መግቢያ » ትረካ » ጴጥሮስን አገኘሁት » ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 6/

የትምህርቱ ርዕስ | ጴጥሮስን አገኘሁት /ክፍል 6/

 

እንኳን ለ2013 ዓ.ም. የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል በሰላምና በጤና አደረሳችሁ !

ቅዱስ ጴጥሮስ እየመገበ ያለው ሥጋችንንም ነፍሳችንንም ነው ። ሥጋችን መቀመጥ ብቻ ያደነዝዘዋል ፣ መሮጥ ብቻም ያዝለዋል ። የተመጠነ ዕረፍትና ሩጫ ግን ሕይወት ይሆነዋል ። በጎዳናው ተላውሰን ፣ በመንገዱ ተመላልሰን ወደ ቤት ተመለስን ። ሐዋርያው ጴጥሮስም ክርስቶስ በዕድሜ በዘመኑ የሠራውን ድንቅ ነገር ለመተረክ ተነሣ ። እንደ መጨረሻ ቃሉም እያስረገጠ ሲናገር እንደ አንቀጽና እንደ ሕግ እንዲያዝለት የፈለገ ይመስላል ። እኛም በትጋትና በጥንቃቄ እንሰማ ነበር ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በአንክሮ ሁኖ ያዳምጥ ነበር ። የሚወራው በሰው ታሪክ ላይ ድንቅ የሚያደርገው የመለኮት ግብር ነውና በታላቅ አክብሮት ያዳምጥ ነበር ። እርሱም በማመንና በማገልገል የሚቀድመውን ጴጥሮስን ያከብር ነበር ። ብዙ መልእክት ቢጽፍም ፣ ብዙ አገር ቢያስስም ፣ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ቢተክልም አሁንም ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጴጥሮስ ለመማር ቀርቧል ። ጸጋ የበዛለት ሰው ምልክቱ የሌላውን ጸጋ የሚያከብር መሆኑ ነው ። የእኔ ጸጋ አባ ጠቅል ነው ብሎ የሌላውን ጸጋ የሚጋፋ እርሱ ጸጋ የተለየው ነው ። ጸጋ በማመን ይሰጣል ። የልጅነት ስጦታ ነው ። ጸጋ በልመናና በትሕትና ይጨመራል ። ማንም ጥበብ ቢጎድለው መጸለይ ፣ ትንቢት መናገርን ወይም መስበክን በብርቱ ቢሻ ከእግዚአብሔር ይሰጠዋል ። ሐዋርያው ጳውሎስም እስከ ዕለተ ሞት ድረስ ትምህርት አያልቅም ብሎ የሚያምን ነበር ። የማይማር ሰው ሞቶ የሚኖር ነው ። የሕያውነት ምልክቱ ትምህርትን አለማቋረጥ ነው ። የምንኖረው ለማወቅ ነውና ። አለማወቅን ማወቅ ብዙ የማወቅ ልክ ነው ። ከሌላው የምማረው አለኝ ብሎ የሚያስብ ሰው እውቀቱ ፍቅርና ትሕትና ያለበት ነው ። ፍርሃት ከጥላቻ ይመነጫል ። ሌላውን ሰው ስንወደው ያጠቃኛል ብለን መፍራት እናቆማለን ። እርሱም ጣቶቹ ምላጩ ላይ ቢሆኑም መተኮስ ግን ያቅተዋል ። ፍቅር ክፉዎችን ልምሾ ያደርጋል ። እጅግ ደንዳኖችን ግን እንደ ክርስቶስ ሰቃዮች ሰቃልያነ ጻድቃን ያደርጋቸዋል ። 

በዚህ ጊዜ እማሆይ ፌበን የሚበላና የሚጠጣ ለማቅረብ የማርታን አገልግሎት ለማከናወን ፈለገች ። የማርታ አገልገሎት የተነቀፈ አይደለም ። ጌታን ለመጋበዝ ስታስብ የጌታ ግብዣ የሆነውንም ቃሉን ብትሰማ ኖሮ አገልግሎቷ ሥሙር ይሆን ነበር ። የመጀመሪያዎቹ ሰባት ዲያቆናት የተሾሙት ማዕድ ለማሳለፍ ነው ። ለአጋፋሪነት ተሹመው ቀዳሜ ሰማዕት በመሆን እስጢፋኖስ ፣ ወንጌላዊ በመሆንና ኢትዮጵያዊውን ጃንደረባ በማጥመቅ ፊልጶስ ትልቅ ሥራ ሠርተዋል ። መንፈሳውያን አገልጋዮች የቱንም ያህል ጸጋ ቢበዛላቸው ሰው መሆናቸው መረሳት የለበትም ። እንደ ሰው ይራባሉ ፣ ይጠማሉ ። ክርስቶስ እንኳ በለበሰው ሥጋ ተራበ ፣ ተጠማ ተብሎ ተነግሮለታል ። መንፈሳውያን አገልጋዮችን በሥጋቸው መንከባከብ ይገባል ። በነፍስ ለሚመግቡንን በሥጋ መመገብ ፣ ጸጋን ለሚያካፍሉን ደመወዝን መስጠት ወግ ነው ። ደግሞም የማያልፈውን ለሰጡን የሚያልፈውን ገንዘብ መስጠት ቁምነገር የለውም ። በእግዚአብሔር ፊት ባዶ እጅ መታየትን ኦሪት ነቅፋለች ። ምእመናን ወደ ቤተ እግዚአብሔር የሚያመጡት ለአገልጋዮች መተዳደሪያ ነውና ። አገር በግብር እንደሚቆም ፣ ቤተ እግዚአብሔርም በአሥራት ይቆማል ። ግብርን አለመክፈል አገርን በመካድ ወንጀል እንደሚያስጠይቅ አሥራትን አለመስጠትም እግዚአብሔር አልሰጠኝም ብሎ መካድና በረሀብ ምክንያት የእግዚአብሔር አገልጋዮች እንዲበተኑ ማድረግ ነው ። ራሱን ደመወዝ እየከፈለ በጎች የሚጠብቅ እረኛ የለም ፣ በራሱ መሣሪያም የሚዋጋ ወታደር የለም ። እንዲሁም ድንኳን እየሰፋ ጳውሎስ ቢያገለግልም ድንኳን እንዲሰፋ ያደረጉትና ስስታም የሆኑት ምእመናን ግን ሳይጠየቁ አይቀሩም ። ድንኳን በሚሰፋበት ሰዓት ብዙዎችን ያድን ነበርና ። ድንኳን በመስፋቱ ጳውሎስን ከማድነቅ የገዛ ስስታችንን መርገም ይገባል ። ወንዶች ለእግዚአብሔር አገልጋዮች አይራሩም ፣ እህል ውኃ ያስፈልጋቸዋል ብለው አያስቡም ። ሴቶች ግን የእናትነት አንጀት ፣ ረቂቁን የማየት ጸጋ አግኝተው ለአገልጋዮች ያስባሉ ። ብዙዎች ሳሉ ኤልያስን የመገበች የሰራፕታዋ መበለት ናት ። ኤልሳዕንም ያሰበችለት የሱነም ሴት ናት ። ጌታችንንም በገንዘባቸው ያገለገሉት ሴቶች ናቸው ። ሐኪሙ ወንጌላዊው ሉቃስ እንዲህ እያለ ያነሣቸዋል፡- “አሥራ ሁለቱም ከእርሱ ጋር ነበሩ ፥ ከክፉዎች መናፍስትና ከደዌም ተፈውሰው የነበሩ አንዳንድ ሴቶች ፤ እነርሱም ሰባት አጋንንት የወጡላት መግደላዊት የምትባል ማርያም ፥ የሄሮድስ አዛዥ የኩዛ ሚስት ዮሐናም ሶስናም ብዙዎች ሌሎችም ሆነው በገንዘባቸው ያገለግሉት ነበር ።” /ሉቃ. 8፡2-3።/ 

ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ከነበራቸው አገልግሎት አንዱ በገንዘባቸው ማገልገል ነው ። ገንዘብ ማገልገያ ነው ። መገልገያ አይደለም ። ገንዘብ ቢኖረን ቁጭ ብለን ስለመብላት እናስባለን ። ገንዘብ ግን ሌላውን የምናበላበት እንጂ የምንበላበት አይደለም ። ብዙ አገልጋዮች ድንኳኑን ሲሰፉ ሰዓቱ እየነጎደባቸው ሙሉ ዘመናቸውን ሰጥተው እግዚአብሔርን ማገልገል አልቻሉም ። ከሥራ በሩጫ ወጥተው የሚያቀርቡልን ማዕድም የችኮላ በመሆኑ አቅም አይኖረውም ። ቃለ እግዚአብሔር ጽሞናና ጸሎት ይፈልጋልና ። ጽሞናና ጸሎት እንዲኖራቸውም እኛም እንድንባረክ አገልጋዮችን በበቂ መመገብ አለብን ። አገልጋዮቿን በቂ ደመወዝ የምትከፍል ቤተ ክርስቲያን ትጉህ አገልጋዮችን ፣ ከአገልግሎት ሰዓታቸው ውጭ የማይልከሰከሱ ሠራዊቶችን ፣ ስጡ ብለው የሚያስተምሩ ብቻ ሳይሆን መስጠት የሚችሉ ቸሮችን ፣ ተገቢውን ርቀትና ክብር ጠብቀው የሚኖሩ አባቶችን ታተርፋለች ። እማሆይ ፌበንም በማዕድ ለማገልገል የማርታን አርአያነት ለመፈጸም ስትከጅል አያት ነበር ። ማርታን ጌታ እንደ ነቀፋት የሚያስቡና የሚሰብኩ ሰዎችን አውቅ ነበርና ትክክል እንዳልሆኑ ገባኝ ። ጌታ በብዙ መጨነቋን እንጂ ተግባሯን  አልነቀፈውም ።

ሐዋርያው ጴጥሮስ ፈገግ አለና፡- “አሳብሽ መልካም ነው ፣ ይህን ስፈጽም ማዕዱን ታቀርቢያለሽ” አላት ። ደግሞም፡- “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር የሣራን በረከት በደስታ መታዘዝን ፣ የርብቃን በረከት ምርቃት ማክበርን ፣ የራሔልን በረከት መወደድን ይስጥሽ” አላት ። እርስዋም ብድግ ብላ ወደ መሬት ለጥ ብላ ቡራኬውን ስትቀበል ከእጅዋ የበላውን አስታውሶ አገልግሎቷን እውቅና ሰጥቶት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ለመባረክ እጆቹን አነሣ ። ሐዋርያው ጳውሎስም ቢቀሙት ቅያሜ እንደሌለበት ቅኔ ከጴጥሮስ ቀምቶ ባረካት ። መመስገን የሚገባቸውን ሳናመሰግን ጊዜ እንዳያልፍብን መጠንቀቅ አለብን የሚል ስሜት ይታይበት ነበር ። በክፉዎች እያዘንን ደጎችን መመረቅ ለምን አልቻልንም  ያለ ይመስለኛል ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ባረካት፡- “በሃና በረከት ተባረኪ ፣ የሰጠሽን ለእርሱ መስጠት ይሁንልሽ ። በአቢግያ በረከት ተባረኪ ፣ የነደደው እሳት ይብረድልሽ ። በድንግል ማርያም በረከት ተባረኪ ፣ የምሥጢር መዝገብ ያድርግሽ” አላት ። እርስዋም ከተሰበረ ልብ የሚወጣውን ልቅሶና የሲቃ ድምፅ እያሰማች አሜን ትል ነበርና ሁላችንም አለቀስን ። በብዙ ጀምራ ብቻዋን የቀረች ፣ ብዙ ሰጥታ ጥቂት እንኳ ያልተቀበለች ፣ ለሁሉ ኖራ ለእርስዋ ግን የኖረላት ያጣች ፣ ስለ ጥሪቷ የምትወደድ ስለ እርስዋ ግን የማትፈቀር ነበረችና አሁን በበረከተ አበው ተካሰች ። የመንፈሳውያን አባቶች ቡራኬ መልካም ምኞት ሳይሆን ከመለኮት ግምጃ ቤት በነጻ የሚሰፈር የእምነት ስጦታ ነው ። ምርቃት ይዞ የወጣ አያልቅበትም ፣ ገንዘብ ይዞ የወጣ ግን ያልቅበታል ። መንፈሳውያን አገልጋዮች ያዘኑባቸውና ያለቀሱባቸው ወዮላቸው ። 

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

እሑድ ሚያዝያ 24 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም