የትምህርቱ ርዕስ | ፈቃደ እግዚአብሔር

“በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን ።” ኤፌ. 1 ፡ 5 ።

አንድ የቆየ ዝማሬ ከነዜማው ትዝ ይለኛል ።

ማንም ሳያስገድድ በራስ ፍላጎት ፣
ምን ዓይነት ፍቅር ነው ራስን መስጠት ?!
ወየው ፣ ወየው መቱት ያን መድኅን ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ ይለዋል ። እኛን ለመውደድ ፣ ለእኛ ለመሞት ፣ ራሱን ለመስጠት ያስገደደው የእኛም ቁምነገር ፣ የፈጣሪነትም ግዳጅ አልነበረም ። መፍጠር የእርሱ ሥልጣን ሁኖ እንደ ፈጠረ ፣ መፍረድም ሥልጣኑ ነውና ፈርዶ መቅጣት ይችል ነበር ። እርሱ ግን ፍትሑን ሙሉ አድርጎ ፣ ፍቅሩንም ገልጦ አዳነን ። ቃልን ለነቢያት ቢሰጥ አምላክነቱ ነው ፤ እርሱ ግን ንስሐ ግቡ የሚል ሰባኪ ሁኖ መጣ ። መሥዋዕትን ተቀብሎ ለዓለም ምሕረት ቢልክ የሚገባው ትልቅነቱ ነው ። እርሱ ግን መሥዋዕቱም ራሱ ፣ አሳራጊ ካህንም ራሱ ሁኖ መጣ ። በዙፋኑ ሁኖ ኃይልና ብርታትን ቢሰጥ የማይጠረጠር አሠራሩ ነው ። እርሱ ግን የእኛን መስቀል ተሸክሞ ደከመ ። ንስሐ ግቡ እያለ ኃጢአታችንን በመስቀል ላይ ተሸከመ ። መሥዋዕትን እያቀረበ ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ ብሎ ሰጠን ። አዳም በበደለኛነቱ ፣ ጴጥሮስም በወዳጅነቱ መስቀሉን ያግዙት ዘንድ አልፈቀደም ፣ ራሱ መስቀሉን ተሸክሞ ወደ ቀራንዮ ኮረብታ ወጣ ። ይህ ሁሉ የሆነው እንደ ወደደ ነው ።

ቅዱስ ኤፍሬም፡- “እስመ በፈቃዱ ወበሥምረተ አቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ መጽአ ወአድኃነነ” ይላል ። እግዚአብሔር አንድ ፈቃድ አለው ። ፈቃዱም በጎና ምንም አስገዳጅ ኃይል የሌለበት ነው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣው በአንዲት የሥላሴ ፈቃድ ነው ። አብ ለራሱ ልብ ሁኖ የወልድና የመንፈስ ቅዱስ ማሰቢያቸው ፣ ማቀጃቸው ፣ መወሰኛቸው ነው ። የሥላሴ አካላት ሦስት ቢሆኑም እያንዳንዱ አካል የራሱ ልብ ፣ ቃልና እስትንፋስ አለው አይባልም ። ይህ ሦስት ፈቃድን ፣ ሦስት ግብርንና ሦስት ህልውናን ያመጣል ። ሥላሴ በኩነታት ሦስት ቢሆኑም በኩነታት መገናዘብም እየተዋሐዱ ፣ አንድ ፈቃድ ፣ አንድ ተግባር ፣ አንድ ሕይወት አላቸው ይባላል ። በዚህም አንዱ አካል ያለ ሌላኛው አካል አልኖረም ፤ አይኖርምም ።

እግዚአብሔር ፈቃዱ በጎ ነው ተብሏል ። ከአፍቃሪነቱና ከቅዱስነቱ የሚወጣው ፈቃዱ በጎ ነው ። ይህ በጎ ፈቃድም ዘመን የወለደው ፣ ሁኔታ ያመጣው ሳይሆን ከአካሉና ከባሕርይው ጋር ለዘላለም የኖረ ነው ። ሴቶች ልጅ ሁነው ያድጋሉ በዚህም ብላቴና ይባላሉ ። ለአቅመ ሔዋን ሲደርሱም ደናግላን የሚል መጠሪያ ያገኛሉ ። አብረዋቸው የተወለዱ ካሉም እኅት አበባ የሚል መጠሪያ ይቀበላሉ ። ሲያገቡ ሚስት ይባላሉ ። ሲወልዱ እናት ሁነው አንጀተ ስስ ይሆናሉ ። እግዚአብሔር ግን በጎ ፈቃድና ፍቅርን የመላእክትና የሰው መፈጠር አላመጣለትም ። እርሱ በበጎ ፈቃዱ ፈጠረን እንጂ ። የእግዚአብሔር ፈቃድ በጎ መሆኑን በነቢዩ ተናግሯዋል ። “ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም” ኤር. 29፡11። ይህ ቃል የተላከው በባቢሎን በምርኮ አገር ኑሮ ለጀመሩት እስራኤላውያን ነው ። ወደ አገራቸው ቶሎ የሚመለሱ መስሏቸው ነበርና ተረጋግተው እንዲቀመጡ የተላከ መልእክት ነው ። በግዞትም ፣ በቅጣትም ውስጥ እግዚብሔር ለእኛ ያለውን በጎ ፈቃዱን አይለውጥም ። እርሱ በቀል የሆነ ቅጣት ፣ ማሳደድ የሆነ ፍርድ የለውም ። እርሱ በምርኮም ፣ እርሱ በኃጢአታችን ውጤት ውስጥ ስናልፍም በጎ አሳብ አለው ።

የሰው ፈቃድ ሥጋ ፣ ዓለምና ሰይጣን የሚባሉ ፈታኞች ስለሚጫኑት በጎነት ያጣል ። ቁሳዊነት ላይ እንዲመሠረት ሥጋ ፣ ብልጭልጭነት ላይ እንዲመሠረት ዓለም ፣ ክህደት ላይ እንዲመሠረት ሰይጣን ይጫኑታልና የሰው ፈቃድ በጎ ላይሆን ይችላል ። ቁሳዊነት ሲጫን ስግብግብነት ፣ በቃኝ አለማለት ፣ ነግዶ አትርፎ አለማመስገን ፣ ሌላው ሞቶ እኔ ልኑር ባይነት ይከሰታል ። ይህ ስግብግብነት አገርን ያፈርሳል ። ሁሉ ካልተደጋገፈ ፣ እኩል ካልተጠቀመ አገር እየተናጠ ይመጣል ። ባለጠጋው ድሀውን እንደ ስጋቱ ፣ ድሀው ባለጠጋውን እንደ ጠላቱ ያያል ። ተረጋግቶ ለመብላት የጎረቤትን ረሀብ ማስታገሥ ያስፈልጋል ።

ብልጭልጭነት ሲበዛ የላይ ማንነት እየነገሠ ፣ ውስጣዊ ሰውነት እየወደቀ ይመጣል ። ሰዎች ለፀጉራቸው እንጂ ለቅንነታቸው ፣ ለፊታቸው እንጂ ለልባቸው የማይጨነቁ ይሆናሉ ። የሰው ግንኙነትም የላይ የላይ የጥርስ ጨዋታ ያለበት ይሆናል ። ብልጭልጭነትም ሰውን የተዋበ ሬሳ ፣ ተንቀሳቃሽ ሙት ያደርገዋል ። ክህደትም እግዚአብሔርን በመካድ ይጀምራል ። ከሀዲ የሰውን ዋጋ አያውቅም ። በሰው ሞትም ይነግዳል ። ከሀዲ ቀጥሎ ወላጆቹን ይክዳል ። መርዳት እየተሳነው ይመጣል ። መልካም ያደረጉለትንም ከማመስገን ግዳጃቸው እንደሆነ ያስባል ። የራሱን የግሉ ፣ የሌላውን የጋራው እንደሆነ ያስባል ። ወይ እምነት ወይ ይሉኝታ ፣ ወይ ሰብአዊነት ወይ መንፈሳዊነት የሌለው የሚለሰልስ ቋጥኝ ይሆናል ። ለመስጠት ስንኩል ፣ ለመቀበል ስልጡን ይሆናል ። ሁሉ ለእኔ ይኑር ባይነት ፣ በልቶ ካጅነት ፣ አገር ሻጭነት ይወለዳል ። ይህ የሰይጣን ቀጥተኛ ፈተና የሚወልደው ነው።

የሰው ፈቃድ ይህ ሁሉ ፈተና ያለበት ነው ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ግን በጎ ነው ። ዘላለሙን ያየልን ፣ ውስጣዊ ማንነታችን ላይ ያተኮረ ፣ በአምልኮት የተቃኘ ሕይወት እንዲኖረን የሚሻ ነው ። ይህ በጎ ፈቃድ የመደበልን እንደ አቤል ሰማዕትነት ከሆነ ሳንወልድ ስማችን ሲጠራ ይኖራል ። እንደ ኖኅ ዓለም ሁሉ ጠፍቶ ብቻ መትረፍ ከሆነ በአምላክ ፍትሕ ልብ ያርፋል ። ከተማ ተቃጥሎ ፣ ቤት አልባ ሁኖ እንደ ሎጥ መውጣት ከሆነ ያለኝና የሚኖረኝ እግዚአብሔር ብቻ ነው ያሰኛል ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /9

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 11 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም