መግቢያ » ትረካ » ጴጥሮስን አገኘሁት » ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 14/

የትምህርቱ ርዕስ | ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 14/

 

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስን ለማየት የነበረኝ ጉጉት ልዩ ነበር ። እግዚአብሔር ከአዋቂ በአስተዋይ ፣ ከብርቱ በገራም ደስ እንደሚለው የቅዱስ ጴጥሮስ ሕይወት ምስክር ነው ። እውቀት ወደ ማስተዋል ካልመራ ፣ ብርታትም ገራም ካላደረገ ጅማሬ እንጂ ፍጻሜ የለውም ። ደስ የሚያሰኝ ጅማሬ ደስታው የሚዘልቀው ፍጻሜ ሲኖረው ነው ። እውቀት ፣ ብርታት ጅማሬ ነው ። ከመጀመሪያው የመጨረሻው ይሻላል ። ሐዋርያው በዚህ ሳምንት ቶሎ ቶሎ እያስተማረን ነው ። እኔም ሁለት ነገሮችን ተገነዘብሁ ። ስፈልገው የነበረውን መንፈሳዊ ገበታ ሳገኘው እንዳልንቀውና እያንዳንዱን ቀን እንደ መጨረሻ ቀናችን አድርገን ከኖርን ብዙ መሥራት እንደምንችል ተረዳሁ ። ሐዋርያው ምስክርነቱን በሰማዕትነት ሊፈጽም ጥቂት ቀን እንደ ቀረው አውቄአለሁ ። ዛሬ ሰኔ 29 ቀን 67 ዓ.ም ነው ። 

ማልጄ ደርሻለሁ ። በቁሙ ያልተጠቀሙበትን ሰው ሲሞት መቆጨት ዋጋ የለውም ። ከዚህ በፊት ስላለፉት ስለ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስና ስለ ያዕቆብ ሐዋርያ ብዙ ይቆጨኝ ነበር ። ባለፉት ስንቆጭ ያሉትን ማየት ተገቢ ነው ። አሊያ የቁጭት ክምር በላያችን ላይ ያርፋል ። ከትላንት እንደ ተማርን ማስረጃው የዛሬዎቹን ማክበር ነው ። ቅዱስ ጴጥሮስ ዛሬ ብርሃን ለማግኘት ወደ በሩ ተጠግቶ ማስተማር ጀመረ ። እንዲህም አለ፡- 

“ባለፉት ቀናት እንደ ነገርኳችሁ ታሪኬ ከክርስቶስ ጋር የተሳሰረ ነው ። ታሪኬ ያለ ክርስቶስ መቆም አይችልም ፣ ይወድቃል ። ጠባዬን ዞር ብዬ ሳየው የተለያየ ነው ። አንዳንዱ የማይጨበጥ ነው ። ክርስቶስ ከዚህ ማንነቴ ጋር እንደ ወደደኝ ሳስብ ኩራት ይሰማኛል ። መከፋቴና መደሰቴ በፊቴ ላይ ቶሎ ይታወቃል ። ሰውን መውደድ እንጂ መደለል አልወድም ። ላመንኩበት ነገር ሕይወቴን እሰጣለሁ ። ብዙ ዘመን ዋጋ ብከፍልበትም ውሸት መሆኑን ሳውቅ ቶሎ እጥላለሁ እንጂ እንዴት ይህን ሁሉ ዋጋ የከፈልኩበትን በቀላል እጥላለሁ ብዬ እልህ አልጋባም ። የዛሬ እውነት የብዙ ዘመንን ውሸት ትክሳለች ። ያልገባኝን ነገር ለመጠየቅ አላፍርም ። ዕድሜዬን ፣ ሽበቴን በማሰብ ወይም በሰብአዊ ኩራት ውስጥ ሆኜ ያልገባኝን ነገር እንደ ገባኝ ለማስመሰል አልጥርም ። ይሉኝታን አልፈራም ። የሰው ልጅ ትልቅ ወጥመድ ይሉኝታ ነው ። እኔ ከዚያ ተፈትቻለሁ ። ዙሪያዬን አይቼ ያመንኩበትን ነገር አልክድም ። ብቻዬን ብቆምም ያመንኩትን አከብረዋለሁ ። ከብዙኃን መጣላትን አልፈራም ። እኔ መጣላት አልፈልግም ፣ ሰዎች ግን እኔን ባሳረፈኝ እውነት መጣላት ከፈለጉ አልጨነቅም ። እንባ ያጠቃኛል ። ስሜቴ ስስ ነው ። ከሰዎች ብዙ እጠብቃለሁ ። ለነገሮች ሁሉ ፈጣን ነኝ ። ፈጥኜ ብሠራም ውጤቱ ግን ያንስብኛል ። የተረዳሁትን እውቀት ቶሎ ለማስተላለፍ እፈልጋለሁ ። የምሥራቹን ይዞ ማደር ያስጨንቀኛል ። ሰው ሁሉ እንደ እኔ ቢሆን እፈልጋለሁ ። ጸሎትን ትቼ ፉከራ አበዛለሁ ። የወደድኩትን ሰው እስከ ዘላለም የምወደው እየመሰለኝ እፎክራለሁ ። መፎከር ጸሎትን ያስረሳል ። ሰው የሚወድቀው እንደሚያሸንፈው እርግጠኛ በሆነበት ነገር ነው ። ምክንያቱም በዚያ ጉዳይ መጸለይ አቁሟና ይዘናጋል ። መንፈሳዊውን ውጊያ በሥጋ መሣሪያ ለማሸነፍ ሰይፍ መምዘዝ እወድ ነበረ ። ሰዎች ፊታቸውን ቅጭም ሲያደርጉብኝ ፀሐይ የጠለቀች ያህል እፈራ ነበር ። ሁሉም ሰው ምን ያውቃል ደግ ነው ሲለኝ ክፉ ነው እንዳይለኝ እባክን ነበር ። የምወደውን ሰው ሞቱን ሳስብ ቁጭ ብዬ አለቅሳለሁ ። መዋደድ እንዳለ ጠብ ፣ መኖር እንዳለ ሞት ተረስቶኝ ነበር ። ኑሮዬ የዕለት ነው ። በትዳር ብኖርም የሌጣ ያህል ገንዘብን እበትን ነበረ ። ምን እሆናለሁ ? የሚል ሙግት በውስጤ ይወዘውዘኝ ነበር ። በይቅርታ ባምንም ሰባት ጊዜ እንጂ ከዚያ በላይ ይቅር ማለት አለብኝ ብዬ አላምንም ነበር ። ይህን ሁሉ ጠባዬን የክርስቶስ ፍቅር ፣ የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት አስተካከለልኝ ። 

እናንተም ቋሚ ማንነት ይኑራችሁ ። እንደ ቀኑ የአየር ሁኔታ ተለዋዋጭ አትሁኑ ። የአየር ንብረት ቋሚ ነው ፣ የአየር ሁኔታ ግን ተለዋዋጭ ነው ። አሁን ሳቂታ ቀጥሎ አኩራፊ ፣ አሁን አመስጋኝ ቀጥሎ ተራጋሚ ፣ አሁን ቸር ቀጥሎ ቢስ አትሁኑ ። እንዲህ ዓይነት ጠባይ ከቀላልነት ፣ ከስሜታዊነትና ከሱሰኛነት የሚመጣ ነው ። መንገደኛና ዛሬ ያወቃችሁ በቀላሉ የሚያነባችሁ ሰው አትሁኑ ። ችግራችሁን በልባችሁ መቻል አቅቷችሁ በፊታችሁ አደባባይ አታስነብቡ ። ሊረዱአችሁ የማይችሉት ልጆቻችሁ ይሳቀቃሉ ። ወዳጆቻችሁ ምን ሆነው ነው በማለት ይጠራጠራሉ ። ጠላቶቻችሁ ይስቃሉ ። ይህን ስላችሁ እውነተኛ ስሜታችሁን አትግለጡ ማለቴ አይደለም ። ቦታውን ግን ምረጡ ። ሰውን በተግባር ውደዱት ። ከእናንተ ጋር ግን መኖር ያለበት በፍቅር እንጂ በማባበላችሁ መሆን የለበትም ። ማባበል ሆድ ማስባስ ነው ። በፍቅር ዓለም ብከዳስ ብላችሁ አታስቡ ። እናንተ ከፍቅራችሁ ጋር ከቀራችሁ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና ከእግዚአብሔር ጋር ቀርታችኋል ። ላመናችሁበት ነገር ስትኖሩ የሚያስከትለውን ውጤት ተምኑ እንጂ አትፍሩ ። ዋጋ ለመክፈል የፈራችሁበት ነገር በደንብ ያልተረዳችሁት ነገር ነው ። ጥላቻም ዋጋ ያስከፍላል ፣ ለፍቅር ዋጋ መክፈል ግን ያኮራል ። የኖርኩበትን ዘመን ውሸት ነበር አልልም ብላችሁ ሐሰትን ለመጣል አትግደርደሩ ። የእናንተን እውነት ከእግዚአብሔር እውነት ለዩ ። አልገባውም እንዳትባሉ ፈርታችሁ ያልገባችሁን ነገር ገብቶኛል አትበሉ ። መጠየቅ የእውቀት እናት ናት ። ሁሉን ለማወቅ እንኳን ምድር ሰማይም ብትሄዱ አይበቃም ። በዓለም ካሳለፋችሁት አእላፍ ቀናት በእግዚአብሔር ቤት የምታሳልፉት አንድ ቀን ይበልጣል ። የሰማንያ ዓመት ኃጢአት በአንድ ሰዓት ንስሐ ይካሳልና ንስሐ ለመግባት አትፍሩ ። ዘመን ያመጣው ዘፈን እንቅርት ያፈርጣል እንዲሉ በወቅታዊ ርእስ ተንታኝ አትሁኑ ። 

ትላንትን ባስብ እኔ ከሀዲ ነበርሁ ። ጌታዬ እኔን የተማመነኝን ያህል እኔ በእርሱ አላመንኩም ነበር ። ዓለቱን ጌታ ተጠራጥሬ ሸምበቆ የምሆን እኔን ግን አምኖ አደራ ሰጠኝ ። ይሉኝታን አትፍሩ ። ሰው የሚለው አያጣም ። ትሑት ብትሆኑ ልምጥምጥ ፣ ትዕቢተኛ ብትሆኑ ጨካኝ ፤ ብትሰጡ በታኝ ፣ ብትሰስቱ ዱሽ ይላችኋል ። እንደ ሰው ማን ጸድቆ ፣ እንደ ክርስቶስ ማን ተኰንኖ ! 

ልጆቼ ሆይ ስሙኝ ። የተማራችሁት ብዙኃኑ ለተስማማበት ሐሰት አሜን እንድትሉ አይደለም ። መማር ልዩነት ካላመጣ አለመማር ነው ። ከብዙኃኑ ይነጥለኛል ብላችሁ መለኮታዊን ነገር አትጣሉ ። ማማት እንጂ መታማትን አትፍሩ ፣ አትጣሉ እንጂ ቢጣሉአችሁ አትስጉ ።  ሰው ከዳኝ ፣ ንብረት ተወሰደብኝ ብላችሁ እንባን አታፍስሱ ። የማይከዳው ጌታ ከእናንተ ጋር ነው ። ርስተ መንግሥተ ሰማያትም ይጠብቃችኋል ። አንድ ቀን ሁሉን ትታችሁ በጨርቅ ተጠቅልላችሁ ወደ መቃብር ስትወርዱ ሁሉም ትቷችሁ ይመለሳል ። ንብረታችሁም ለጠላችሁት ሰው ይሆናል ። ከሰዎች ብዙ እንድትጠብቁ ሰይጣን ሲፈትናችሁ ሰዎቹ ደግሞ በጥቂቱ እንዳይገኙ ይዋጋቸዋል ። እግዚአብሔርን የጠበቀ ፍሬውን ይበላል ። ሰውን የጠበቀ ያፍራል ። ፍጥነት ሁሉ ትጋት ፣ ማዝገም ሁሉ ትዕግሥት አይደለም ። ዛሬ ልትሠሩት ስትችሉ ነገ ብላችሁ ሥራን አታሳድሩ ። የሰማችሁትን ቃለ እግዚአብሔር ለሌሎች ማሰማት ተገቢ ነው ። አዋጅ ያልሰማህ ስማ ፣ የሰማህ ላልሰማ አሰማ ነውና ። ሰው እንደ ራሱ እንጂ እንደ እናንተ አይሆንምና ትግል ውስጥ አትግቡ ። ጸሎትን የሚያስተው ሥጋዊ መተማመን ነውና ተጠንቀቁ ። ካልደፈረሰ አይጠራም ብላችሁም ነገሮችን አታደበላልቁ ፣ ሰው ያደፈረሰው አይጠራምና ። መንፈሳዊ ውጊያን በሥጋ መሣሪያ በስድብ ፣ በትችት አትመክቱ ። ጸጋ እግዚአብሔር እየራቃችሁ ይመጣል ። የነቀፋ ትምህርት ማስተማር የለመደ ጤነኛ ትምህርት ማስተማር ይቸገራል ። ነቀፋ ያልቃል ፣ ቃለ እግዚአብሔር ግን አያልቅምና ኩሬውን ትታችሁ ከምንጩ ቅዱ ። 

እኔ በገባሁበት ጦርነት ሁሉ ሲባባስ እንጂ ሲበርድ አይቼ አላውቅም ። የጦርነት መጨረሻ ጦርነት አይሆንም ። ሥጋዊ ውጊያ ግን ሁልጊዜ በጦርነት ያኖራል ። እግዚአብሔር ይዋጋላችሁ ዘንድ እመኑት ። ወዶኛልና አዳነኝ ይላል ። ሰው ወድዶ ሊያድን አይችልም ። የማያድነውን የሰው ፍቅር አታሳድዱ ። ደግ ነው የሚል ዜማ ለመስማት ገንዘባችሁን አትበትኑ ። ያለ ምርቃትም መስጠትን ተለማመዱ ። ገንዘብ ዘር ነውና የት ነው የምዘራው ? በሉ ። ለባለጠጋ ድሀ ብትሰጡ እሾህ ላይ የተዘራ ነውና ይታነቃል ። ይገባኛል የሚሉ ደንዳኖች ላይ ብትዘሩ ድንጋይ ላይ የወደቀ ነው ። ሱሰኞች ላይ ብታባክኑ መንገድ ዳር የተዘራ ነው ። ጥሩ ልብ ላላቸው ፣ አትርፈው ለሚጸልዩላችሁ ገንዘባችሁን ዝሩ ። ሰው በፍቅር ጀምሮ በጠብ መጨረሱ የተለመደ ነው ። ያልወደደውን አይጣላምና በሰው ተለዋዋጭነት አትገረሙ ። የምትወዱት ሰው የሞተው የከዳችሁ ቀን ነው ። የተፈጥሮ ሞትን ቢሞት የሰው ሁሉ መንገድ ነው ። ምን እሆናለሁ ? ማለት የአሕዛብ ጥያቄ ነው ። የሰው ዕድሉ በእግዚአብሔር እጅ ነው ። እግዚአብሔር የጻፈላችሁን ሰው አይሰርዘውም ። ያለ ገደብ ይቅር ተብላችኋልና ለይቅርታ ገደብ አይኑራችሁ ። ያዘናችሁበትን ሰው ተቀይሜሃለሁ በሉ እንጂ የውሸት እወድድሃለሁ አትበሉ ። ያም ሰው ስህተቱን ማወቅ እናንተም ከቂም መዳን አለባችሁ ።

በሉ ለዛሬው ይበቃናል ። እግዚአብሔር በሰማያዊና በምድራዊ በረከት ይባርካችሁ !

ሁላችንም ከተቀመጥንበት ተነሥተን አሜን አልን ። ሐዋርያውም በአሚነ ሥላሴ ያጽናችሁ ብሎ ባረከን ! 

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሰኔ 22 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም