መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ፍርድህ የጠራ

የትምህርቱ ርዕስ | ፍርድህ የጠራ

እንደ ውቅያኖስ ምሕረትህ የሰፋ ፣ እንደ ባሕር አሠራርህ የጠለቀ ፣ እንደ ምንጭ ፍርድህ የጠራ ፣ እንደ ወንዝ ርቀህ የምትሄድ ፤ የመልክን ቀለም ፣ የባለጠጎችን ሽቱ ፣ የጎበዞችን ቁመና አይተህ የማትመርጥ ፤ በልቡ ጉልበት የሰገደልህን የምትወድድ ፤ በመቅደስህ የቅኔ ማዕበል ፣ በማደሪያህ የምስጋና ጅረት የሚፈስልህ ፤ እኔ አንተን ብሆን የማልወደውን እኔን የወደድህ ምስጋና ይገባሃል ። ዛሬ እንደ ትላንት እየመሰለኝ ፣ መምሸት መንጋቱም ግዴታው እንደሆነ እያሰብሁ ፣ ክረምትና በጋ ሲፈራረቅ ልማዱ ነው እያልኩኝ ያንተን ስጦታ ማቃለሌ ፣ አዲሱን አሮጌ ማድረጌ ከቶ ለምንድነው ? የዘመን ክፋት ደግነትህን ፣ ማለቂያ ያጣው የሰው ተንኮል አምላክነትህን ፣ ድንበር ገፊ ድሀ አጥፊዎች ፈራጅነትህን የሚያስረሱኝ እስከ መቼ ነው ? የጥበበኞች ጥበብ በፊትህ ሞኝነት ፣ የኃያላን ጉልበትም ድካም ነው ። ጥበበኛውን በመናኛ ነገር ታስጨንቀዋለህ ፣ ኃያል ነኝ ያለውንም በአንድ ቀን ትኩሳት ታንበረክከዋለህ ። አንተ በፍጡር ፊት ግርማዊ ነህ ፣ ባንተ ፊት ግርማዊ የሆነ ማንም የለም ። የአስደንጋጮች ማስደንገጥ በአንተ ዘንድ ከንቱ ነው ። የጨካኞች ፉከራና ዘመቻ እንደ ኢምንት ነው ። ያላንተ የቆነጁ የሬሳ ውቦች ናቸው ። በራስህ የታወቅህ አንተ ነህ ። ብናውቅህ ራሳችንን እናውቀው ነበር ። ባናውቅህ ግን አንተ ራስህን ታውቃለህ ። የለህም ሲሉህ አትሰጋም ፣ መቼም አትታጣምና ። ይህ ሁሉ ክብር ያለህ የእኔ አምላክ ነህ ። ምስጋና ይገባሃል ።
ያለ ቃልህ ዕውር ነኝ ። ያለ መሪነትህ እግሬም አያደርሰኝ ። ልቤን ካለፈወስከው አፌ የምስጋና በረሃ ነው ። ጆሮዬን ካልዳሰስከው የእሾህ መከማቻ ነው ። ያየሁትን መውረስ አሁንስ ይቅርብኝ ። ያየህልኝን አውርሰኝ ። ከአገር አስወጥተህ አገር የምትሰጥ ፣ ወዳጅ ወስደህ ወዳጅ የምትሆን ነህ ። ሳሙኤል ልቤ ኤልያብን ሲመርጥ ልበ ሥላሴ ግን ዳዊትን ምረጥልኝ ። ባለ ቁመናው ቀርቶ ባለ በገናው ይሁንልኝ ። መልክ ያለው ሳይሆን እግዜር ያለው ይሰጠኝ ። ቅቤ አፍ ያለው ሳይሆን ዝማሬ አፍላቂው ይደረግልኝ ። የአሳብ መንገደኛ የእግር እስረኛ ነኝ ። በአሳቤ ስንቱ ገደልኩ ፣ ሁሉን ጨርሼ እኔ ብቻ ቀረሁ ። ዓለምን እንኳን ለእኔ አልሰጠሃት ። ዓለምን በእፍኝህ የያዝሃት አንተ አዋቂ ነህ ። አንተ የሕይወት ግብ ሁነኝ ። አንደበቴን እንደ ተቀደሰ ምንጭ አጣፍጥልኝ ፣ በልቤ ከተማ አንተ ንገሥ ። ጆሮዬም ናፍቆቷ አንተ ብቻ ሁንላት ። የሰማሁትን ሳልፈይደው ሌላ መስማት ያምረኛል ።
አምላኬ እግዚአብሔር ሆይ ለለመኑህ ስጣቸው ። የሻቱትን የልባቸውን ምኞት ፈጽምላቸው ። የሚያንኳኩ ደጅህ ላይ እንዳይቀሩ ክፈትላቸው ። ከዘመን ትኩሳት አንተ ጠልላቸው ። አባራሪውን አባርላቸው ። የተሳሳተውን መንገድ የምንጠቁም ነንና መንገድ መሪ ሁነህ ትውልድን አድን ። ወደ አንተ መጥቶ በባዶ የሚመለስ አይኑር ። ስምህን ጠርቶ ማንም አይፈር ። በልቅሶ የዘራ በደስታ ይጨድ ። የሆዱን የነገረህ በአደባባይ ልመናው ይመለስለት ። ከቀን ወራሪ ፣ ከሌሊት ሰባሪ ማዳን ትችልበታለህ ። እኔ ያላንተ የተራቆትኩ ነኝ ። እንኳን በመዘናጋቴ በመንቃቴም የተኛሁ ነኝ ። ንቁ ሆይ ጠብቀኝ ። በሳጥኔ ያስቀመጥሁህ ወርቄ አንተ ነህ ። ለችግሬ ቀኔ ያልኩህ አማኑኤል ሆይ ክበር ። እሬትነቱን በማር የምልሰው ዓለም ሲያጓጓኝ ይገርመኛል ። ደሊላ ዓለም የልቤን ምሥጢር አስጨርሳ እንዳትገድለኝ ወልድ ሆይ አንተ ሰውረኝ ። በልዑልነትህ እየፈራሁህ ፣ በዝምድናህ እያቀረብሁህ የሠራኸው ሲፈርስ ለምን ዝም አልክ እልሃለሁ ። ዛሬም ቅኑ እየፈረሰ ፣ ምስኪኑ እየተደቆሰ ነው ። የኃያላኑን በር አንተ ክፈት ። ጽኑዓን ነን የሚሉትን በክብርህ መልስ ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ ለሚሆን ክብር ምስጋና ይገባል ፤ ከልባችን እስከ አርያም ፣ በማይፈጸም ዘመን ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 17
መጋቢት 18 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም