መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት/4

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት/4

 

የጠርሴሱ ጳውሎስን በአካለ ነፍስ በማግኘቴ ትልቅ ደስታ ተሰምቶኛል ። ነፍስ አካል አላት ። ነፍስ በዚህ ዓለም ላይ በሥጋ ገዝፋ ትታያለች ። በባሕርይዋ ረሀብ የሌለባት ብትሆንም ከሥጋ ጋር ተዋሕዳለችና የሥጋን ረሀብ የራስዋ አድርጋ ራበኝ ትላለች ። ሥጋ በነፍስ የማትሞት ፣ ነፍስም በሥጋ የምትሞት ናት ። ተዋሕዶ የሚሞተውን የማይሞት ፣ የማይሞተውን የሚሞት ያደርገዋል ። ሁሉም በአገሩ ያስተናግዳል ። ሥጋ አገሩ ምድር ላይ ነው ። የመጀመሪያው ሰው አዳምም የስሙ ትርጓሜ አፈር ወይም መሬት ማለት ነው ። ሥጋ ነፍስን በዚህች ዓለም ታስተናግዳለች ። የሥጋ ታቦት ወይም ማደሪያ ትሆናለች ። ቤቱ ሲፈርስ ሰውዬው እንዲወጣ ሥጋ ሲፈርስም አዳሪዋ ነፍስ ትወጣለች ። ነፍስም በአካልዋ ፍጹምነት ዛሬ በገነት ፣ ነገ በመንግሥተ ሰማያት ትኖራለች ። ረቂቃን አካላት ብለን የምንጠራቸው ራሱ እግዚአብሔር ፣ ቅዱሳን መላእክትና ነፍስ ናቸው ። የእግዚአብሔር መንፈስነት በቦታና በጊዜ የማይወሰን ነው ። የመላእክት መንፈስነት ተፈጥሮአቸውን የሚገልጥ ፣ ረቂቃን ወይም መናፍስት የሚያሰኛቸው ነው ። የነፍስ መንፈስነት በሚታይ ሥጋ ውስጥ የማይታይ ህልውና መሆንዋን ነው ። ነፍስ አካል ያላት ስትሆን በራስዋ ለመኖር ትችላለች ። በዚህ ዓለም ግን ያለ ሥጋ ደግ አልሠራችምና ፣ ነፍስ ብትራራ የሰጠችው በሥጋ እጅ ነውና ሥጋም አብሮ ሊከብር ትንሣኤ ሙታንን ይጠብቃል ። 

በአካለ ነፍስ ያሉ ቅዱሳን ብርሃን የለበሱ ናቸው ። የነፍስን ውበት መግለጥ አይቻልም ። እንኳን የነፍስን ውበት ለነፍስ የተዘጋጀውን የመንግሥተ ሰማያትን ውበት መግለጥ አይቻልም ። በገነት የአንዱ ክብር ካንዱ ክብር ይበልጣል ። የዛሬው ሞኝና ላይ ላዩን የሚሄድ ክርስቲያን ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እኩል ክብር የሚያገኝ ይመስለዋል ። የድንግል ማርያም ክብርም ከፍጥረታት ሁሉ የከበረ ነው ። በአንድ ገነት ውስጥ የተለያዩ ክብሮች አሉ ። ይህ ክብር እንደ ሥራ መጠን የሚሰጥ ነው ። ሐዋርያው ጳውሎስ፡- “የፀሐይ ክብር አንድ ነው የጨረቃም ክብር ሌላ ነው የከዋክብትም ክብር ሌላ ነው፤ በክብር አንዱ ኮከብ ከሌላው ኮከብ ይለያልና” ይላል /1ቆሮ. 15፡41 /። 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በክብር ስሙ ጠራሁት ። በሰማይ ውርደት ሳይሆን ክብር ብቻ ነው ያለው ። እግዚአብሔር እንኳ ጥፋት የተቀጠረባትን ከተማ ነነዌን፡- “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ” ብሏል ። ዮና. 1፡2 ። እግዚአብሔር ከተማን እንኳ ታላቂቱ ይላል ። እግዚአብሔር አክባሪ ነው ። የእግዚአብሔር መንፈስ ባለበት ሁሉ ክብር አለ ። በአንድ ስፍራ ላይ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዳለ ምልክቱ ክብር ሲኖር ነው ። አባቶች እንደ አባቶች ፣ ወንድሞች እንደ ወንድሞች ፣ እኅቶች እንደ እኅቶች ሲከበሩ በዚያ ቦታ መንፈሰ እግዚአብሔር አለ ማለት ነው ። ሐዋርያው አልኩት ። ሐዋርያ ሖረ ከሚል ግስ የወጣ ሲሆን ሂያጅ ገስጋሽ ፣ የንጉሥ መልእክተኛ ማለት ነው ። ቅዱስ አልኩት ቅዱስ ማለት ልዩ ማለት ሲሆን ዘመኑን ለእግዚአብሔር የለየ ሰው ነውና ደግሞም ከተቀደሱ መርከስ በሌለባት ሰማይ ነውና ቅዱስ አልኩት ። ሐዋርያውም በፍቅር ዓይን እየተመለከተኝ ነበር ። ቅዱሳን ሰውን የሚወዱት ዓላማቸውን ሳይረሱ ነው ። በምድር ላይ ያለን እኛ ግን ለሰው ፍቅር ብለን ዓላማችንን እንረሳለን ። ቤተሰቤ እንዳያዝን ብለን ክርስትናን ፣ ወላጆቼ ተስፋ እንዳይቆርጡብኝ ብለን ምናኔን እንተዋለን ። እግዚአብሔርን ከሁሉ አስተካክለን ሳይሆን አብልጠን መውደድ አልቻልንም ። 

ሐዋርያው ንግግሩን ቀጠለ ። ቤተሰቦቼ በጠርሴስ ቢወልዱኝም የሃይማኖትን ትምህርት እንድማር ገና በሰባት ዓመቴ ወደ ኢየሩሳሌም ወስደውኝ እኅቴ ዘንድ አስቀምጠው ፣ ከገማልያል እግር አጠገብ እንድማር አደረጉኝ ። ሰባት ዓመት የዕድሜ አንድ እርከን ነው ። ልጆች የልጅነት የደስታ ጊዜያቸውን በቅጡ አሳልፈው በሰባት ዓመት ወደ ትምህርት ቢመጡ የተሻለ ቁመና ይኖራቸዋል ። አንድ አይሁዳዊ ሕፃን በሰባት ዓመቱ ከመምህር ዘንድ ተሰጥቶ መጀመሪያ የዕብራይስጥ ፊደልንና የብሉይ ኪዳን ንባብን እስከ አሥራ ሁለት ዓመቱ ይማራል ። አሥራ ሁለት ዓመት ለአይሁዳውያን የአካለ መጠን ዘመን ስለሆነ ልጁ ወደ ተግባረ ሥጋ ለመሄድ አሊያም መንፈሳዊውን ትምህርት ለማጠናከር ምርጫ ያደርጋል ። ምርጫው መንፈሳዊውን ትምህርት መማር ከሆነ በንባብ የዘለቀውን ብሉይ ኪዳን በትርጓሜ እስከ ሃያ ዓመቱ ድረስ ይማራል ። እኔም ከሰባት ዓመቴ የጀመርኩትን ትምህርት በሃያ ዓመቴ ፈጸምሁ ። ቋንቋን በቀላሉ ለማወቅ እስከ ሰባት ዓመት ያለው ዕድሜ ወሳኝ ነው ። እስከ ሰባት ዓመት ከአራት ቋንቋ በላይ ማወቅ ይቻላልና ወላጆች ለልጆቻቸው ቋንቋን ቢያስተምሩ መልካም ነው ። እኔም እስከ ሰባት ዓመቴ የዕብራይስጥን ፣ የግሪክንና የሮማይስጥን ቋንቋ አውቅ ነበረ ። 

ሐዋርያው አሁን ቀጠለ፡- የተማርኩት በታወቀው በገማልያል እግር ሥር ቁጭ ብዬ ነው ። ገማልያል በትክክል ያወቀ ፣ በታሪክና በዛሬው ሁነት መካከል ያለው ትስስር የለየ ፣ የሚሆነው ሲሆን የነበረ ነው ብሎ የሚያምን ፣ ከእግዚአብሔር የሆነውን ማንም እንደማያጠፋው ፣ ከእግዚአብሔር ያልሆነው ደግሞ ሰው ሁሉ እየወደደው በራሱ እንደሚጠፋ የሚያምን መምህር ነበር ። ከመምህር የሚወሰድ እውቀት እርግጠኝነት አለው ። ከመምህር መማር የማይፈልጉ የተለያዩ ችግሮች ይገጥሟዋል ። የመጀመሪያው ሐረገ ትውልዱን ይስታሉ ። አበው ለነቢያት ፣ ነቢያት ለሐዋርያት ፣ ሐዋርያት ለሊቃውንት ፣ ሊቃውንት ለመነኮሳትና ለጳጳሳት እያቀበሉ መንፈሳዊ ውርስ ተላልፏል ። ከመምህር የማይማር ይህን ሐረገ ትውልድ ስለማያገኝ የተገነጠለ ቅርንጫፍ ይሆናል ። ለጊዜው ቢለመልምም ቆይቶ ግን ይደርቃል ። ሁለተኛው ችግር ራስን መውለድ ብርቱ ድካም አለው ። አባት ያለው የሚያምጥለት አለው ። አባት የሌለው ግን ራሱ አምጦ ራሱን የሚወልድ ነውና በከንቱ ጉልበቱን ይጨርሳል ። ሦስተኛ የኑሮ ልምድ አይኖረውም ። መምህራን በቃላቸው ብቻ ሳይሆን በኑሮአቸውም ያስተምራሉ ። ደቀ መዝሙሩም መምህሩ ለተጠየቁት ጥያቄ ፣ ለደረሰባቸው ፈተና የሰጡትን መልስ እያየ ይማራል ። የሕይወት እውቀት ዕድሜና እውነት ካስተማራቸው የሚገኝ ነው ። በቤተሰብ ሕግ ታናሹ የአንድ ዓመት ታላቁን ያከብራል ። በመንፈሳዊ ዓለምም እኛን በማመን የቀደሙንን ማክበር ይገባል ። መምህራን በማመን የቀደሙን ፣ እኛ በንባብ የምንጮኸውን እነርሱ በትርጓሜና በሕይወት የሚያውቁት ናቸው ። አራተኛ ከመምህራን አለመማር ያልተጣራ እውቀት ለመያዝ ይዳርጋል ። አምስተኛ እርግጠኛነት ኖሮት ለማስተማር ይቸገራል ። ያልተማረ ያለው ሀብት ድፍረት ቢሆንም እምነት ግን የሚገኘው በቅጡ በትሕትና ከመማር ነው ። ከመምህር እግር ሥር ቁጭ ብሎ መማርን ሰማይ ያከብረዋል ። 

ከመምህር እግር ሥር ቁጭ ብሎ መማር ማለት በትሕትና በታዛዥነት ዘመንን በመስጠት መማር ነው ። ደቀ መዝሙር ማለት ተመላላሽ ተማሪ ሳይሆን አዳሪ ተማሪ ነው ። ማቄን ጨርቄን የማይሉ ደቀ መዛሙርት ካልተገኙ ፣ ዘመናቸውን በሙሉነት ለክርስቶስ የሰጡ ካልመጡ ወንጌል ጉዞ አይሮጥም ። በዱላ ቅብብሎሽ የመጨረሻ ሯ ፈጣን መሆን አለበት ። እናንተም የመጨረሻ ዘመን ሯጮች ናችሁና መፍጠን አለባችሁ” አለኝ ። በሐዋርያው ንግግር ወደ ታላቅ ተመስጦ ገባሁ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታኅሣሥ 27 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም