መግቢያ » ትረካ » ጴጥሮስን አገኘሁት » ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 10/

የትምህርቱ ርዕስ | ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 10/

 

ማለዳው ብሩህ መስሎ ታየኝ ። ማለዳው ብርሃን ሆኖ የሚታየው በሁለት ነገሮች ነው ። አንደኛው የምንሄድበት ሲኖረን ሁለተኛ የምንሄደው በረከተ እግዚአብሔር ያለበት ስፍራ ሲሆን ነው ። ትላንት ወደ ቤቴ ስሄድ ደስታ ኃይል ሰጥቶኝ ነበር ። ያለ ሰረገላ በምንጣፍ ላይ እንደሚጓዝ ያህል መንገዱ ምቹ ሆኖልኝ ነበር ። በግራ በቀኜም ብዙ ጠባቂዎች እንዳሉኝ እየተሰማኝ ልቤ ሙሉ ነበር ። የሮም አደጋ ጣዮችና ቀማኞችን እንደ ዛሬ ደፍሬ አላውቅም ። ክፉዎችን እኔ የማያቸው እነርሱ ግን የማያዩኝ መስሎ ይሰማኝ ነበር ። የእግዚአብሔርን ቃል ስንሰማ ከዋልን ቅዱሳን መላእክት በታላቅ ጥበቃ ወደ ማደሪያችን ያደርሱናል ። የሚታየውንና የማይታየውን ጠላት በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ተከልለን ማለፍ እንችላለን ። ደስታ የሚያስተኛ ይመስለኝ ነበር ። ደስታ ግን እንቅልፍ የሚሰጠውን አቅም ስለሚሰጥ ያነቃል ። ሰው በአምስት ነገሮች እንቅልፍ እንቢ ሊለው ይችላል ። የመጀመሪያው ሕመም ሲሰማው ፣ ሁለተኛው ሲርበው ፣ ሦስተኛ ነገር ሲገባው ፣ አራተኛ በጣም ሲደክመው ፣ አምስተኛ በጣም ደስ ሲለው ነው ። ደስታ እንቅልፌን አራቀው ። ልቤ እንደ እንቦሳ ይዘላል ። አፌ በዚያ ውድቅት ሌሊት እልል ሊል መዝጊያውን ይታገላል ። ክርስቲያን የጎረቤቱን ሰላምና ምቾት የሚጠብቅ በመሆኑ ስሜቴን ታገሥ እለዋለሁ ። ከእግዚአብሔር ሰዎች ጋር መዋል ብቻውን ያጽናናል ። እንደ እኔ የሚያምን ሰው መኖሩን ማየት በራሱ አቅም ይሰጣል ። የእግዚአብሔር ሰዎች ጋር የምንለዋወጠው ምስክርነት ለእምነታችን ጽናትን ይሰጣል ። እግዚአብሔር ያደረገልንን እንናገር ። የደከመው መንፈሳችን ይበረታታል ። የደከሙ ሰዎችንም ያነቃቃል ። ምስክርነቶች እምነትን ይጨምራሉ ። 

ሐዋርያው ጳውሎስ ተከራይቶት የነበረው ቤት ስደርስ በሩ እንደ ትላንቱ ክፍት ነበረ ። በውስጤም የአገልጋይ ቤት የእግዚአብሔር ደጅ ነውና አይዘጋም አልኩኝ ። ሐዋርያው ጳውሎስ ከሰው ገንዘብ መቀበል እየተሰቀቀ ድንኳን ሲሰፋ ፣ ከሰው ቤት መጠጋትን እንቢ እያለ ቤት ሲከራይ መኖሩ ገረመኝ ። እሰው ቤት የሄደና መሬት ላይ የወደቀ ሥጋ ጉድፍ ሳይዝ አይነሣም ይባላል ። ሁሉም ሰው የራሱ አመልና ገመና አለው ። የሚችለውም ቤቱ ነው ። ደጃፉን ለወጉ ጸፋሁና “ሰላም ለዚህ ቤት ይሁን” ብዬ ስገባ “የክርስቶስ ሰላም ከሁላችን ጋር ይሁን” በማለት ሐዋርያው ጳውሎስ መለሰልኝ ። እውነተኛ ምርቃት ነውና ሲያረሰርሰኝ ይሰማኝ ነበር ። ቅዱስ ጴጥሮስ ትላንት በተነጠፈለት ምንጣፍ መሬት ላይ ተኝቶ ነበር ። በልጅ ልጅ ተከብቦ ፣ በቤቱ ተከብሮ ፣ በሰፈሩ አረጋዊ ተብሎ ሰዋዊ ክብር ከሚያገኝበት ከገሊላ ኑሮው ተላቅቆ ለክርስቶስ በሰማዕትነት ጽዋ ለመመስከር ወደ ሮም መምጣቱ አስገረመኝ ። በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ስለ ጴጥሮስና ስለ ጳውሎስ አገልግሎት ብቻ የተጻፈ ይመስላል ። ብዙ ከተጻፈላቸው ብዙ መከራ ይጠብቃቸዋል ። ወንጌላዊ ሉቃስ አስተባብሮ ከጻፈላቸው እነርሱም ተባብረው ለክርስቶስ ሰማዕት ለመሆን ተሰባሰቡ ። ያገናኛቸው ቀጠሮ “ሰማዕትነት አያምልጥህ” የሚለው መንፈሳዊ ጥሪ ነው ። 

ሐዋርያው ጴጥሮስም ከመኝታው ብድግ ብሎ ተነሣ ። የመጨረሻው ሰዓት እየተቃረበ ነውና መልእክቱን በተተኪዎቹ ውስጥ ለመጻፍ እየተጋ ነው ። ጸሎት ከደረሰ በኋላ ሁላችንም ስፍራችንን ይዘን ተቀመጥን ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም፡- “ዛሬ የምነግራችሁ በፊልጶስ ቂሣርያ ስለተፈጸመው ቅዱስ ማቴዎስ በምዕራፍ 16 ላይ ስለመዘገበው ክስተት ነው ። ፊልጶስ ቂሣርያ የተባለችው በታላቁ ሄሮድስ ልጅ በፊልጶስ ተሠርታ ስለ ነበርና በባሕሩ ዳርቻ ካለችው ቂሣርያ ለመለየት ነው ። በሰሜን እስራኤል ከአርሞንየም ተራራ በስተደቡብ የምትገኝ የዮርዳኖስ ወንዝ መፍለቂያ ናት ። በዚህች ከተማ ታላቅ በረከትንና ጸጋን አገኘሁ ። ይህች ከተማ የዮርዳኖስ ወንዝ መፍለቂያ ስትሆን ጌታን ያገኘሁበትን የመጀመሪያውን ቀን ታስታውሰኛለች ። ከጌታዬ ጋር የተገናኘነው ዮሐንስ በሚያጠምቅበት በጌልጌላ አቅራቢያ ባለው በዮርዳኖስ ፍጻሜ አካባቢ ነው ። ዛሬ ደግሞ ወደ መነሻው መጣሁ ። በመጀመሪያው ቀንና በዮርዳኖስ ወንዝ ፍጻሜ ስሜ ተለወጠ ። ስምዖን ሳለሁ ኬፋ ተባልሁ ፤ በዮርዳኖስ መነሻም በፊልጶስ ቂሣርያ ጴጥሮስ ተብዬ እንደገና ስሜ ተለወጠልኝ ። ኬፋም በአራማይክ ፣ ጴጥሮስም በግሪክ ዓለት ማለት ነው ። ያ ዓለትም የማይፈረፈርና ጽኑ የሆነ ዓለት ነው ። ልቤን ፣ አቋሜን ፣ ኑሮዬን ሳስበው ይህ ስም አይገባኝም ። እኔ የሆንኩትን ሳይ ጌታዬ ግን የምሆነውን ያሳየኝ ነበር ። በዮርዳኖስ ፍጻሜ ጌታዬ መሰከረልኝ ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ መነሻ ደግሞ እኔ መሰከርሁለት ። ከፍጻሜው ወደ ጅማሬ የሚሄደው የአምላክ አሠራር ይገርመኛል ። እርሱ ሰማይንና ምድርን ፈጠረ ። ሰማይ ጉልላት ድምድማት በመሆኑ ፍጻሜ ነው ። ሥራውን የጀመረው ከፍጻሜው ነው ። እስራኤልን ከግብጽ ምድር ሲያወጣ ይነግራቸው የነበረው ማርና ወተት ስለምታፈስሰው አገር ነው ። በግብጽ ጭንቅ ውስጥ ሳሉ እርሱ ግን ከነዓን ቆሞ ጠራቸው ። ፍጻሜው ላይ ቆሞ ይጠራናልና ማንም ሊያስቆመን አይችልም ። የእግዚአብሔርን ጥሪ በሚመለከት መፍራት ያለብን ጠላትን ሳይሆን እልኸኛውን ልባችንን ነው ። እግዚአብሔር አሰበ ማለት ፈጸመ ማለት ነው ። በእግዚአብሔር ጅማሬና ፍጻሜ መካከል ምንም ልዩነት የለም ። ሲሻ ከመጀመሪያው ሲሻም ከመጨረሻው ይጀምራል ። በጥሪዬ ቀን ወንድሜ እንድርያስ ወደ ጌታ አቀረበኝ ፣ ዛሬ ግን ከሁሉም ቀድሜ አምላክም ሰውም መሆኑን መሰከርሁ ። ሰው እንደ ትላንቱ አይሆንም ። ሕይወት ጉዞ ናትና ለውጥ ይኖረዋል ። ከእኛም የተሻለ ይሆናል ። መኖር ያልጨረሰ ሰው መለወጡ አይቀርም ።

ጌታችን በፊልጶስ ቂሣርያ ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል  ብሎ ጠየቀን ። ሰዎች የሚሉትን ቢያውቀውም መስማት ግን ፈለገ ። ይሉኛልን ፈርተን ወደ ኋላ እንዳንል ፣ ሰዎች ግምታቸውን እንደ እውነት ሲናገሩ ፈገግ ብለን እንድናልፍ ይህን ጥያቄ አነሣ ። ሰዎች እርሱን የሚሉት ብዙ ነበር ። ሎቱ ስብሐት አብዷል ፣ በብዔል ዜቡል ይመራል ፣ ሕግ ያፈርሳል ፣ አገር ያስወርራል ይሉት ነበር ። እኛ ግን ይህን አላልነውም ። ክፉ ነገር ለወዳጅ አይነገርም ። እዚያው መልስ ሰጥተን መምጣት እንጂ ክፉ ወሬ ይዘን ወደ ወዳጃችን መምጣት እንቅልፍ መንሣት ነው ። ለጌታችን ጥያቄ የሰጠነው መልስ መልካም መልካሙን ነበረ ። እርሱ ግን ከመልካም በላይ ነበር ። “አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ ፥ ሌሎችም ኤልያስ ፥ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ” አልነው ። መጥምቁ ዮሐንስ ነው የሚሉት መናኔ ንብረት ፣ የከተማ ባሕታዊ መሆኑን አይተው ነው ። እርሱ ድንግልናዊ ሕይወትን አርአያ የሆነበት ፣ በተጠመቀ ቀንም ወደ ገዳም ወደ ደናግል መኖሪያ የሄደ ነው ። የደናግል መኖሪያ በከተማ ከሆነ ፣ የዚያም ምክንያት እነርሱን እያዩ ሰዎች ዓለምን እንዲንቁ ነው ። እንደ ዮሐንስ መጥምቅም በምድረ በዳ መኖር ይቻላል ። የድንግልናዊ ኑሮ ዓላማም ሕዝብን ወደ ክርስቶስ ለመመለስ ነው ። ጌታችን ዓለምን የናቀ ፣ ኑሮው ለደናግል አብነት የሆነ ነውና ዮሐንስ መጥምቅ ነው ይሉት ነበር ። ኤልያስም ኤርምያስም ደናግላን ናቸውና ነቢያትም ዓለምን የናቁ ናቸውና ግምታቸው ኑሮውን በማየት ነበር ። ነገር ግን እርሱ የነቢያት አምላክ እንጂ ከነቢያት አንዱ አልነበረም ። 

ጌታችን ሰዎች የሚሉትን መስማት የመጨረሻ ግቡ አልነበረም ። እርሱ መስማት የፈለገው እኛ የምናምነውን ነው ። አምኖ መመስከርና መስክሮ ማመን ይለያያል ። እኔም ለበጎ ነገር መዘግየት ብሎም ግራና ቀኝ መተያየት አይገባምና ፈጥኜ መልስ ሰጠሁ ። የአእምሮ ውጤቴ አልነበረም ። ጌታ እንደመሰከረልኝ ተገልጦልኝ ነው ። አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ አልኩት ። ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን በአጭር ቃል ገልጥሁ ። ይህን ምስክርነት ባለማጽናት በኋለኛው ዘመን ቤተ ክርስቲያን ትከፈላለች ። አርዮስ አምላክነቱን ዘንግቶ ፍጡር በመለኮቱ ይለዋል ። በዚህም በኒቅያ ታላቅ ጉባዔ ይደረጋል ። አውጣኪም ፍጹም ሰውነቱን ረስቶ አምላክ ብቻ ነው ይለዋል ። ከሥጋዌ በኋላ ያለውን በአንድ አካል መለኮትና ሰውነት ተዋሕደው መኖራቸውን ይክዳል ። ንስጥሮስም ሁለት አካልና ሁለት ባሕርይን ሲያስተምር የእርሱ ተከታዮች ደግሞ አንድ አካል ሁለት ባሕርይ ብለው ቤተ ክርስቲያንን ለሁለት ይከፍሏታል ። 

ይህን ምስክርነት እንደሰጠሁ ጌታችን አመሰገነኝ ። “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ።” አለኝ ። ምስክርነት እርሱን ደስ ያሰኘዋል ። ብፁዕ የተባልሁት አብ አምኖ ስለገለጠልኝ እንጂ ተመራምሬ ስለደረስሁበት አይደለም ። የተገለጠልኝን መግለጤም ብፅዕናን አስገኘልኝ ። ቤተ ክርስቲያኔን እመሠርታለሁ በማለትም ቤተ ክርስቲያን የእኔ ሳይሆን የራሱ መሆኗን መሰከረ ። በቃለ አሚንም ቤተ ክርስቲያን መመሥረቷን አወጀ ። እውነተኛይቱ ቤተ ክርስቲያን አንድ አካል አንድ ባሕርይ ብላ በክርስቶስ የምታምን ናት ። ሥልጣንንም ዛሬ ለእኔ ነገ ለተተኪዎች ሰጠ ። የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻዎችን ማለትም የጸጋ ስጦታዎችን ሲሰጠኝ ፣ የገሀነም ደጆችን ኃጢአትና ዓመፃ ቤተ ክርስቲያንን እንደማይችሏት አበሰረ ። የማሰርና የመፍታት ሥልጣንን ለእኔና ለቀጣይ የወንጌል አገልጋዮች ሰጠ ። ምድራዊውን ወንጌላዊ መግፋት ሰማያዊውን ክርስቶስ መግፋት ነው ። በረከተ ሐዋርያት በላያችሁ ላይ ይደር” ብሎ ዐረፍ አለ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

እሑድ ግንቦት 22 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም