መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » ጸጋ እንዲበዛ

የትምህርቱ ርዕስ | ጸጋ እንዲበዛ

“እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማልና ፥ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል ።” 1ጴጥ. 5፡5
ትሑቱ ሐዋርያ ስለ ትሕትና ሲገልጥ በእውነት ደስ ይላል ። በሽምግልናው ፣ በተቀበለው አደራ እኔ የበላይ ነኝ የሚል ስሜት የሌለው ሐዋርያው ጴጥሮስ በርግጥም ትሑት ነበር ። በአምስተኛው ክፍለ ዘመን “የሮም መንበር ፣ መንበረ ጴጥሮስ ነው ፤ ስለዚህ እኛ ከሁሉ እንበልጣለን” የሚል አስተሳሰብ በመጀመሩ የቤተ ክርስቲያን መከፋፈል ሆነ ። እኔ እበልጣለሁ ፣ እኔ እበልጣለሁ ማለት አንዲቷን ቤተ ክርስቲያን ምዕራብና ምሥራቅ ብሎ ለሁለት ከፈለ ። መንበረ ጴጥሮስ ትሕትና እንደሆነ ማሰብ የፈለግን አይመስልም ። ትሑቱ ጴጥሮስ በጸጋ ላይ ጸጋ ተጨመረለት ። መውደቅንም መነሣትም የሚያውቀው ጴጥሮስ ፣ ኋላ በገባው ሐዋርያ በጳውሎስ ሲገሠጽ ያልከፋው ጴጥሮስ ፣ እንደ ጌታዬ አትስቀሉኝ የቁልቁሊት ስቀሉኝ ብሎ የተማጸነው ጴጥሮስ በርግጥም ትሑት ነው ። የወንጌላዊው ማርቆስ  መምህር እንደሆነ ይታወቃል ። የማርቆስ ወንጌልም የጴጥሮስ ወንጌል ነው ተብሎ ይታመናል ። ምክንያቱም ጴጥሮስ እየነገረው እንዳጻፈው ታምኗልና ። ታዲያ ጴጥሮስ በማርቆስ ወንጌል ውስጥ በጌታ መገሠጹን /ማር. 8፡32/ ፣ ፍርሃቱን /ማር.9፡5/፣ ከንቱ ትምክሕቱን /ማር. 14፡29/ በጸሎት አለመትጋቱን /ማር. 14፡37/፣ ጌታን መካዱን /ማር. 14፡70/ በግልጽ እንዲጻፍ አድርጓል ። ከፈተናዬም ከውድቀቴም ይማሩ የሚል ትሑት ሐዋርያ ነበር ። የዛሬ አገልጋይ ደግሞ ዕለት ዕለት በደመና እንደሚረማመድ የሚናገር ፣ በእያንዳንዱ ነገር ድምፅ ከሰማይ እንደሚሰማ የሚተርክ ፣ ማታ የጀመረው ጸሎት ጠዋት ላይ እንዳለቀ ስሙልኝ ብሎ የሚያውጅ ነው ። ደካሞችን የማያበረቱ አገልጋዮች ያተረፍነው ትሕትናን በመሸጣችን ነው ። የራሳቸውን ዝና ለመካብ የሰውን ዝና የሚያወርዱ ፣ በአደባባይ የሰውን ገመና የሚያወሩ ልክ የለሾችን ያመረትነው ትሕትና በመጥፋቱ ነው ።
ስለ ትሕትና ትምህርቶች እየተሰጡ አይመስሉም ። አብዛኛዎቻችን በትዕቢት ተወጥረናልና ። ጭንቀትና ፍርሃት ሲበዛ ከንቱ ፉከራ ይወለዳል ። ከንቱ ፉከራ የትዕቢት ልጅ ነው ። ስለ ትሕትና ትምህርት ከተሰጠም ምእመናን ፀጥ ብለው እንዲገዙ ሊሆን ይችላል ። በትሕትና መማርና ማስተማር ፣ በትሕትና መምራትና መመራት ግን ለሁሉም አስፈላጊ ነው ። ትሕትና እንደ ልምጥምጥነት መታየቱ አሳዛኝ የዘመናችን አተረጓጎም ነው ። ትሑታንን ካልተቀበልን ትዕቢተኞችንና ዕቡያንን ደግሞም በደም ሰርግ የሰከሩትን መጋበዛችን አይቀርም ። “አህያ ተማልላ ጅብ አወረደች” እንዲሉ ። ትዕቢት እብጠት በመሆኑ መፈንዳቱ ወይም መበጣቱ አይቀርም ። ትዕቢት ነፋስ የተሞላ ፊኛ በመሆኑ መተንፈሱ አይቀርም ። ትዕቢት እንደ ባሎን በመሆኑ ወዴት እንደሚያደርስ አይታወቅም ። ገጣሚው ስለ ትዕቢት ሲናገር እንዲህ ብሏል፡-
በሥልጣን ከፍ ከፍ ፣
በዝና ከፍ ከፍ ፣
ወደ ላይ ከፍ ከፍ ፣
ከፍ ከፍ … ከፍ ከፍ ፣
ከዛ የወደቅህ ዕለት አጥንትህ እንዳይተርፍ ።
ርእሰ መናፍቃን የተባለው ሲሞን መሠርይ ጴጥሮስና ዮሐንስ በተአምራት ወደ ላይ ከፍ ከፍ ብለው ደመናን ሲሳፈሩ እርሱም በምትሐት እንደ እነርሱ እሆናለሁ በማለት ሕዝብ ሰብስቦ ያሳይ ነበር አሉ ። ታዲያ ከላይ ያለው ጴጥሮስ ከሥር እየመጣ ያለውን ሐሳዊ ለማሳፈር “እናማትብበት” ሲል ዮሐንስ ግን “ጴጥሮስ ሆይ አትቸኩል ፣ ከፍ ከፍ ይበል ላወዳደቁ እንዲመች” አለው ይባላል ። ያለ ልክ ከፍ ከፍ ማለት ያለ ልክ ለመውደቅም ነው ። ሆ ሆ ሲበዛ ፣ እገሌ እገሌ ሲባል ፣ ፎቶ በዓይነት ሲለቀቅ ፣ በደማቅ አካባቢ መለስ ቀለስ እያሉ መታየት ዘላለም ለመጨለም ነው ። እስቲ እንታይ ብለው ያለ ጉዳይ ከተማውን ይዞሩ የነበሩ ውብ መኪና አሽከርካሪዎች ዛሬ የት አሉ ? ዓለም ተረኛ እንጂ ቋሚ ወዳጅ የላትም ። ከአዲስ አበባ ለንደን ይገላበጡ የነበሩ ዛሬ እስራት ዕጣቸው ሲሆን እሰይ ከማለት እኔን አውጣኝ ማለት ትልቅ ጸሎት ነው ። ሰዎች ጠባያቸውን ቀይረው ይቀርቧት ይሆናል እንጂ ዓለም እንደሆነ ፈርዖንን ቀይ ባሕር ከታ የተሰናበተች ፣ ናቡከደነጾርን ሣር ያስጋጠች ፣ ቄሣሮችን የተናቁ ያደረገች ፣ እነ ናፖልዮንን የደሴት እስረኛ ያደረገች ናት ። ዓለም ጅምር እንጂ ፍጻሜ የላትም ።
አንቺ ዓለም ፣ አንቺ ዓለም ፤
የጀመረሽ እንጂ የጨረሰሽ የለም ።
ዓለም ውሽማ እንጂ ባል አትሆንም ። ውሽማ ለዛሬ ብቻ መጠቀሚያ የሚያደርግ ነው ። የዓመቱን በዕለት ይጋብዛል ፣ ባል ግን ለነገም አለና በመጠኑ ይሰጣል ። ዓለም ውሽማ መሆኗን የሚዘውራት ሰይጣን ተናግሯል ።ጌታን ሲፈትነው ወድቀህ ብትሰግድልኝ የዓለምን ክብርና ሥልጣን እሰጥሃለሁ ብሎታል ። ለአንድ ስግደት የዓለምን ክብርና ሥልጣን ሁሉ መደበ ። ዓለም በአንደ ጊዜ ገናና ታደርጋለች ። ውሽማ ናትና ከዛሬ በላይ ጊዜ የላትም ። እግዚአብሔር ግን ለዘላለም ስላሰበን ቀስ እያለ ይባርከናል ። ታዲያ ዓለምን የታዘቡ ፣ ከኪሳራቸው የተማሩ እንዲህ አሉ፡-
“በላነው ጠጣነው ፣
ለበስነው አለቀ ፤
ዓለም መች ይለቃል ካላጨማለቀ።”
ትሕትናን የትዕቢት ያህል የሚቃወማት ነገር ቢኖር ግብዝነት ነው ። ግብዝነት የሆኑት አለመሆን ፣ ያልሆኑትን መምሰል ነው ። ግብዝነት ጭንብል ማጥለቅ ነው ። የልጆች ፊልም የሚሠሩ ፣ ደግሞም ሌቦች ጭንብል ይጠቀማሉ ። ሕፃናት በግብዝነት ይታለላሉ ። የተሰረቁ ሰዎችም ማን እንደ ሰረቃቸው ለማወቅ ይቸገራሉ ። ግብዝነት ያታልላልና ሕፃናት ያደርገናል ። የግብዝነት የመጨረሻው ዓላማ ግን እምነታችንን ፣ አቋማችንን ለመስረቅ ነው ። ከሚያገሱ አንበሶች የሚለሰልሱ እባቦች አደገኛ ናቸው ።
“እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማልና ፥ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል ።” ይላል 1ጴጥ. 5፡5 ። ይህ ምክር የተላለፈው ለወጣቶች ነው ። ወጣቶች ለመንፈሳውያን አገልጋዮቻቸው እንዲታዘዙ የተላለፈ ነው ። በወጣትነት ፍላት ወንበር ካልገለበጥሁ የሚሉ ፣ እግዜርን በእምነት ሳይሆን በዱላ ሊያስከብሩ የሚሹ ፣ አማኝነት ሳይሆን ወንድነት የሚሰማቸው ፣ በዘራፍ አድገው በዘራፍ ለማመን የሚከጅሉ ብዙ ምስኪን ወጣቶች አሉ ። ለእነርሱ ዕድሜአቸው የሚረዝምበት መድኃኒት ትሕትና ብቻ ነው ።
አገልጋዮችም በፍቅር እንጂ በኃይል እንዲያስተዳድሩ አልተፈቀደም ። መንፈሳዊ ቤተሰብ የሆነችውን ማኅበረ ምእመናን በትሕትና ማስተዳደር አለባቸው ። ብዙ አገልጋዮች ምእመኑን አሥራት እንደሚያመጣ ደንበኛ ያዩት ይሆናል ። ምእመኑ ግን ልጃቸው መሆኑን መረዳት ያስፈልጋቸዋል ።በትክክል ካገለገልን እግዚአብሔር ለቤቱ በጀቱን አያጓድልም ። ቢጎድልም የምንፈተንበት ርእስ ሊሆን ይችላል ።
ታዲያ ወጣቶች ጸጋ ቢበዛላቸው ይመኛሉ ፣ ይጸልያሉ ። ጸጋ ግን የሚበዛው በትሕትና ብቻ ነው ። ትዕቢት ያለውን ጸጋ ይነሣል እንጂ አይጨምርም ።
የሁላችን ተስፋ ፣ ልባችንን በቃልህ የደገፍህ ፣ አለማወቃችንን ያገዝህ እግዚአብሔር ሆይ ስምህ ቡሩክ ቅዱስ ይሁን ። ጌታ ሆይ በራሳችን የምናበጀው መስሎን በብዙ መንገድ ባከንን ። እባክህን በትሕትና ጌጠኛ ልጆችህ አድርገን ። መልካችን ጠፍቶ ክርስትና ጣዕም አልባ ሁኖብናልና ትሑት አድርገን ። ጌታ ሆይ እንኳን ትሑት ልንሆን ትሑታንን እየናቅን ነውና ከዚህ ሚዛን ካጣ ማንነት አድነን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 16
ግንቦት 15 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም