መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /11/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /11/

 

ሐዋርያው ጳውሎስ ከዚህ በፊት እንዳደረገው ነገሮችን እስክረዳቸው ድረስ ይጠብቀኝ ነበርና ገረመኝ ። እርሱ ግን፡- “አትገረም እኛ ለጆሮ ስንናገር እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ለልብ ይናገራል ። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ያንን ሰው እስኪገልጥለት ድረስ ከተናገርን በኋላ በትዕግሥት መጠበቅ አለብን ። ዓይኑን ጨፍነን ፣ ጆሮውን ደፍነን የምናድነው ሰው የለም ። ከሚያየው ይልቅ የማይታየውን ክርስቶስ ፣ ከሚሰማው ብዙ ነገሮች ይልቅ ወንጌልን ሰምቶ መዳን የሰው ነጻ ፈቃድ ነው” አለኝ ። እኔም መንፈስ ቅዱስ እንዲሠራ ጊዜ ያልሰጠሁበትን ዘመን አሰብሁና ችኮላዬ ሳይሆን ትጋቴ ሰውን እንደሚያተርፍ አስተዋልሁ ። ቅዱስ ጳውሎስም ሁለተኛውን ሐዋርያዊ ጉዞውን ሊነግረኝ ስለፈለገ አሳቤን አቋርጦ ጉዞውን መተረክ ጀመረ ። 

“የመጀመሪያውን ሐዋርያዊ ጉዞ እንዳደረግሁ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም የመጀመሪያውን ጉባዔ አደረጉ ። ይህ ጉባዔ የሲኖዶሶችና የውሳኔያቸው ፊታውራሪ ነው ። ሲኖዶሱም የተሰበሰበው የሰውን መዳን በሚመለከትና የቢጽ ሐሳውያንን መሰናክል አንሥቶ የአሕዛብ አብያተ ክርስቲያናትን ለማጽናት ነው ። በኋላ ዘመን ይደረጉ የነበሩ ሲኖዶሶች በሐዋርያት መንበር ላይ የተሰየሙ አባቶች የሚያደርጉት ቢሆንም ዋዛ ፈዛዛ ነገር የበዛበት ፣ ከጽድቅና ከኰነኔ የማይገቡ ነገሮችን በማንሣት ፣ ጊዜ መግፊያ ፣ ጉንጭ ማልፊያ እንደነበር እናውቃለን ። ሲኖዶስ ግን በጀት አጽድቆ ፣ ወንጀል አውግዞ የሚለያይ ሳይሆን ሰውን ለማጽደቅ ፣ ሽፍታውን ባሕታዊ ለማድረግ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚመክር ነው ። እንዴት እናውግዝ ብሎ ውግዘትን የቂምና የበቀል በትር የሚያደርግ ሳይሆን እንዴት የጠፋውን እንመልስ ብሎ የሳቱትን መንገድ የሚያሳይ ነው ። የጭካኔ በትር የሚያሳርፍ ሳይሆን የፍቅር እጅ የሚዘረጋ ነው ። ቤተ ክርስቲያን ልጆችዋ እየተራቡ ገንዘብ በማከማቸት የሚደሰት ሳይሆን ምእመናንን ከረሀብ አትርፎ ገንዘብን አሳንሶ የሚያይ ነው ። በኪራይ ሕንፃዎች የሚኮራ ሳይሆን ሕንፃ ሥላሴ የሆነውን ሰው የሚታደግ ነው ። ከቄሣሮች ጋር ለመስማማት ምን እንበል ? የሚል ፣ ላሸነፈ የሚያድር ሳይሆን ከተጠቁት ጋር የሚቆም ነው ። ለባለጠጎች እውቅና የሚሰጥ ሳይሆን ድሆችን ከችግር የሚያሳርፍ ነው ። ዓለም እየታመሰች የቅንጦት ውይይት ይዞ የእመቤታችን የድንግል ማርያም የዓይኗ ቀለም ጥቁር ነው ወይስ ሰማያዊ ፣ የቅዱስ ቍርባን ጽዋ ውስጥ ዝንብ ቢገባ ዝንቡ ይቀደሳል ወይስ ደሙ ይረክሳል ? እያሉ ይወያዩ የነበሩ የሐዋርያትን ስም የያዙ አባቶች እንደተነሡ በሰማይ ሰምተን ተገርመናል ። እኛ ሰይፍን ተደግፈን የሰበክነውን ወንጌል የወርቅ ዘንግ ይዘው መስበክ ለምን አቃታቸው ? የእነርሱ ዕረፍት የመጣው በእኛ ድካም መሆኑን ለምን ዘነጉት ? ብለን የሰማይ ማኅበረተኞች በሙሉ አዝነናል ።

የመጀመሪያው የሐዋርያት ሲኖዶስ እንደተፈጸመ ሁለተኛውን ሐዋርያዊ ጉዞዬን ቀጠልሁ ። ሁለተኛው ሐዋርያዊ ጉዞ በሐዋ. 15፡36 እስከ ምዕራፍ 18፡22 ተመዝግቦ ተቀምጧልና ማየት ትችላለህ ። ማርቆስ እናቱ ናፍቃው ወዲህም መከራው አሰቅቆት ወደ ኋላ ተመልሶ ነበርና እኔም ቆራጥ ፣ ቆፍጣና ፣ ጊዜውን ሳይሆን ነፍሱን አስቀምጦ የሚዘምት ወታደር እፈልጋለሁና አዝኜበት ነበር ። ታዲያ ማርቆስ በመጀመሪያው ጉዞ ተለይቶን በሁለተኛው ጉዞ ልቀላቀላችሁ ብሎ መጣ ። በእርግጥ የሄደበት ጉዳይ የእናት ናፍቆትም ከክርስቶስ ፍቅር በላይ ፣ ሥጋዊ ዕረፍቱም ስለ ወንጌል ከሚቀበሉት ትግል በላይ አስደሳች አይደለምና ተመልሶ መጣ ። ጥሪ ያለው ሰው በፍቅርም በመከራም አሳብቦ ቢመለስም የሚሄድበት ቦታ የመቃብር ስፍራ ፣ ሕይወት የሌለበት መንደር ይሆንበታልና ተመልሶ ይመጣል ። ማርቆስም ተመልሶ መምጣቱ መልካም ቢሆንም ከልፍስፍስ ጋር መሰለፍ አልወድምና እንዳላይህ ብዬ አባረርሁት ። ሰው የሚመዘነው በዕድሜውና ባወቀው መጠን ነው የሚል ሰዋዊ መመዘኛ አልነበረኝም ። የእግዚአብሔር ቃል ሽማግሌውንና ወጣቱን እኩል ያስጠብባልና እገሌ ልጅ ነው እንደፈለገው ይኑር የሚባለውን ሥጋዊ ኀዘኔታ አልቀበልም ። በርናባስ ግን ማርቆስን ጥሎ መሄድ አልሆነለትም ። በዚህ ምክንያት ሊያሳምነኝ በሞከረ ቍጥር እኔ እየጠነከርሁ መጣሁ ። ከምወደው በርናባስ ጋርም እስክንከፋፋ ተጣላን ። በዚህ ጊዜ በርናባስ ማርቆስን ይዞ ወደ ቆጵሮስ ለመስበክ ሄደ ። እኔም ሲላስንና ጢሞቴዎስን ይዤ ወደ ሶርያና ወደ ኪልቂያ ወጣሁ ። እግዚአብሔር ለበጎ አደረገውና አንድ ቡድን የነበረውን ፣ ሁለት ሐዋርያዊ ጉዞ የሚያከናውን ቡድን አደረገው ። አንድ ቡድን ቢሆን ኖሮ በአንድ ጊዜ ወደ ቆጵሮስም ወደ ሶርያም መሄድ አይሆንልንም ነበር ። እኔም ሲላስን ለመምረጥ ጢሞቴዎስን ለማጥመቅ የበቃሁት በማርቆስ ምክንያት ነው ። ማርቆስ እየበደለን የሚክሰን ሰው ነበር ። 

ሁለተኛው ሐዋርያዊ ጉዞዬ ጢሞቴዎስን ያገኘሁበት ነው ። ይህ በዓላማ የሚመስለኝን አማኝ ፣ የሚታዘዝልኝን ልጅ ፣ ዘመኑን የሰጠ ድንግል ቤተ ክርስቲያን ያገኘችው በሁለተኛው ሐዋርያዊ ጉዞዬ ነው ። ኋላ ላይም የኤፌሶን ጳጳስ አድርጌ ሾምሁት ። የግሪክ አብያተ ክርስቲያናት የተመሠረቱት በሁለተኛው ጉዞዬ ነው ። በዚህ ጉዞ መነሻ ያደረግነው አንጾኪያን ነበር ። ጉዞው ሶርያ ፣ ኪልቅያ ፣ ደርቤን ፣ ልስጥራን ፣ ፍርግያ ፣ ገላትያ ፣ ጢሮአዳ ፣ ሳሞትራቄ ፣ ናጱሌ ፣ ፊልጵስዩስ ፣ አንፊጶልያ ፣ አጶሎንያስ ፣ ተሰሎንቄ ፣ ቤርያ ፣ አቴና  ፣ ቆሮንቶስ  የተደረገ ነው ። በዚህ ጉዞ 16 ከተሞችን በወንጌል አገልግለናል ። ጉዞው የተጀመረው በ50 ዓ.ም ነው ። በዚህ ጉዞ የፊልጵስዩስ ፣ የተሰሎንቄና የቆሮንቶስ አብያተ ክርስቲያናት ተመሠረቱ ። 

ሦስተኛው ሐዋርያዊ ጉዞዬ በሐዋ. 18፡23 እስከ ምዕራፍ 21፡16 የተመዘገበ ነው ።  በዚህ ጉዞዬም  መነሻዬ አሁንም አንጾኪያ ናት ። ገላትያ ፣ ፍርግያን ፣ አሶን ፣ ሚሊጢን ፣ ኤፌሶን ፣ ቆስ ፣ ሩድ ፣ ጳጥራ ፣ ጢሮስ ፣ አካ ፣ ቂሣርያ በወንጌል ሲከለሉ ፣ በመጨረሻም ወደ ኢየሩሳሌም ጉዞዬን ቀጠልሁ ። በዚህ ጉዞ 12 አገሮችንና ከተሞችን በወንጌል አገልግያለሁ ። ወደ ኢየሩሳሌም የሄድሁበት ዋነኛ ምክንያትም ከአሕዛብ አብያተ ክርስቲያናት ያሰባሰብሁትን የገንዘብ እርዳታ ለማስረከብ ነው ። በዚያም በተነሣ ሁከት ታስሬ በ58 ዓ.ም ወደ ሮም ተወሰድሁ ። በሮምም የቁም እስረኛ ሁኜ ለሁለት ዓመታት ያህል ከቆየሁ በኋላ በቄሣር ችሎት ነጻ ነው ተብዬ ተለቀቅሁ ። ከዚህ ጊዜ በኋላ አራተኛውን ሐዋርያዊ ጉዞ አደረግሁ ። እስጳንያን የጎበኘሁት በዚህ በአራተኛው ጉዞዬ ነው ። በ64 ዓ.ም ኔሮን ቄሣር ሮምን ራሱ አቃጥሎ በክርስቲያኖች ላይ ስላሳበበ በ65 ዓ.ም እንደገና ለእስር ተዳርጌ ከሁለት ዓመት እስር በኋላ በ67 ዓ.ም. ሐምሌ አምስት ቀን በሮም ሰማዕትነትን ተቀበልሁ ። 

በሦስተኛው ጉዞዬ ወቅት እርዳታን ለኢየሩሳሌም ድሆች ለማድረስ መሄዴን እደሰትበታለሁ ።  የገጠመኝ ነገር ታላቅ መከራ ቢሆንም እውነትን በሚገጥመኝ ነገር ሳይሆን በእውነትነትዋ መለካት አለብኝ ብዬ አምን ነበር ። እውነት ከገጠመኝ በላይ ናት ። በዚያ ዘመን ከሰንበት አገልግሎት በኋላ በተወከሉ ሰዎች አማካይነት እርዳታ ለድሆች ይሰባሰብ ነበር ። የመጀመሪያ የእርዳታ ድርጅት የተመሠረተው በመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው ። ድሆችን የረሳች ቤተ ክርስቲያን በምጽአት ቀን በክርስቶስ ፊት ለመቆም ሞገስ የሌላት ቤተ ክርስቲያን ናት ። እናንተም ድሆችን በሚመለከት በጣም ቸልተኛና ጨካኝ እንደሆናችሁ ሰምተናል ። ብድር ለሚመልሱ ሰዎች ደግሞ እያነቃቸው እናጉርስ የምትሉ ፣ እከክልኝ ልከክልህ ማለትን የምትወዱ ሥጋውያን መሆናችሁን ሰምተን ማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት አዝናባችኋለች ። ይግባኝ በማይጠየቅበት የፍርድ አደባባይ መልስ እንዳታጡ ድሆችን አስቡ ። ድሆች በክርስቶስ ፊት ጥያቄዎቻችሁም መልሳችሁም ናቸው ። ዳግም ወደ ምድር የመመለስና የመኖር ዕድል ቢገጥመኝ ተግቶ ወንጌልን መስበክንና ድሆችን መርዳትን አከናውን ነበር ። ሰማይ ደርሳችሁ ትልቅ ዋጋ ስትቀበሉ በምድር የሠራችሁት ያንስባችኋል ፣ እኛ ሠርተን ካነሰብን እናንተ ስንፍናን ጌጥ ያደረጋችሁት ፣ ሞልቃቃነት ከእግዚአብሔር እንደሚለይ የዘነጋችሁት ምን ሊሰማችሁ ይችላል ብዬ አስባለሁ” አለኝ ። እኔም በርግጥ ድሀን የምወደው በአፍ ነው ? ወይስ በተግባር ነው ? ብዬ ራሴን ጠየቅሁ ። 

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

የካቲት 15 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም