ ። ሽቅብ ወደ ላይ ስጓዝ በተጓዝሁ ቍጥር ሥጋዬ ትርቀኝ ነበር ። ወደ ነፍስ መጓዝ ከሥጋ ፣ ወደ ሰማይ መጓዝ ከምድር መራቅ ነው ። ልቀቀኝ እያሉ መታገል ነፍስን ከሥጋ ፣ መንፈስን ከምድር አይለይም ። ወደ አንደኛው መጓዝ ከሌላኛው መራቅ ነው ። በመጓዝ እንጂ ቆሞ በመደራደር መላቀቅ የለም ።

   

ከሥጋ ወጥቼ በነፍስ አካልና አቋም በነፍስ የኑሮ ሥርዓት ውስጥ ስገባ ፍርሃት ፣ ጭንቀት ፣ መርገብገብ ፣ መንታ ማንነት ፣ የተለዋወጠ ስሜት ጥሎኝ ሲሄድ ታወቀኝ ። ፍርሃትም ልክ አለው ። የፍርሃት ልኩ እስከ ሰማይ ነው ። በሥጋዬ ሁለት ጌታ ተሸክሜ እኖር ነበር ። የነፍስ ጉዞ ስጀምር ግን ለአንድ ጌታ አደርሁ ። ለአንድ ጌታ ማደር ክብር ነው ። ለሁለት ጌታ ያደረ ሁለቱም አያምኑትም ። እርሱም ሚዛኑን ላስተካክል ሲል በጭንቀት ያብዳል ። ለማረፍ የጀመረው ጉዞ ጭንቀት ይሆንበታል ። ወደ እግዚአብሔር ገነት እየተቃረብሁ ስመጣ ገነት የአትክልት ስፍራ ናት የሚለው ግምቴ ከንቱ ሆነብኝ ። አትክልት የሚያስፈልገው ደረቅ ነገር ስላለ ነው ። በገነት ግን የእግዚአብሔር ልጅ የዘላለም ልምላሜ ነውና አትክልት አያስፈልግም ። ገነት ሲባል አበባ ያለባት ውብ ስፍራ ትመስለኝ ነበር ። መልአኩ ግን ነጠቅ አድርጎ ፣ የልቤን አውቆ “የቅዱሳን መዓዛ ክርስቶስ ነው” ብሎ የአባቶቼን ምስጋና አስታወሰኝ ። ዛፍ የሚያስፈልገው ቃጠሎ ላለበት ነው ፣ ገነት ግን ከፀሐይ በላይ ናትና ዛፍ አያስፈልጋትም ። ገነትን የሚያጠጡ ወንዞች በሰማይም እየጠበቅሁ ነበር ። ክርስቶስ እርካታ በሆነበት ስፍራ ምንጭ አስፈላጊ አልነበረም ። 

ቅዱሱ መልአክ፡- “መጥተህ ርስትህን እንደ ቸርነቱ እስክታገኝ ድረስ ለዛሬ የተፈቀደልህ ሐዋርያውን ቅዱስ ጳውሎስን እንድታገኝ ነው” አለኝ ። በመቀጠልም፡- “ይህ የብቃትህ ውጤት ሳይሆን አገልግሎትን ሳይጀምሩ የጨረሱ የሚመስላቸው በዝተዋልና በጳውሎስ አንደበት ገና መሆኑን እንዲሰሙ ነው ። ለዚህም አንተ ድምፅ ማጉያ ነህ ። አንድ ቀን ወደዚህ መምጣትህ አይቀርምና ሰማይ ደርሼ መጣሁ እያልሀ አታውራ ። የክርስቲያን ጠባቂው ትሕትናና ምሥጢር የመያዝ አቅም ነው” አለኝ ። እኔም በቅዱሱ መልአክ ፊት ጆሮ እንጂ አፍ አልነበረኝም ። ሰማይ አስደሳች ግርማ ያለበት ነው ። በምድር ላይ የነበረኝ ድፍረትና ቀደም ቀደም ማለት አልተከተለኝም ። የሥጋ ትልቅነትም በሰማይ ስፍራ የለውም ። በሰማይ ማወቅ ጥቅም የለውም ። በሁሉ ጌታ መታወቅ ብቻ የዘላለም ሕይወት ተብሎ ይጠራል ። በሰማይ የሃይማኖት ትምህርት የለም ፣ የሃይማኖት ዋጋ የሆነው እግዚአብሔር ግን አለ ። ብዙ ምርምር ለሰማይ አይጠቅምም ፣ የመጨረሻ እውቀት በዚያኛው ዓለም ገና አዲስና ዝቅተኛ እውቀት ነው ። 

ዓይኖቼ ቅዱሱን መልአክ ሰርቀው ያያሉ ። ባሻገር ደግሞ አንዳንድ ሰዎችን ያያሉ ። የማልጠብቀው አንድ ኃጢአተኛ ታየኝ ። ዓይኔን ማመን አቃተኝ ። “እንዴት እርሱ እዚህ ተገኘ?” የሚል መደነቅ ያዘኝ ። እኔ ስለምወዳቸው የሚጸድቁ የመሰሉኝን የእኔን ጀግናዎች ብፈልግ ብቅ አይሉም ። በልቤ፡- “እነ እገሌ እንዴት እዚህ ተገኙ ? እነ እገሌስ እንዴት ከዚህ ጠፉ ?” ልል ስል ቅዱሱ መልአክ ለካ የልቤን አሳብ ያውቀው ነበርና፡- “አንተ በዚህ ስለመገኘትህ ብቻ አመስግን ሌላው ያንተ ድርሻ አይደለም” አለኝ ። እኔ የመጣሁበት ዓለምና አገር ሰው የራሱን አስቀምጦ የሰውን የሚጫወትበት ፣ የሚመለከተውን ለይቶ የማያውቅበት ነው ። ቅዱሱ መልአክም በግሣጼም መለሰኝ ። በሰማይ ማዳለል የለም ። መልሼ ውስጤ ትሑት የሆነ መሰለኝና፡- “እኔ እዚህ በመገኘቴ እንዳላረክሳቸው” አልኩኝ ። ትሕትናዬም ትዕቢት ነበርና ቅዱሱ መልአኩ ገሠጸኝ ። “በአንተ ኃጢአት የሚረክስ መቅደስ ከሆነ ቀድሞም ቅዱስ አልነበረም ማለት ነው ። ከንቱ ትሕትና ከክርስትናና ከአገልግሎት ያወጣሃልና ተጠንቀቅ” አለኝ ። ቅዱሱ መልአክ ትዕቢቴንም ትሕትናዬንም ገሠጸው ። ትሕትና የሚመስሉ ሰይጣናዊ ማስበርገጊያዎች አሉ ። ከተመኘሁ አይቀር ባመነዝር ፣ በልቤ ከጠላሁ አይቀር ብገድልስ ፣ በእግዚአብሔር ቤት ሆኜ ከምበድል በዓለም ሆኜ የፈለግሁትን ብሠራ ይሻለኛል ። ያልኖርኩትን ከመናገር ስኖር ብሰብክ መልካም ነው ። እኔ ታምሜ ስለ ሌላው ድካም እጨነቃለሁ ። ለራሴ መግቢያ የለኝ ብዙ ስደተኛ አስከትላለሁ የሚሉ የትሕትና ማር የተላበሱ ሰይጣናዊ እሬቶች ናቸው ። በሰማይ እውነት ብቻ ስፍራ አለው ። ውሸቴ ታረመ ። ትሕትናዬም የትዕቢት ታናሽ ወንድም ነበረ ። 

ሐዋርያውን ቅዱስ ጳውሎስን ለማግኘት ብመጣም በዚሁ ጌታዬን ባየሁት ብዬ ማሰብ ጀመርሁ ። ቅዱሱ መልአኩ ግን፡- “ጳውሎስን ስታይ ክርስቶስን ታያለህ” አለኝ ። እኔም ሐዋርያው ያለውን አስታወስሁ ። “እኔ ክርስቶስን እንደምመሰል እኔን ምሰሉ” ያለውን አስታወስሁ ። ቅዱሱ መልአክም፡- “እኛም ክርስቶስን የምናየው በዓይን ሳይሆን በማመን ነው ። ዓይን የሚያየው የመጠኑን ያህል ነው ። ክርስቶስ በምድርም በሰማይም ብትሆን የሚታየው በእምነት ነው” አለኝ ። እኔም አንድ ጊዜ በምድር ሳለሁ “እምነት እግዚአብሔርን የምናይበት መነጽር ነው” የሚል ትምህርት እንደ ሰማሁ አስታወስሁ ። ከመልአኩ ጋር እያወራሁ ወደ ምድር መመለስ እያስፈራኝ መጣ ። “ደስታውን ሳታጣጥም ስለመመለስ ለምን ታዝናለህ?” በማለት መልአኩ አረጋጋኝ ። እኔም ለመልአኩ፡- “ሐዋርያው ጳውሎስ እስከ ሦስተኛ ሰማይ ድረስ መጥቶ እንደ ገና ተመልሶ ማገልገል መፈለጉ ይገርመኛል” አልኩት ። “አዎ ሰማይ ስትደርስ ትልቅ የመሰለህ አገልግሎትህ ያንስብሃል ። ተመልሰህ ማገልገልና የሃይማኖት ገድል መፈጸም ትፈልጋለህ” አለኝ ።

ከመልአኩ ጋር እያወጋሁ ሳለሁ ሐዋርያው ጳውሎስ ሲመጣ ከሩቅ አየሁት ። እኔም መንገድ አጋምሼ ብቀበለው ብዬ ሳስብ መልአኩ ከለከለኝ ። “ገና ወደ ሥጋ ማደሪያ የሚመለሱ ከዚህ ማለፍ አይችሉም ፣ ሙሉውን ክብር የምታየው ቆርጠህ ስትመጣ ነው ። የምታየው በመጣህበት የቆራጥነት መጠን ነው” አለኝ ። ከደስታ የተነሣ ልቤ መዝለል ጀመረ ። ደስታ እያንጠራራኝ ፣ የሟሸሸውን ሰውነቴን እየወጠረው መጣ ። ነፍሴ በሐሤት ተሞላች ። መልአኩ የሚመልስልኝን መልስ መምህሬ የኔታም ይሰጡኝ ከነበረው ፍቺ ጋር ተቀራረበብኝ ። በሰማይና በምድር አንድ ድምፅ አለ ። እርሱም እውነት ነው አልኩኝ ። ጥያቄ አንድ እስከሆነ ድረስ በሰማይም በምድርም የምሰማው መልስ ተመሳሳይ ነው ። ተመሳሳይ መልሶች የተመሳሳይ ጥያቄ ውጤት ናቸው ። ኦ እግዚአብሔር ይመስገን ጳውሎስን አየሁት ፣ ጳውሎስን አገኘሁት ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታሕሣሥ 18 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም