መግቢያ » ትረካ » ጴጥሮስን አገኘሁት » ጴጥሮስን አገኘሁት

የትምህርቱ ርዕስ | ጴጥሮስን አገኘሁት

 

/ክፍል 1/

ሰው መሞቻው ሲቃረብ መቀበሪያ አገሩን መራቅ አይፈልግም ። የኢየሩሳሌም ሐዋርያ ሁኖ ኑሮ አሁን ደግሞ የሮም ሰማዕት ለመሆን ፈልጓል ። ሐዋርያው ጴጥሮስ ወደ ሮም እንደ መጣ ሰማሁ ። ወደ ሮም የሚመጡ የዓለምን ትልቅ ከተማና ንጉሠ ነገሥቱ ያለበትን ውብ መንደር ለማየት ነው ። ለኑሮው የተጠየፋትን ሮምን ለሞቱ ሲመርጣት ፣ ተሸሽጎ ኑሮ ፣ በኢየሩሳሌም ገጠር ተጥሎ በደማቅ ከተማ ሊሠዋ መከጀሉ እጅግ ገረመኝ ። ጌታ ሲጠራው 58 ዓመቱ ገደማ እንደነበር ባለፈው ያገኘሁት ጳውሎስ ነገረኝ ። አሁን ደግሞ ከጥሪው እስከ አገልግሎቱ 37 ዓመት ይሆነዋል ። እንደምገምተው ጴጥሮስ የ95 ዓመት አረጋዊ ነው ። አሟሟቴን አሳምርልኝ በሚባልበት ዕድሜ ቁልቁል ሊሰቀል መምጣቱ ገረመኝ ። ላገኘው ማሰስ ጀመርሁ ። ሀገረ ስብከቱን ለቆ እንዴት መጣ ስል ኢየሩሳሌምም በአርበኞች ግንባር እንቅስቃሴ ከሮማውያን ጋር ብርቱ ጦርነት ውስጥ ናት ። ደግሞም ለንጉሠ ነገሥቱ ሳይመሰክር ሞት እንዳይቀድመው ሰግቷል ። ኔሮን ቄሣር ጠባዩ ተለውጦ ለስህተቱ ክርስቲያኖችን ተጠያቂ ማድረግ የጀመረው በ64 ዓ.ም. ጀምሮ ነው ። በዚህ የቍጣና የስደት ጊዜ መምጣቱ ገረመኝ ። በኢየሩሳሌምም ሁከት ፣ በሮምም ጭንቀት ነበረ ። ሮም ተጨማሪ ቤተ መንግሥት ለመሥራት ከተማ አቃጥላ ክርስቲያኖች ላይ በማሳበብ ጭፍጨፋ ታካሂዳለች ። ኢየሩሳሌም ደግሞ ነጻነት ወይስ ሞት ብላ ትፋለማለች ። በሁሉም ቤትና አገር እሳት አለ ።

ባሻገር ሳይ ሐዋርያው ጴጥሮስን አየሁት ፤ በዚያ ዕድሜው እየተጣደፈ ሲሄድ ጎበዝ አይቀድመውም ። እኔም አጠገቡ ያለውን ሰው እየመከረው ነውና ላደናቅፈው አልፈለግሁም ። እርሱ ግን እንዲህ እያለ ሲናገር ጆሮዬን ጥዬ እየሰማሁ ከኋላቸው ክው ክው እል ነበር ። 

“ልቤ እንደ ባሕሩ ይዋልላል ። ቢጸና ብዬ ብመኝም በሚበልጥ ማዕበል ይናጣል ። የቆምሁበት መሠረት ሲናወጥ ፣ የማየው ሰማይ በደመና ፣ ዙሪያዬ በጉም ይጋረዳል ። ታንኳዬን ሠውቼ ራሴን ለማዳን ብዙ ጥረት አድርጌአለሁ ። ንብረት ስለ ሰው እንጂ ሰው ስለ ንብረት አልተፈጠረም ብዬ ያለኝን ሁሉ ለሰላሜ ስል ከፍያለሁ ። ለማግኘት ማግኘት ብቻ ሳይሆን ሰላምን ለማግኘት ገንዘብን መጣል አስፈላጊ እንደሆነ ተረድቻለሁ ። ከጠፋው ጥሪት ጋር ከጠፋሁ ፣ ከተወረሰው ርስት ጋር ካልተቀበርሁ ካልሁ እኔ እኔ መሆኔ ይቀራል ። ያምናው ማዕበል ዘንድሮ ፣ ያለፈው ወጀብ ዛሬ ይመጣል ። ማዕበል ያው ማዕበል ነው ። ሁከት ነውና ሰላም መሆን አይችልም ። ባሕርዩና ሥሪቱ አይፈቅድለትም ። በለውጥ ሕግ የምመራ እኔ ግን ያው ሆኜ መጠበቅ አይገባኝም ። ካለፈው ዓመት ይልቅ የዘንድሮ ፈተና ለተማሪው ይከብደዋል ። ያው ፈተና ከመጣ ተማሪው ክፍሉን አልለወጠም ። ሌላ ፈተና ከመጣ ግን ደረጃው አድጓል ማለት ነው ። ማዕበል ከባሕሩ ዳርቻ ላለ ሰው መዝናኛው ነው ። መጣሁ ሄድሁ ሲል እንደ ባሕል ጭፈራ እንደ ሕብረት ውዝዋዜ የሚያስገርም ነው ። ባሕሩ መሐል ላለ ግን ማዕበሉ አስጨናቂ ነው ። ዳር ሆነው የሚታዘቡ ፣ በሰው ቍስል እንጨት የሚሰድዱ አመስግን ፣ ለመከራ እጅ አትስጥ ፣ ደግሞም ስምህ ካልጠፋ የእግዚአብሔርን ስም ማክበር አትችልም ይላሉ ። በዳርቻው ላይ ያለ ስለ ማዕበል ያመሰግናል ። ሳይሰለች የሚያጫውት ፣ ከፍ ዝቅ የሚል ፍልቅልቅ ሕፃን ነውና ። በባሕር መካከል ያለ ግን ከማዕበሉ አውጣኝ እያለ ይጸልያል ። ያስጨነቀኝ ማዕበል የምስጋና ርእስ ይሆንልኛል ። መሐል ላይ ያስለቀሰኝ ከሰማዩ ዳርቻ ላይ የዝማሬ ቅኔ ያስገኝልኛል ። 

በትዳር ዓለም ከገባሁ ቢያንስ አርባ ዓመት ይሆነኛል ። ክርስቶስን አላገኘሁትም ያለሁበት ድረስ መጥቶ ያገኘኝ እርሱ ነው ። እርሱ ሲያገኘኝ የአርባ ዓመት የትዳር እውቀቴ እርሱን ለማወቅ ተጨማሪ ጥበብ አልሆነልኝም ። ብርሃኑን ጌታ በብርሃን ቃሉ ማየት ግድ ይላል ። በፀሐይ ብርሃን ፣ በመቅረዝ ወጋገን እርሱ አይታይም ። እርሱ የሚታየው በቃሉ ብርሃን ነው ። ከብርሃን ጌታ የተገኘው ብርሃን ቃሉ ራሴን ያሳየኛል ። ልክ የሆነውን ማሳየት ብቻ ሳይሆን ውሳኔዬን እየተከተለ ልክ ያደርገኛል ። ልክ ስለሆኑ ነገሮች ብዙ እውቀት ያላቸው ልክ ያልሆኑ ሰዎች አሉ ። እግዚአብሔር በእኛ ላይ ያለው ዓላማ ልክ የሆኑ ነገሮችን የምናውቅ ሳይሆን ልክ የሆኑ ሰዎች ማድረግ ነው ።”

የሚናገረው ሁሉ ብርቱ ቃል ነው ። ከሽምግልና እውቀት ይልቅ የሰማይ ጥበብ ያለበት ነው ። የጁልየስ ቄሣር ጎዳና ላይ እንደደረስን የጳውሎስ ተማሪ የነበረችው ድንግላዊት ፌበንን አገኘናት ። እኔ ከኋላቸው እየተከተልሁ መሆኔን አላወቁም ። ጴጥሮስም በጉባዔ እንደ ተሰየመ ፣ አትሮኖንስ እንደ ጨበጠ ሁኖ ይናገር ነበር ። መንገደኛው ሁሉ ምን እያለ ነው  እያለ ዞር ብሎ አይቶ አይሁዳዊ መሆኑን ከአለባበሱ ተረድቶ ገላምጦት ያልፋል ። እኔም ከኋላቸው እንደ ጥላ እየተከተልሁ ፣ ስውር ደቀ መዝሙር ሆኜ እየተማርሁ ነበር ። ያቺ ፌበን በጎዳናቸው ትክክል መጣች ። የምትሄድበትን መንገድ ጥላ ከእነ ጴጥሮስ ጋር ተመለሰች ። ከእግዚአብሔር ሰው ጋር የማሳልፈው የማይደገም ዕድል ሊሆን ይችላል ። ሌላው ነገር ይደረስበታል ። ጽድቅ ቀዳሚ ሲሆን ጉዳይ ተከታይ ይሆናል ። ጉዳይ ሲቀድም ጽድቅ ይከተላል የሚል ስሜት ተቆጣጠረኝ ። ያች እማሆይ ፌበን ጴጥሮስን አንድ ጥያቄ ነበረኝ አለችው ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም ሊሰማት ጆሮውን ቀሰረ፡- “ጌታችን አንዳንድ ሰዎችን የገሠጸበት ቃል ስድብ አይመስልም ወይ” ብላ ጠየቀች ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም በሰፊው ሊመልስላት ጉሮሮውን ሞረደ፡- 

“ጌታችን ፈሪሳውያንንና መሪዎችን ይዘልፍ ነበረ ። እርሱ መደበኛ ትምህርትን ለደቀ መዛሙርት ሲሰጥ መደበኛ ያልሆኑ ትምህርቶችን አንድ ጊዜ ለሚያገኛቸውና ተግሣጽ ለሚያስፈልጋቸው ያስተላልፍ ነበር ። ብዙ ጊዜ ትምህርትን የማይማር የትምህርት ተቃዋሚ ነው ። እውቀት ብልጭ እንዳትል ዘብ የቆሙ ሰዎች አሉ ። አደንቁረው የሚገዙ ሕዝብ ሲማር አልገዛም ብሎ ያምጻል ስለሚሉ ትምህርትን አይወዱም ። ያልተማረ ሰው ቢጭኑበት አህያ ፣ ቢጋልቡት ፈረስ ነው ። በቅሎ አትወልድም የሚወልድም አትወድም ይባላል ። ፈሪሳውያንም አይማሩም ፣ የሚማርም አይወዱም ። ጌታም እንደዚህ ያሉትን ሰዎች ይገሥጽ ነበር ። ተግሣጽ በስህተቱ ለሚኮራና ለሚቀጥል የሚሰጥ የትምህርት ዓይነት ነው ። ተግሣጽና ዘለፋ አንዱ የማስተማሪያ ዘዴ ነው ። ተግሣጽ ረቂቅ ዱላ ፣ ሕሊናን የሚገርፍ ጅራፍ ነው ። በትምህርት ቤት ከተማርነው ትምህርት ይልቅ የተሳሳትነውና የተቀጣነውን አንረሳውም ። የአምናው ትምህርት ዘንድሮ ይረሳል ። በመከራ የተማርነው ግን በዓለት ላይ የተቀረጸ በመሆኑ አይጠፋም ። እግዚአብሔር በመከራ ውስጥ የሚያስተምረን ትምህርቱ እንዳይጠፋን ነው ። ተግሣጽም የቅጽበት መከራ ነው ። ትምህርቱም አይረሳም ። 

የጌታችን ትምህርት ተግሣጽም ማስጠንቀቂያም ያዘለ ነው ። እርሱ ያልተማሩትን ሲያስረዳቸው ተምረው የደነቆሩትን ግን ይገሥጻቸዋል ። ማስተማር በሰው ሕሊና ላይ ሥዕል መሳል ነው ፤ ሰሌዳውም ፣ ቡሩሹም ፣ ቀለሙም አይታይም ። ትምህርቶች ሥዕል ይበዛባቸዋል ። ከተራ ሰው ይልቅ ሠዓሊዎች ትምህርት ሲማሩ ይገባቸዋል ። በሕሊናቸው ማጠራቀሚያ የሚያቁሩት በምስል ነው ። ጌታችን የሰማይ ወፎችን እዩ እያለ ስለ ኑሮ ዋስትና ፣ አበቦችን እየዳሰሰ እንዴት እኖራለሁ  የሚል ፍርሃትን ይጥል ነበር ። ቀና ካሉ የሰማይ ወፎች ፣ ካማተሩ የመስክ አበቦች አሉና ትምህርቱ አይረሳም ። ፍጥረታት ደስታዎቻችን ብቻ ሳይሆን መማሪያዎቻችንም ናቸው ። መጽሐፍ ቅዱስ በሥዕል የተሞላ መጽሐፍ ነው ።

በተግሣጾች ውስጥ ስድብ የሚመስሉ ነገሮች ተስተውለው ከሆነ ትርጉማቸውን ማየት ያስፈልጋል ። ጌታችን የገሠጸው በአብዛኛው በኃላፊነት ላይ የነበሩትን ነው ። ሄሮድስን  ቀበሮ ብሎታል ። ቀበሮ ሲታይ ውሻ ይመስላል ። ነገር ግን አውሬ ነው ። ሄሮድስም ሲታይ የአይሁድን ሃይማኖት የተቀበለ ይመስላል ፣ ልቡ ግን አረማዊ ነው ። ሄሮድሳውያን የኤዶም ወይም የዔሣው ዘሮች ናቸው ። ዔሣው አደነተኛ የበረሃ ሰው ነበር ። ሄሮድሳውያን ወዲህ ቤተ መቅደስን አስፋፍተው ያድሳሉ ፣ ወዲህ ሕፃናትን ያርዳሉ ። ፍቅርን ያልመረጠ ፣ ታማኝነት የሌለው ነውና ቀበሮ መባሉ ገላጭ ነው ። እንደ ሰው ለመሆን የፈለጉ አራዊት ባይኖሩም እንደ አራዊት የሆኑ ሰዎች ግን ነበሩ ። ውሻ ሰውን መርጦ የቀረ የቀበሮ ዘመድ ነው ። ድመትም ሰውን መርጣ የቀረች የነብር ዘር ናት ። ሄሮድስ ግን ፍቅርን ያልመረጠ ቀበሮ ነው ። 

ጌታችን ፈሪሳውያንንም ገሥጾአል ። ታላቅ የሃይማኖት ቡድን አቋቁመው ፣ ሕዝቡን በመንፈሳዊ ተውኔታቸው ልቡን ሰልበው ፣ በላያቸው ቅዱሳን በውስጣቸው ቀማኞች የነበሩትን የሃይማኖት መሪዎችን መገሠጹ እውነት ነው ። ጌታችን ዕውር ፣ ደንቆሮ መሪዎች ብሏቸዋል ። አያስተውሉም ፣ ውስጣዊ እይታቸው የተንሸዋረረ ነውና ዕውር ያለው የውጭ ዓይናቸውን ሳይሆን አስተሳሰባቸውን ነው ። በርግጥም የሚበልጠውን የማያውቅ ፣ ከመቅደሱ ወርቁን ፣ ከሰጪው ስጦታውን የሚያስበልጥ ዕውር ነው ። እናውቃለን ፣ እንመራለን የሚሉት ዕውራን ናቸውና ዕውር መሪ የሚያደርሰው ወደ ገደል ነው ። ተግሣጹ ከጥፋታቸው አይበልጥም ። ደንቆሮ ማለቱም የማይሰሙና የመጨረሻ አዋቂዎች ነን ብለው ራሳቸውን በማስቀመጣቸው ነው ። የማወቅ ዕድሉን የማይጠቀምበት ደንቆሮ ነው ። ስለ እጅ ንጽሕና እየተጨነቁ ስለ ልብ ክፋት ግዴለሽ የሆኑትን ትንኝን የምታጠሩ ግመልን የምትውጡ ብሎ መገሠጹ እውነት ነው ። 

እናንተ ግብዞች እያለም ገሥጾአል ። ሌቦች እንዳይታወቁ ጭንብል ያጠልቃሉ ። ሁሉም ሌቦች ሳይሆኑ የሰለጠኑ ሌቦች ባለ ጭንብል ናቸው ። ሌብነቱን ይፈልጋሉ ፣ ሌባ መባልን ግን አይፈልጉም ። ፈሪሳውያን የነፍስ ሌቦች ነበሩ ። የገንዘብ ሌባን እየገሠጽን የነፍስ ሌባን ዝም ማለት አይገባም ። ፈሪሳውያን ላዩ ያማረውን የተለሰነ የመቃብር ድንጋይ እንደሚመስሉ ተናገረ ። የመቃብር ድንጋይ ውብ ነው ። የፍቅር መግለጫ አበባ አለበት ። የሃይማኖት ምልክት የሆነው መስቀልም ፣ የዳዊት ኮከብም ይቀመጥበታል ። የሕይወት ታሪክን ይዟል ። የቅዱስ መጽሐፍ ጥቅስም አለበት ። የሚወዱት ሰዎች ስም ዝርዝርም ተጽፎአል ። እርሱ ግን አበባውንም ፍቅሩንም ሊቀበል የማይችል ፍርስራሽ ሆኖ በውስጥ አለ ። ላዩን ያዩ ቢከፈት ግን አጽምን ማየት አይችሉም ። ግብዞችም እንዲሁ ናቸው ። አበባ ይሰጣቸዋል የሚወዳቸው ግን የለም ፤ የሕይወት ታሪካቸው ይነገርላቸዋል ፣ ሕይወት ግን የላቸውም ። ጥቅስ ተሸክመዋል ፣ እነርሱ ግን አያነቡትም ። እነዚህን መገሠጽ ለጌታችን ሥልጣኑ ነው ። የሰው ልጅ ያልጣመውን እውነት ስድብ ይለዋል ። 

አንድ ሐኪም ሲያክም በሰው ሰውኛ ክብርን ሽሮ ነው ። ዓይኑን ወደታች ከፍቶ ፣ አፍህን ክፈት ብሎ ፣ ምላስህን አውጣ ብሎ ፣ ልብስ አስወልቆ ፣ ባለቤቱ ብቻ የሚያገኘውን የአካል ክፍል ነክቶ ፣ ቆዳን በስለት ቆርጦ ያክማል ። ከእነዚህ ነገሮች አንዱም ከሐኪም ውጭ በሌላ ሰው ቢደረግ የመጋደል ርእስ ይሆናል ። ሐኪም ግን የሚያክመው ውርደት በሚመስል ነገር ነው ። ተግሣጽ ውርደት ቢመስልም ድኅነት ያለበት ነው ። 

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠውን ምላሽ ትክ ብላ የሰማችው የክንክራኦስዋ ፌበን በፊትዋ ታላቅ ደስታ ይነበብ ነበር ። ሰላምታ ሊሰጣት ቡራኬም ሊያክልበት ጀመረ ። ከሰላምታ በፊት እርስዋም ጥያቄዋን አስቀደመች ፣ ሐዋርያውም መልሱን አስቀደመ ። ፌበን ሆይ በ56 ዓ.ም . ገደማ የሮሜን መልእክት ይዘሽ እንደመጣሽ እዚሁ ቀረሽ ወይ ? ሲላት እኔም አብሬ ለመጠየቅ ተነሣሣሁ ። እንደምከተላቸው ግን ገና አላወቁምና ዝም አልሁ ። ትምህርት በመደበኛ ሰዓትና ቦታ ይሰጣል ። መደበኛ ባልሆነ ቦታና ሰዓትም ትምህርት ይኖራል ።  

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መጋቢት 25 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም