መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት/ 2

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት/ 2

 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ እኔ እየተጠጋ ሲመጣ በታላቅ ደስታ ውስጥ ሆኜ በሲቃ ድምፅ መናገር ጀመርሁ ። እርሱ ግን ከዚህ በፊት እንደሚያውቀኝ በታላቅ መረጋጋትና ፍቅር እየቀረበኝ መጣ ። እውነት የራስዋ ግለት አላት ፣ ስሜትም የራስዋ ግለት አላት ። የእውነት ግለት እንደ ፍም በመሆኑ ይቆያል ፣ የስሜት ግለት ደግሞ እንደ ቅጠል እሳት በመሆኑ ቶሎ ያበቃል ። ፍም አመድ አለውና ቀሪ ነገር አለው ፣ የቅጠል እሳት ግን አመድ የለውም ። ከሚግለበለበው የቅጠል እሳት ዝም ያለው የፍም እሳት የተሻለ ነው ። አንዳንድ ሰዎች ብክነታቸውን ትጋት ፣ ቍጣቸውን መንፈሳዊ ቅንዓት ይሉታል ። ሁሉን ልያዝ ሁሉን ልጨብጥ በማለት ዓለም ቤቴ ናት ይላሉ ። የእነርሱን ትንሽ እውቀት ውኃ ጨምረውበት ለሰው ዘር ሁሉ ለማዳረስ ይፈልጋሉ ። እንቅልፍ በማጣታቸውና በመናገራቸው ትውልድን እየወለዱ መስሎ ይሰማቸዋል ። መንፈሳውያን ሰዎች ትኩስ ናቸው ። ትኩሳቱ ግን እንደ ፍም እሳት የሚቆይ ነው ። ምድራውያን ሰዎች ግን ቶሎ የሚያበቃ ትኩስነት አለባቸው ። ሐዋርያው እስከ ነገ በሚተርፍ ነገ ከተባለው ከጊዜ ቀጠሮም የሚዘልል መንፈሳዊ ግለት አየሁበት ። እኔ ከምድር የመጣሁ በመሆኑ ያየሁትንና የሰማሁትን ሳላጣጥም ፣ እገሌን አየሁት ብዬ የመረጃ ሽያጭ ለማድረግ እፈልጋለሁ ። ሰበር ዜና ብዬ የወሬ እሽቅድድም ውስጥ እገባለሁ ። ሁሉ አይወራም የሚለው ጨዋነት ጠፍቶ ሁሉን የማውራት የሕፃን ባሕል ውስጥ ገብተናል ። 

ሐዋርያው ጳውሎስ መልኩ ምን እንደሚመስል ያዩት  ሰዎች ገጣጥመው አስቀምጠውልናል ። ጭንቅላቱ ትልቅና ራሰ በራ ፣ የሁለቱ ቅንድቦቹ ጠጉር የተጋጠሙ ፣ ዓይኖቹ ሰማያዊ ቀለም ያላቸው ሲሆኑ ዘወትር ብርሃን ነበሩ ። አፍንጫው ትልቅና ቀጥ ብሎ የወረደ ጽሕሙና ሪዙም ረጃጅም ሲሆኑ ከአንገቱ አጠር ያለ ሁኖ ትከሻው ክብና ጎባባ እግሮች ደግሞም ከጉልበቱ ላይ የተቃረቡ ናቸው ። ቁመቱ አጠር ያለ ከድንክ የረዘመ ደንደን ያለ ሰው እንደነበር ይነገርለታል ። የሰማሁትን ያንን መልኩን ስፈልግ የነፍስ መልኳ ሁለት ዓይነት መሆኑን ተገነዘብኩ ። ነፍስ ወይ ክርስቶስን ወይ ሰይጣንን ትመስላለች ። ነፍስ የምትመስለው ምርጫዋን ነው ። ነፍስ ዘር የላትም ፣ ግዙፍና ቀሪ አይደለችምና ። ነፍስ ጎሣ የላትም በክርስቶስ ከመዛመድ ውጭ ልክ የሚሆናት አታገኝምና ። ሐዋርያው አጠገቤ ሲቆም ሰላም ተሰማኝ ። እኔ የማውቃቸው መንፈሳውያን ነን ብለው የሚያስቡ አጠገባቸው ሰው ሲደርስ እንዲወድቅ የሚፈልጉ ግርማዊ ምኞት ያላቸው ናቸው ። እውነተኛ መንፈሳዊነት ግን እንደ ማግኔት ተቃራኒውን ይስባል ። የተቀደሱ ሰዎች ለረከሱ ሰዎች ዕረፍት ይሰጣሉ ። የእግዚአብሔር ንጽሕና አያስበረግግም ። 

ሐዋርያውን “እንዴት ነህ ?” ብዬ ምድራዊ ሰላምታ ላቀርብለት ፈለግሁ ። ሰው የሚሰጠው ያለውን ነውና ። “በክርስቶስ ያደረ ግን እንዴት ነህ ?” አይባልም ። ሁለት ልብና ዓለም ያለው ብቻ እንዴት ነህ  ? ይባላል ። ስለ እኛ ዓለም ልተርክለት ፈለግሁ ክፋት የማይዳነቅበት ዓለም መሆኑን በዓይኑ ገርመም አድርጎ አሳወቀኝ ። ደግሞም “እነዚህ የሚወራው ስለ እግዚአብሔር ቅድስና እንጂ ስለ ፍጡር ክፋት አይደለም” አለኝ ። ቅዱሱ መልአክም አልተለየኝም ። መላእክትን ልዩ የሚያደርጋቸው የእግዚአብሔር ልጆችና የቅዱሳን ጠባቂዎች መሆናቸው ነው ። ልጁን ጠባቂ የሚያደርግ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። መላእክት ለጥበቃቸው የሚያገኙት ደመወዝ የእግዚአብሔር ፍቅር ይበዛላቸዋል ። 

ሐዋርያው ጳውሎስ ብርቱ በሆነ ራስ ምታት የሚሰቃይ ሰው ነው ። ከራስ ምታቱ የተነሣ ዓይኑን እንኳ መግለጥ ይቸገር ነበር ። በዚህ ምክንያት አንዳንድ መልእክቶቹን ዓይኑን ጨፍኖ ለፀሐፊ ሲነግር ጻፊው ብራናና ብርዕን አስማምቶ ይጽፍለት ነበር ። በጨርቁ ቅዳጅና በጥላው ድውይ የሚፈውስ ሰው እንዴት የራሱን ራስ ምታት ማስወገድ ያቅተዋል ? ለሚል ወታደር በተሰጠው መሣሪያ አገሩንና ሕዝቡን እንጂ ራሱን አያገለግልም ብለን እንመልስለታለን ። ጸጋ መሣሪያ ነው ፣ መሣሪያነቱም ሌሎችን ለመጠበቅ ነው ። ሐዋርያውን ሳየው ያ ሕመሙ ትዝ አለኝ ። እርሱ አሁን በሕመም ውስጥ ባይሆንም ሕመሙ ግን በበሽታ የሚሰቃዩ አገልጋዮችን ያጽናናል ። የተጻፈው ሁሉ ለሦስት ነገሮች ተጽፎአል ። ለትምህርት ፣ ለተግሣጽና ለማጽናናት ።

ሐዋርያው እንደ ተገናኘን ከየት መጣህ ? ከየትኛው አህጉር ነበርህ ? አላለኝም ። ሰዎችን በክርስቶስ እንጂ በአገርና በቋንቋቸው ለማወቅ የማይፈልግ ነበረ ። ሰማይ ያለ እንደ ምድራውያን ከቀይና ከነጭ አፈር ፣ ከጥቁርና ከቢጫ አፈር እያለ ጭቃ አያማርጥም ። አፈርም አፈር ነው ፣ ደምም ቀይ ነው ። ሐዋርያው የዘመን እላቂ እንደደረሰብን ነገረኝ ። “ያን ጊዜም ዘመኑ ደርሶአል ይባል ነበረ ። ዛሬም ከሁለት ሺህ ዓመት በኋላ ዘመኑ ደርሶአል ይባላል” አልኩት ። እርሱም፡- “ዘመኑ የሚደርሰው ለሰሚው ሰው ነው ። ፈጥኖ ንስሐ ካልገባ ዘመን ኪሣራና ዕዳ ይሆንበታል” አለኝ ። እኔም ሐዋርያውን፡- “ያመኑ እየካዱ ፣ የሰበኩ እየፈሩ ፣ ጠንካሮች የነበሩ በገዛ ደቀ መዛሙርቶቻቸው እየተሰናከሉ ምድረ በዳ እየቀሩ ነው” አልኩት ። እርሱም ባለመደነቅ፡- “ሙሴ ምድረ በዳ የቀረው ከነዓን ሊያስገባው ባስወጣው ሕዝብ ነውና አትደነቅ” አለኝ ። ደግሞም፡- “ዴማስን ጥዬ ጢሞቴዎስን አንጠልጥዬ ገነት እንደ ገባሁ አትዘንጋ ፣ እግዚአብሔር የጻፈልህ ላይ ደርበህ መጻፍ ያንተ ድርሻ ነው ፤ እግዚአብሔር በማጽደቁ ብቻ ሳይሆን ነጻ ፈቃድ በመስጠቱም ፍቅር መሆኑን ይገልጣል” አለኝ ። በመቀጠልም፡- “ሳይህ ፖለቲካው ፣ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደሩ ፣ የወንድሞች ፍቅር ማጣት ፣ የአብያተ ክርስቲያናት ሁከት እየረበሸህ ነው ፣ ከተረበሽህ ሥራ መሥራት አትችልምና በመረጋጋት ቁም ። ለምን እንዲህ ሆነ ? ከማለት የሚሆነው መሆን ስላለበት መሆኑን ተረዳ” አለኝ ። እግዚአብሔር ትልቅ አምላክ በመሆኑ ለሁሉም ግራ መጋባቶች ዝርዝር መልስ አይሰጥም ። ሰማይ ስትደርስ ያልተመለሱልህን ጥያቄዎች አትጠይቅም ። የበጉን ፊት ስታየው ጥያቄህ እንደ ጢስ ይበናል” አለኝ ። 

ሐዋርያው ጳውሎስ ዕድገቱንና ትምህርቱን እንዲነግረኝ ፈለግሁ ። እርሱም፡- “ሰው ይታነጽበት ዘንድ አገልጋዮች ልምዳቸውንና ታሪካቸውን መናገራቸው መልካም ነው ። አሁን በምድር ላይ እያዳበራችሁት ያለው ግንኙነት ከምእመናን ጋር ድብብቆሽ የምትጫወቱ ይመስላል ። ያለ አቅማችሁ መልአክ የሚያደርጉአችሁና ያለ ግብራቸው ደግሞ ሰይጣን የሚያደርጉአችሁ ምእመናን እንደ ተፈጠሩ እናውቃለን ፤ የዚህ ትልቅ ችግር የእውቀት ማነስ ነው ። ምእመናን አገልጋይ ሰው መሆኑን ማወቅና መማር አለባቸው ። ነቢዩ ዳዊት ወደቀ ተብሎ የተጻፈው ለሐሜት ሳይሆን እኔም ብወድቅ እነሣለሁ ለሚል እምነት ነው” አለኝ ። ሐዋርያው የልጅነት ዘመኑን ሊተርክልኝ ተሰናዳ ። ያለ ማስታወሻ የሚናገረውን ሁሉ እይዝ ነበር ። ዝንጋዔ ያለው በምድር ላይ ነውና ። 

ይቀጥላል 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታሕሣሥ 21 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም