መግቢያ » ትረካ » ጴጥሮስን አገኘሁት » ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 13

የትምህርቱ ርዕስ | ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 13

 

የሮማ ጎዳናዎች የቀደመውን መልካቸውን ባያጡም ኔሮን በ64 ዓ.ም. ሮም እንድትቃጠል በማድረጉ ብዙ ፍርስራሽ ቤቶች ይታያሉ ። ከዛሬ ሦስት ዓመት በፊት ኔሮን ቄሣር ሮምን ያቃጠለው ቤተ መንግሥቱን ለማስፋፋት አስቦ ነው ። ያቃጠሉትም ክርስቲያኖች ናቸው በማለቱ ሕዝቡ ሁሉ ባገኘበት ቦታ እንዲገድላቸው መንገዱን አመቻቸ ። በ54 ዓ.ም የነገሠው ኔሮን እስከ 64 ዓ.ም. በክርስቲያኖች ላይ ጥላቻ አላሳየም ነበር ። ግማሽ እብድ ተብሎ የሚጠራው ኔሮን የከተማይቱን መቃጠል ቁልቁል እያየ ይደሰት ነበር ። ከተማይቱም ሁለት ሦስተኛዋ በእሳት ነደደ ። እርሱም ሕዝቡም በሐሰተኛ ክስ ወንጀለኛ በተደረጉት ክርስቲያኖች ላይ የመዓት ጅራፋቸውን አነሡ ። እነዚህ ዓመታት ከባድ ናቸው ። ከሮማ ነገሥታትም የመከራው ጀማሪ እርሱ ሆነ ። ሮም ግን በፍርስራሽና በቃጠሎ ውስጥም ሁና ታምራለች ። ጎዳናውን ሳየው ሁሉም መንገዶች በእቅድ የተሠሩ ከሮም እንዲያወጡና ወደ ሮም እንዲያደርሱ ሁነው የተሠሩ ነበሩ ። ሕዝቡ ግን ንብረቱ ስለወደመበት አንዴ ንጉሡ ነው ሌላ ጊዜም ክርስቲያኖች ናቸው አንዳንዴም አማልክትን ክርስቲያኖች ስለ አስቆጡአቸው መዓት አምጥተውብን ነው ይል ነበር ። እኔም ከአውግስጦስ ቄሣር ጎዳና ተነሥቼ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ቤት የምጓዘው የሕዝቡን የጥላቻ አስተያየት እያየሁ ነበር ። የዓለምን እንኳን ጥላቻውን ፍቅሩንም ንቄው ነበርና አልተገረምኩም ። ላመነበት ነገር ጠንካራ የሆነው የሮም ሕዝብ ክርስትናን ቢያውቅ ከእኔ የተሻለ በሕይወቱ ይኖረው ነበረ ። በጥላቻና በፍቅር ፣ በኀዘንና በደስታ ውስጥ ጎዳናውን አቋርጥ ነበር ። እግሬ ሠረገላ ባይሳፈርም ልቤ ግን በአሳብ ሠረገላ ላይ ነበረ ። 

ከቀልቤ ጋር ባልሆንም ጎዳናውን በትክክል እያቋረጥሁ መንገዱንም ሳልስት በጳውሎስ ደጃፍ ደረስሁ ። ወዴት እንደምሄድ አውቅ ነበርና ሰዓቱን አልባከነብኝም ። እንዴት በአሳብ ዓለም ጠፍቼ ሳለሁ በደመ ነፍስ መንገዱን አወቅሁት ብዬ ራሴን ስጠይቅ አንደኛ ማንነቴ እግዚአብሔር መንገዱን እየመራህ ነበር አለኝ ። ከሚወጣና ከሚገባ ሰው የተነሣ ክርስቲያኖች በዚህ ቤት መሰባሰባቸው ብዙም እንዳይታወቅ የጳውሎስ ቤት በሩ ገርበብ ያለ ነበር ። ደግሞም የአገልጋይ ደጃፍ የእግዚአብሔር ደጃፍ ነውና በሩ ዝግ መሆን የለበትም ። እኔም ሰላምታ ሰጥቼ ወደ ውስጥ ስገባ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከመሬት መኝታው ለመነሣትና እኔን ለመቀበል መቧጠጥ ጀመረ ። ሐዋርያው ሥልጣኑ አገልጋይ እንጂ ጌታ አላደረገውም ። እኔም አይገባም ብዬ መኝታው ላይ ሳለ ያዝሁት ፣ ጉልበቱንም ስሜ ዝቅ አልኩ ። እርሱም ወትሮ እንደሚያደርገው እጆቹን በግንባሬ ላይ አድርጎ ባረከኝ ። ታላቅ ሸክምም ሲናድልኝ እየተሰማኝ የነፍስ አርነት ወደ ውስጤ መግባት ጀመረ ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከላይ ሲያዩት ቍጠኛ ፣ ንግግሩም ኃይለኛ ቢመስልም ውስጡ ግን በፍቅር የረጠበ ፣ በእንባም ቋንቋ የሚናገር ነበረ ። ሐዋርያው ጳውሎስም ከጴጥሮስ ተቀብሎኝ እቅፉ ውስጥ አስገብቶ ሰላምታ ሰጠኝ ። በአባታዊ ፍቅርም ጀርባዬን እየጠበጠበ አቀረበኝ ። እኔም የሁለቱን ቅዱሳን ሐዋርያት በረከት ሳገኝ ሁለት ክንፍ እንዳበቀለ ተሰማኝና በአየራቱ ላይ ለመብረር ለልቤ መልእክት ላኩበት ። ለካ የእግዚአብሔርን አገልጋይ ማግኘት ትልቅ በረከት አለው ! 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ራሱ በራ ወይም የሚያበራ ነበር ። አሁን በጋ እየመጣ ስለነበር ገለጥ አድርጎታል ። ቁመቱ አጭር ሲሆን ከእቅፉ ውስጥ ለመግባት ዝቅ ማለት ነበረብኝ ። ሐዋርያው አቅሙ ደካማ በበሽታ የተጎዳ ነበር ። የሥጋ ብርታት የእግዚአብሔርን መንግሥት አያገለግልም ። የመንፈስ ሙላት ግን ለብዙዎች መዳን ምክንያት ይሆናል ። ሐዋርያው በልብሱ ቅዳጅ ፣ በአካሉ ጥላ ድዉይ እየፈወሰ እርሱ ግን ታማሚ ነበረ ። በተሰጠው ጸጋ እንዳይታበይ በሽታው መጠበቂያ ሆኖለት ነበር ። ከበሽታ በላይ ትዕቢት ትልቅ በሽታ ነው ። እኛ ራስ ምታትን እንፈራለን ፣ እግዚአብሔር ግን ትዕቢትን ይፈራልናል ። ዲያብሎስ የወደቀው በዝሙት ሳይሆን በትእቢት ነው ። ትዕቢት የኃጢአት መነሻ ነው ። ሐዋርያው ጳውሎስ የማያቋርጥ ራስ ምታት ደግሞም የዓይን ሕመም ያሰቃየው ነበር ። መልእክቱንም ዓይኑን ጨፍኖ እየተናገረ ፀሐፍያኑ ይጽፉለት ነበር ። በመጨረሻ መልእክቱን ሲዘጋ ለፊርማው እርሱ ይቀበላቸው ነበር ። 

ቅዱስ ጴጥሮስም ለማታ የእግር ፣ ለጠዋት የፊት ውኃ የሚያቀርብለትን ማርቆስን ጠራው ። ሲላስና ጢሞቴዎስ ቢኖሩም እንዲህ ያሉ ትእዛዛትን ለማዘዝ ማርቆስ ይቀለው ነበር ። ከጣትም ጣት ይበልጣል እንዲሉ ማርቆስ ያረካው ነበር ። የማርቆስ ወንጌልም የጴጥሮስ ወንጌል ነው ። ጴጥሮስ ታሪኩን እየነገረው ጻፈው ። ነገር ግን ትሑት ነውና በአንተ ስም ይሁን በማለት የማርቆስ ወንጌል ተብሎ ተሰየመ ። ማርቆስ ስሜቱ ቶሎ የሚረበሽ ልጅነት የሚያጠቃው ቢሆንም ጴጥሮስ ግን ያንን የድሮውን ሕፃንነቱን እያሰበ ይራራለት ነበር ። ማርቆስም እንደ ተቀባበለ መሣሪያ ፈጥኖ የታዘዘውን አደረገ ። አባት ለመሆን ልጅ ፣ መምህር ለመባልም ተማሪ መሆን ግድ ይላል ። የረድዕ ጆሮ ንቁ ፣ ክንፉም ለመብረር የተዘረጋ ነው ። ጴጥሮስም የፊት ውኃ እንደ ቀረበለት ማርቆስን፡- “የግብጽን ቤተ ክርስቲያን ትመራለህ ፣ አባት ተብለህም ትጠራለህ ። ሰብአ ኢትዮጵያም ማርቆስ አባቴ  ብለው ይጠሩሃል ። በመንበርህም የሚሾም አይታጣም” በማለት የጅምሩን ፍጻሜ ነገረው ። ማርቆስም ደስ አለው ። አንድ የፊት ውኃ አቅርቦ ይህን ሁሉ በረከት መቀበል እግዚአብሔር ባለጠጋ ነው እንድል አደረገኝ ። ማርቆስም ጴጥሮስን ፣ እነ ሲላስም ጳውሎስን ሊሰናበቱ የመጡ መሰለኝ ። የመጨረሻው ሰዓት ሁሉን ይሰበስባል ። 

ሐዋርያው ጴጥሮስም የእግዚአብሔርን ሥራ ሊናገር ሲል የደከመው አቅሙ በረታ ። ቃለ እግዚአብሔር አጥንትን የሚያጸና ፣ ሥጋን የሚያለመልም ነውና ። ጉባዔውን በጸሎት ከፈተ ። ሐዋርያውም መናገር ጀመረ ፡- 

ከደብረ ታቦር ከወረድን በኋላ ወደ ቅፍርናሆም መጣን ። በዚያም ግብር የሚያስከፍሉ ሰዎች ግብር እንድንከፍል አዘዙን ። በቀጥታ ክርስቶስን አልጠየቁም ፣ እኛን ጠየቁን ። የዓለሙ መምህር ሳለም መምህራችሁ ግብር አይከፍልም ወይ ? የሚል ጥያቄ አቀረቡልን ። ጥያቄውንም ያቀረቡት በይበልጥ ለእኔ ነበርና ግራ ገብቶኝ ነበር ። እንዲህ በአሳብ እየተጉላላው ወደ ቤት ገባሁ ። ይህ በብዙ መንገድ ከባድ ነበረ ። ግብር የሚሰበስቡት ለሮማ መንግሥት ነበረ ። ጌታን ከሚከተሉ አብዛኞቹ ከሮማውያን ነጻ ያወጣናል ፣ አንድ ቀንም እንቢ ለሮማውያን ብሎ ያዘምተናል ብለው በእምነት ሳይሆን በአርበኝነት መንፈስ የሚከተሉት ነበሩ ። ቀነናዊ ስምዖንም ከአርበኝነት የተጠራ ነውና ስሜቱ ስስ ነው ። ግብርን ሲከፍል ሲያዩት የሮማ መንግሥት ወዳጅ ነውና መሢሕ አይደለም ለማለት ቅርብ የነበሩ ሰዎች አሉ ። ግብርን አልከፍልም ቢል ደግሞ የሮማ መንግሥትን ይቃወማል ይባላል ። ከሁሉ በላይ እርሱ ንጉሠ ነገሥት ሳለ ግብር ይገባለታል እንጂ አይገብርም ። ጌታ ግን የሰዎቹንም ጥያቄ የእኔንም ግራ መጋባት ያውቃል ። ወደ ቤት እንደ ገባን አንድ ጥያቄ ጠየቀኝ፡- ስምዖን ሆይ ፥ ምን ይመስልሃል ? የምድር ነገሥታት ቀረጥና ግብር ከማን ይቀበላሉ ? ከልጆቻቸውን ወይስ ከእንግዶች ? ሲለኝ ከእንግዶች አልኩት ፤ ጌታም እንኪያስ ልጆቻቸው ነጻ ናቸው ። ነገር ግን እንዳናሰናክላቸው ፥ ወደ ባሕር ሂድና መቃጥን ጣል ፥ መጀመሪያም የሚወጣውን ዓሣ ውሰድና አፉን ስትከፍት እስታቴር ታገኛለህ ፤ ያን ወስደህ ስለ እኔና ስለ አንተ ስጣቸው አለኝ ። እኔም ያዘዘኝን አደረግሁ ። 

ጌታችን እግረ መንገዱን ያስተማረው ቋሚ የሆነውን ትምህርት ነው ። በዚህ ዓለም ላይ አንግዶች ነን ። እንግዳ ከቤቱ ርቆ የሚኖር ነው ። እኛም ከመኖሪያችን ርቀን ያለን እንግዶች ነን ። እንግዳ በትሩን በእጁ ይዞ ፣ ወገቡን ታጥቆ ፣ የጫማውን ማዘቢያ ቋጥሮ የሚበላ ነው ። እኛም ሰማይን እያሰብን የምንማርና የምንሠራ ነን ። እንግዳ ቢዘገይም መሄዱ አይቀርም ፣ እኛም ማለፋችን አይቀርም ። አንድ ቀን የሚውለውም ሳምንትና ወራት የሚከርመውም ሁሉም እንግዳ ይባላሉ ። በዕለት የሞተውም በሰማንያ ዓመት የሚሞተውም እንግዳ ናቸው ። እንግዳ ፊት አይነሡትም ፣ ነገ ይሄዳልና ፤ እኛም ወንድማችንን ከደቂቃ በኋላ ልናጣው እንችላለንና ክፉ ፊት ልናሳየው ፣ ክፉ ቃል ልንናገረው አይገባም ። እንግዳ መሄዱን እያሰበ አመሉን አያስቆጥርም ። ክርስቲያንም ሞቱን እያሰበ በቅዱስ ፍርሃት ይኖራል ። ጌታ የነገሥታት ንጉሥ ሳለ ግብር ከፈለ ። እኛም የእርሱን ትሕትና እያሰብን ግብር መክፈል ይገባናል ። የመንግሥት ሥርዓት የእግዚአብሔር ሥርዓት ነውና ማክበር ያስፈልገናል ። ጌታችን በተአምራት ከዓሣ ሆድ የተገኘውን እስታቴር እንድገብር አደረገ ። በዚህም መገበር የማይችል በኪሱ ገንዘብ የሌለው ፍጹም ድሀ መሆኑን ፣ መስጠት የሚችል የተአምራት አምላክ መሆኑን ገለጠ ። 

ሐዋርያው ጳውሎስም በዚህ አለ ፣ ጢሞቴዎስም በዚህ አለ ። ባለፈው በላከው በጢሞቴዎስ መልእክት በምዕራፍ ሁለት ላይ፡- “እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር፥ ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ።” ብሏል ። ነገሥታትን ማክበር ማለት ግብርን በታማኝነት መክፈል  ነው ። ደግሞም ክርስቶስ ለእነርሱም ሙቷልና የመዳንን ወንጌል ማድረስ ፣ ከሁሉ በፊት ስለ መሪዎች መጸለይ ይገባል ። የመርከቡ ካፒቴን ሲታወክ ተሳፋሪውም አብሮ ይታወካል ። የመርከቡ አደጋ መርከቡ ላይ ሁሉ የተሳፈሩትን ይነካል እንጂ እኔን አይመለከተኝም የሚባል አይደለምና ለአገራችሁም ጸልዩ ። ርቃችሁ በሮም ብትኖሩም ለምትኖሩበት አገርም ጸልዩ ። እግዚአብሔር በጸጋ በበረከት ይጠብቃችሁ።”

ሁላችንም ተነሣን “አሜን” አልን ። አገራችን ኢየሩሳሌም በ70 ዓ.ም እንደምትደመሰስ ትንቢት ሰምተናልና ለመጸለይ ልባችን መደንዘዙን የሐዋርያው ምክር አነቃን ። ለመፋቀርም ፣ ወድቆ ለመነሣትም አገር ያስፈልጋል ። በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ የኢየሩሳሌም ብሔራዊ መዝሙር መስፈሩ አገር ክቡር መሆኑን ፣ ደግሞም አገራችን ለእኛ ኢየሩሳሌም መሆንዋን እንድናስብ ነው ። ሰማያዊት አገርን የምንወርሰው በምድራዊት አገራችን ላይ ሆነን በምንወስነው የእምነት ውሳኔ ነው ። አቤቱ አገራችንን ጠብቅልን ።

ይቀጥላል 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ማክሰኞ ሰኔ 15 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም