መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /7/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /7/

 

እንኳን ለ2013 ዓ.ም. ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የጥምቀት በዓል በሰላም አደረሳችሁ !

ቅዱሳን በምድር ትዕግሥትን ያፈራሉ ፣ በሰማይ ደግሞ የትዕግሥትን ዋጋ ያገኛሉ  ። ትዕግሥት የሚያስፈልገው በምድር ነው ። ከአሁኑ የተሻለ ነገር ይጠብቀኛል ብሎ ተስፋ ማድረግ እርሱ ትዕግሥት ነው ። ትዕግሥት በፍቅር ላይ ተመሥርቶ በተስፋ ላይ ድምድማቱን ይሠራል ። መምህር ተማሪውን እስኪገባው ድረስ መታገሥ አለበት ። ለዓለም ታላላቅ ነገር ያበረከቱ ሁሉ ትምህርት አልገባ ብሎአቸው የተሰደዱ ሰዎች ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ትምህርቱን አልቻሉትም ሳይሆን ትምህርት ቤቱ እነርሱን አልቻላቸውም ማለት ይቀላል ። ብዙ ቅዱሳንም ትምህርት እንቢ ብሎአቸው ኋላ ግን የሰማይ መስኮት ተከፍቶላቸው ረክተው ምድርን አርክተዋል ። ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ ዜማ የተገለጠለት ፣ ብሉይና ሐዲስን ያመሰጠረ ፣ ቅኔን ያበረከተ ትልቅ መምህር ነው ። ቅዱስ ያሬድ ግን ትምህርት እንቢ ብሎት አዝኖ የተሰደደ ፣ እንደገና ተስፋ አድርጎ የተቀመጠና የእግዚአብሔርን ጸጋ ያገኘ ኢትዮጵያዊው ነቢዩ ዳዊት ነው ። መምህራን ተማሪዎቻቸውን በትዕግሥት ማስተማር ይገባቸዋል ። የትዕግሥት ቅጠሉ መራራ ፣ ፍሬው ግን ጣፋጭ ነው ። በሥጋ የሚወልዱ ያምጣሉ ፣ በነፍስ የሚወልዱ በአእምሮ የሚያሳድጉ የበለጠ ሊያምጡ ይገባቸዋል ። ተማሪዎችም ዛሬ አልገባ ያላቸው እውቀት ነገ ላይ በቀላሉ እንደሚይዙት ፣ እውቀት ከዕድሜም ጋር ተናባቢ መሆኑን ማወቅ አለባቸው ። በሰባት ዓመታችን የተማርነውን በሃያ ዓመታችን ብንማረው የዓመቱን በወር እንፈጽመው ነበር ። የልጆች የጨዋታ ዘመናቸው ተከብሮ ቀለል ያለ ትምህርት ቢሰጥ ፣ ጠንካራውን ከፍ ባለ ዕድሜ ቢሰጥ መልካም ነበር ። ለትምህርትም የሚያልፍ ጊዜ የለም ። 

ምድር ዱላ ያለባት ትምህርት ቤት ናት ። በልጅነት በሰበዝ ሀሁ እንላለን ፣ ስናድግ ደግሞ በብረት በትር እየተመታን የሕይወትን ሆሄ እንቆጥራለን ። በልጅነት ሰበዙ የሚነካው ፊደሉን ነበር ፣ በጎልማሳነት ግን ብረቱ የሚነካው እኛን ነው ። ፊደል እየነካን ተምረን ኋላ ደግሞ መከራው እየነካን  እንማራለን ። ሐዋርያው ጳውሎስ በትዕግሥት ጠበቀኝ ። በጆሮ የሰማሁትን በልቤ እስክሰማው ድረስ ታገሠኝ ። በመታገሡ መጠበቅ ነበረበት ። መታገሥ መጠበቅ ነው ። ሰውን በቃል ብቻ ማስተማር ከባድ ነው  ። የመምህራን አቅም በቃል ማስተማር ነው ። እግዚአብሔር ግን በሕይወት ውስጥ እያሳለፈ ያስተምራል ። መምህራን በሕይወት ውስጥ ፣ በጉዳትም በስብራትም እንደሚማሩ በማወቅ ደቀ መዛሙርቶቻቸውን መጠበቅ ወይም መታገሥ አለባቸው ። መታገሥ ተስፋ ማድረግ ነው ፣ እኔም ለዚህ የእውቀት ብርሃን እንደበቃሁ እርሱም ይበቃል ብሎ በሌላው ላይ ተስፋ አለመቁረጥ የመምህርነት መገለጫ ነው ። ልጅ ያልነበረ አባት ፣ ደቀ መዝሙር ያልነበረ መምህር የለምና ያሳለፍነውን እያሰብን የሚያልፉትን ተማሪዎች መታገሥ ይገባል ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በትዕግሥት ጠበቀኝ ። እስኪገባኝ ብቻ ሳይሆን እውነቱ ውስጤን እስኪቆጣጠረው ድረስ ታገሠኝ ።

 

እኔም ሐዋርያው ጳውሎስን ቀናተኛ ፈሪሳዊ ሆኖ ቤተ ክርስቲያንን ስለማሳደዱ ጠየቅሁት ። ሐዋርያው ጳውሎስም እንዲህ አለ፡- “ለእግዚአብሔር ብቀና እግዚአብሔር የሚወደውን ሰው አልጠላም ነበር ፣ የእኔ ቡድን ለምለው መቅናቴ ግን እግዚአብሔር የሚወደውን ሰው እንድጠላ አደረገኝ ። የቅንዓቱ እሳት ውስጤ ሲትጎለጎል ከእኔ አስተሳሰብ ውጭ ያሉት መጥፋት አለባቸው ብዬ እንዳምን አደረገኝ ።  ዓለም የጋራ ቤት መሆንዋን ረስቼ ፣ ሁሉ እንደ እኔ ካላሰበ የሚል አዙሪት ውስጥ ገባሁ ። አዙሪት የያዘው ሰው ሁሉም ነገር ይዞርብኛል ይላል ፣ ነገሮች ግን ባሉበት አሉ ፣ የእርሱ አእምሮ ግን ስፍራውን ለቋል ። ስለዚህ ከቆመ ነገር ጋር ይጋጫል ። ክርስትናው እኛን በመንቀፍ አልጀመረም ፣ ፈሪሳዊ ቅንዓቴ ግን ክርስትናውን በመጥላት ጀመረ ። ተነጋግሮ ለመግባባት እውቀት ቢኖረኝም አቅም ግን አልነበረኝም ። ከማይነጋገር ምሁር የሚነጋገር መሃይም በደህና ይኖራል ። ለዚህ ነው በገጠሩ በሽማግሌ ሲታረቁ በከተማው ግን በመጽሐፍ ቅዱስም አይታረቁም ። ጠብ በምሁራን ከገነነ መማር አለመማር ሆነ ። በቃል የማይነጋገር በድንጋይ መነጋገር ይጀምራል ። የሚናገር አምላክ የሚነጋገሩ የሰው ልጆችን ፈጠረ ። የሰው ልጆች የሚናገር አንደበት ይዘው ካልተነጋገሩ ተፈጥሮ ይባክናል ። ባለመነጋገር አእምሮ ሥራ ይፈታል ። አእምሮ ሥራ ሲፈታ እየዛገ ይመጣል ። የመርሳት በሽታ ይመጣል ። ባለመነጋገር የአፍ ጠረን እየተበላሸ ይመጣል ። ባለመነጋገር በግምት መጥፋት ይጀመራል ። “ይህን ጊዜ እንዲህ እያሰበ ነው የቀረው” በማለት አደጋ ደርሶበት የቀረውን ሰው “የአልኮል መጠጥ ሲጠጣ ነው የቀረው” ለሚል ግምት አሳልፎ ይሰጣል ። ባለመነጋገር ሰው ሁሉ የመሰለውን እያዳመጠ እውነትን ገሸሽ ብሎ ከወንድሙ ጋር ይጣላል ። ባለመነጋገር እየተፋቀሩ ሰዎች ይጣላሉ ። ባለመነጋገር ትንሹ ችግር አድጎ ቤት ያፈርሳል ። ባለመነጋገር የአገር መሠረቱ ይናዳል ። ባለመነጋገር ሰው ሁሉ የተፈበረከ ውሸትን ያምናል ። ባለመነጋገር በቆዳው ቀለም እገሌ እንዲህ ነው ብሎ ብይን መስጠት ይጀምራል ። 

የሰው ልጆች መነጋገርን የሚጠሉት ትንሽ ጉዳይ ትልቅ ጠብ ትወልዳለችና ከተነጋገሩ የምክንያቱ ትንሽነት ስለሚያስገምታቸው ነው ። የሰው ልጆች መነጋገርን የሚጠሉት ተሳስቻለሁ ለማለት ባለመፈለግና ካፈርሁ አይመልሰኝ ለሚል ድርቅና ታማኝ ለመሆን ነው ። መነጋገርን መጥላት በቂ እውቀት የለኝም ብሎ መረታትን መፍራት ነው ። መነጋገርን መጥላት ለፍቅር ያለን ዋጋ አናሳ መሆን ነው ። መነጋገርን መጥላት ለትውልድ አለማሰብ ነው ። መነጋገርን መጥላት ሐሜትንና ለዚያ ሰው ያለንን ሐሰተኛ ግምት ማመን ነው ። እባካችሁ ተነጋገሩ ። ካልተነጋገራችሁ እንደ እኔ ነፍሰ ገዳይ ትሆናላችሁ ። ያውም ቅዱሱን እስጢፋኖስን ታስወግራላችሁ” አለኝ ። 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ታላቅ ግለት ውስጥ ሲገባ የእኔም መንፈስ ማተኮስ ጀመረ ። የነቃ ያነቃል ፣ የጋለ ያግላል ። እውቀቴ ፣ ስሜቴ ሳይሆን እምነቴ ተቀጣጠለ ። እውቀቴ ሲግል የትምህርት ምስክር ወረቀት ለመሰብሰብ ይፈልጋል ። ስሜቴ ሲግል አሁን ዓለምን ካልያዝሁ ይላል ። እምነቴ ሲግል እግዚአብሔር ይታየኛል ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የአሳዳጅነት ዘመኑን መተረክ ቀጠለ፡-

“ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነኝ ያንን ወጣት እስጢፋኖስን ማስገደሌ ነው ። እስጢፋኖስ ለትንሽ ተግባር ተሹሞ ለትልቅ ክብር የበቃ ነው ። ለማዕድ ማስተላለፍ ተሹሞ ለወንጌል ምስክርነት የደረሰ ፣ ሐዋርያትን እንዲራዳ ተጠርቶ ከሐዋርያት ቀድሞ ሰማዕት የሆነ ነው ። እስጢፋኖስ ማለት አክሊል ማለት ነው ። ስምን መልአክ ያወጣዋል ትሉ የለ ። እስጢፋኖስ እንደ ስሙ የሰማዕትነትን አክሊል አገኘ ። ቀዳሜ ሰማዕት ሆነ ። እርሱ ሰማዕት በሆነባት ቀን እኔ ግን ነፍሰ ገዳይ ሆንኩኝ ። አንዷን ቀን አንዱ ሰማዕት አንዱ ገዳይ ፣ አንዱ ጻድቅ አንዱ ርኵስ ሲሆኑባት ይውላሉ ። እኔን የለወጠኝ ጸጸቱ አልነበረም ፣ ልቤ እየደነደነ ስለነበር ሌላም መግደል ያምረኝ ነበር ። የለወጠኝ የእስጢፋኖስ የይቅርታ ጸሎት ነበር ። እስጢፋኖስ ክርስቶስን መሰለ ። የእስጢፋኖስ የይቅርታ ጸሎትም የልቤን ደጃፍ አንኳኳ ። ተቃዋሚዎችን የክፋት ምላሽ የበለጠ ሲያደነድናቸው የፍቅር ምላሽ ግን ይሰብራቸዋል ። በዓለም ላይ መጥላት ቀላል ሲሆን ጠላትን መውደድ ግን ከባድ ነው ። ለጠላቶች መማለድ የሚጠቅመው የተበዳይን ልብ ከቂምና ከመሰበር ስለሚጠብቅ ፣ ተቃዋሚዎችም የሚመለሱበትን ጸጋ ስለሚልክላቸው ነው ። በእስጢፋኖስ ላይ ካወረድሁት ድንጋይ እርሱ የወረወረው የፍቅር ቃል የበለጠ አሸነፈኝ ። እስጢፋኖስ በሥጋ ሞተ ፣ እኔን ግን ልበ ሙሉ እንዳልሆን አደረገኝ ። ከዚያ በኋላ ፈቃድ ተቀብዬ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ብወጣም ልበ ሙሉ ግን አልሆንሁም ። ከዚያ ሁሉ በላይ እስጢፋኖስ ቤተሰቡን ያሳመነ ስለነበር የልጃቸው ገዳይ ብሆንም በእኔ እጅ መጠመቅ ፈለጉ ። እኔም ካጠመቅሁት ሁሉ የእስጢፋኖስን ቤተሰብ በማጥመቄ ትልቅ ዕረፍት ይሰማኛል ። ክርስቶስ ደም ለተቃቡትም ፍቅር ይሰጣል ። ብዙ የይቅርታ ታሪኮች አሉ ። እስጢፋኖስ የድንጋዩ ናዳ ከአናቱ ላይ ሳይበርድ የሰጠው ይቅርታ ፣ የእስጢፋኖስ ቤተሰብም የልጃቸው ገዳይ ሳለሁ በጳውሎስ እጅ ነው የምንጠመቀው ብለው ግድ ማለታቸው ከሁሉ የሚልቅ የይቅርታ ታሪክ ነው  ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ማጥፋት ሲችል መሞቱ ከሁሉ በላይ ያሳዝነኛል ። 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የጌታውን ፍቅር አስቦ ልቡ ሲነካ እኔም ኀዘኑ እንዳይቀጥል ላረጋጋው ፈለግሁ ። እኔ እንኳን ለወገሩኝ ክፉ አስበውብኛል ብዬ ስንቱን መቀየሜን አስታወስኩና ልቡና ስጠኝ አልኩኝ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥር 11 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም