የትምህርቱ ርዕስ | ጊዜ ይመጣል

“ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል” /ዮሐ. 4፥21/ ።
ጌታችን ሳምራዊቷ ሴት የሕይወትን ውኃ ፈልጋለችና ለንስሐ ጋበዛት። ሳምራዊቷ ሴት ግን ወደ እርስዋ የመጣውን ቀስት አቅጣጫውን አዞረችው ። ራስን ለማየት ፈተና የሆነውን የሃይማኖት ክርክር አነሣች ። በንስሐ የሚያልቀውን ርእስ ወደማያባራው የሃይማኖት ክርክር ውስጥ መክተት ከጥንት እስከ ዛሬ የሰዎች ጠባይ ነው ። አንተ ከአባታችን ከያዕቆብ ትበልጣለህን ? የሚለው መስቀለኛ ጥያቄ ወደ ሌላ ጥያቄ ተለወጠ ። አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰግደዋል ፣ እናንተ ደግሞ ስግደት በኢየሩሳሌም ነው ትላላችሁ በማለት ሁለተኛውን መስቀለኛ ጥያቄ አቀረበች ። ከዚህች ሴት አንደበት አባቶቻችን የሚለው ቃል አይጠፋም ። አባቶችን የሚመስል ሕይወት ግን አልነበራትም ። ለመለያየትና ለመከፋፋት አባቶች የሚል ድምፅ ታሰማለች ። አባቶቻችን እነ አብርሃም በዚህ ተራራ ሰግደዋል እናንተ ግን ስግደት በኢየሩሳሌም ነው ትላላችሁ አለችው ። ስግደት በገሪዛን ተራራ ብቻ መሆን እንዳለበት አምናለች ። ምክንያቱም አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ ብላለችና ። ወስና ትጠይቀዋለች ። መልሱን አውቃ ያቀረበችው ጥያቄ መፈተኛ ነበር ። የሴቲቱ ጭንቀት ግን እኔ ራሴ ላስበው የማልፈልገውን የእኔን ሕይወት አታስበው የሚል ነው ። ሥራ አላሠራ ለሚል ሕጻን ልጅ የጨዋታ ካርታ ሰጥተው እንደሚገላገሉት ፣ ለንስሐ የመጣውን ድምፅም በሃይማኖት ክርክር በመለወጥ ለመገላገል ፈለገች ። ክፉ ሴት ስለነበረች አይደለም ። ሕይወቷን ማሰብ ስለማትፈልግ ነው ። እኔ አልድንም ብላ ስለተቀመጠች መምህርንም ነቢይንም ማድከም አትፈልግም ። በራሷ ተስፋ ስለቆረጠች ተስፋ በሚያደርጉባት ትስቃለች ።
ጌታችን ግን ለምታቀርብለት የመገላገያ ጥያቄ ይመልስ የነበረው ውይይቱን በሚያስቀጥል ንግግር ነው ። አንድ ታማሚ ሁለተኛውን ጉርሻ አልቀበልም ብሎ ሲቆጣ አስታማሚው ቀስ አድርጎ አባብሎ ይሰጠዋል እንጂ የራሱ ጉዳይ ብሎ ጥሎት አይሄድም ። ጌታችን ኃጢአተኞችን እንደ በሽተኛ ያያቸው ነበር ። የሚራራላቸውም በፍቅር ዓይን ስላያቸው ነው ። የእግዚአብሔር መንግሥት በዚህ መንገድ ቢሰበክ ኑሮ ስንቱን ሰው ባሳረፍነው ነበር ። ጌታችን ስግደት በገሪዛን ነው ወይስ በኢየሩሳሌም የሚለውን ጥያቄ የመለሰው በልዩ ጥበብና ግልጽነት ነው ። በኢየሩሳሌም ነው ቢላት ጥላው ትሄድ ነበር ። ጌታችን ጥለው ለመሄድ ለሚፈልጉ ምስኪኖች መንገድ አይሰጥም ። ሆድ ለባሰው ማጭድ አታውሰው ይባላል ። ለብዙ መቶ ዓመታት የቆየው ክርክር የስግደቱ ማዕከል ኢየሩሳሌም ነው ፣ አይ አይደለም ደብረ ገሪዛን የሚል ነው ። እግዚአብሔርን የሚያከብረው ግን ከቦታው በላይ የልጆቹ አንድነት ነው ። በዘር ፣ በሃይማኖት ፣ በጾታ ተከፋፍለው እናመልክሃለን ቢሉት እግዚአብሔር አይደሰትም ። ልጆቹ ሁሉ መሥዋዕታቸውን ፣ ጸሎታቸውንና ምስጋናቸውን ቆም አድርገው ንስሐ ቢገቡ ፣ እርስ በርስ ቢታረቁ እግዚአብሔር ይደሰታል ። ፍቅር የሌለበት አገልግሎት ወደ ተዘጋ ሰማይ የሚደረግ ግስጋሴ ነው ። እየዘመርን ደስ የማይለን ፣ እየጸለይን የማንቀበለው ፣ እየተማርን የማንለወጠው ፍቅርንና ይቅርታን ስለጣልን ነው ።
“ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል” አላት /ዮሐ. 4፥21/ ። ለአብ ለምን አለ ? እርሱስ ከአብ ጋር አምልኮ ተቀባይ አይደለም ወይ ? ቢሉ የሴቲቱን አእምሮ ለመጠበቅ ነው ። ስግደት ለእርሱ እንደሚገባ ቢነግራት ገና ነቢይ ነው ብላ ላመነች ሴት ብን የሚያደርግ ነው ። የሚገርመው በደብረ ገሪዛንም በኢየሩሳሌምም ለአብ እንደሚሰግዱ ጌታ ተናገረ ። ለሁለቱም እውቅና ሰጠ ። በደብረ ገሪዛን መሥዋዕቱ ሲያርግ ፣  በኢየሩሳሌምም መሥዋዕቱ ሲያርግ አብ በመገረም ያየዋል ። ምክንያቱም ሁለት ልጆች የወለደ አንድ አባት ሁለት ልጆቹ በየራሳቸው ስጦታ ይዘውለት ሲመጡ ሁለቱ ግን ተኳርፈው ደግሞም ለሞት ሲፈላለጉ ያያል ። ከስጦታችሁ በላይ መጀመሪያ ታረቁልኝ አይልም ወይ ? ጌታችን ለአብ በሚል ቃል መናገሩ ድንቅ ነው ። እግዚአብሔር የሁለት ልጆች አባት መሆኑን በጠፋው ልጅ ታሪክም እናያለን ። በቤት የሚያቆስልና በደጀ ፋንኖ የወጣ ሁለት ልጆች ያሉት አባት ነው ። ከአገልግሎት በፊት እርሱን ማወቅን ፣ ከመሥዋዕት በፊት መፋቀርን ይፈልጋል ። ምክንያቱም እርሱ አብ ወይም አባት ነውና ። እግዚአብሔር የሌለበት ለእግዚአብሔር መቅናት ከባድ ነው ። እግዚአብሔርን የራስ ዓመፅ ተባባሪ ማድረግ ነውና በደሉ ከፍ ያለ ነው ። በራስ ስም ከሚሠራ የዓለማውያን ኃጢአት በእግዚአብሔር ስም የሚሠራ የአማንያን ኃጢአት ከባድ ነው ።
እግዚአብሔር የደብረ ገሪዛንና የኢየሩሳሌምን እውቅና የሚያነሣበት ጊዜ እንደ ቀረበ ጌታችን ተናገረ ። ምክንያቱም እግዚአብሔር የሚፈልገው አምልኮ ቢያንስ ሦስት ነገሮች ያሉት ነው ።
1-  እውቀት
2-  መመሰጥ
3-  እውነት
ጌታችን ትልቅ ትንቢት ነገራት ። ከአርባ ዓመት በኋላም ይህ ትንቢት ተፈጸመ ። መላው እስራኤል በሮማውያን ተደመሰሰ ። ደብረ ገሪዛንም ሆነ የኢየሩሳሌም መቅደስ ወደመ ። ይልቁንም ደብረ ገሪዛን በአይሁድ ወድሞ ነበርና የኢየሩሳሌም መቅደስ ግን በሮማውያን ተደመሰሰ ። የመቅደሱ እያንዳንዱ ድንጋይ ተለቅሞም በደቡብ ኢየሩሳሌም ባለው ሸለቆ ተወረወረ ። ጌታችን ይህን የሚያህል ምሥጢር ለአንዲት ሴት መናገሩ ይገርማል ። የሕዝብ ተወካይ ለነበረው ለኒቆዲሞስ ያልነገረውን ለዚህች ሴት መንገሩ ይገርማል ። ለኒቆዲሞስ ግላዊ ሕይወቱን በሚመለከት ተናገረ ፣ ለዚህች ሴት ግን ብሔራዊና ሃይማኖታዊ እንዲሁም መጻኢ ጉዳዮችን ነገራት ። ለኒቆዲሞስ ብሔራዊ ጉዳይን ለዚህች ሴት ግላዊ ሕይወቷን ቢነግር መልካም ነበር ። ይህ የእኛ ቀመር ነው ። እግዚአብሔር ግን መንገዱ ከሰው መንገድ የተለየ ነው ።
ስግደት የሚለው ቃል አምልኮተ እግዚአብሔር ማለት ነው ። ስግደት የሰውን ሥጋ ፣ ነፍስ እንዲሁም መንፈስ የሚያስተባብር ነው ። ትልቅ የአምልኮ መገለጫም ነው ። ለእግዚአብሔር የመዋረድ ፣ ክብርን የመጣል ምልክት ነው ። ስለዚህ አምልኮተ እግዚአብሔር ስግደት በሚል ቃል ሊጠራ ይችላል ። ጌታችንም ለእግዚአብሔር የምትጸልዩበት ፣ የምትዘምሩበት ፣ መሥዋዕት የምታቀርቡበት ከማለት የምትሰግዱበት ብሏል ። ይህ የሚያሳየን በስግደት ውስጥ ፡-
–     ስብሐት /ስለ ህልውናው ስለ ጌትነቱ ክብር መስጠት/ ፣
–     ውዳሴ /ስለ ባሕርዩ ስለ ተግባሩ አድናቆት/ ፣
–     አኮቴት /ስለተደረገልን ነገር ምስጋና/ ፣
–     አስተብቊዖት /ለወደፊት እንዲፈጽምልን ልመና/ ስላለ ነው ።
ስግደት ለሰገደው ልብ መግለጫ ሲሆን ብዙ ኃይል አለው ። ጌታችን አምልኮን ስግደት በሚል ቃል ገለጠው ። ሰግደን የምናናግረው እግዚአብሔርን በመሆኑ ስግደት ለእግዚአብሔር አምላክነት እውቅና የምንሰጥበትም ነው ።
“ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል” /ዮሐ. 4፥21/ ። አዎ ጊዜ ይመጣል ። የተጣላንበት ፣ የተባላንበት ፣ የተገዳደልንበት ነገር ሁሉ የሚያበቃበት ፤ ራሳችንን የምንታዘብበት ጊዜ ይመጣል ። ዛሬ የሚያጸጽቱን ነገሮች ትላንት ላይ ልክ የነበርንባቸው ነገሮች ናቸው ። ዛሬ ላይ ልክ መስሎን ያደረግናቸው ነገሮች ነገ ላይ እናዝንባቸዋለን ። ጊዜ ይመጣል ። የቆመም የሚወድቅበት ፣ የወደቀም የሚቆምበት ጊዜ ይመጣል ። ትላንት እየተሳደቡ ይሰጡ የነበሩ ዛሬ ለምነው ሲያጡ አይተናል ። ጊዜ ይመጣል ። ያለው እንደሌለው የሌለው እንዳለው የሚሆንበት ጊዜ ይመጣል ። ጊዜ ያልነውም እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ሰው የወሰነለት የምሕረት ወራት ነው። ሀብቱ የከበደውን መንጠቅም ምሕረት ነው ። ሥልጣን የከበደውን ማሳረፍም ምሕረት ነው ። እግዚአብሔር ጽዋን የሚያለዋውጥበት ጊዜ ይመጣል ። መስቀል አሸካሚዎች መስቀል የሚሸከሙበት ፣ እርጥብ መስቀል ያሸከሙ ደረቅ መስቀል የሚሸከሙበት ጊዜ ይመጣል ። በጅራፍ የገረፉ በጊንጥ የሚገረፉበት ፣ ነፋስ የዘሩ አውሎ ነፋስ የሚያጭዱበት ጊዜ ይመጣል ። ምርቱ ከተዘራው በላይ ነውና ።
ጌታ ኢየሱስ ሳምራዊቷን ሴት ፡- “እመኚኝ” አላት ። ሰዎች ማመን የሚቸግራቸው ጊዜ እንደሚመጣ ነውና ። አሁን ያለው ሙግትና ክርክር ዘላለም የሚኖር ይመስላቸዋል ። እንዳለ የሚኖር እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ያለፈው የነበረ እስከማይመስል አሻራ እንኳ ሳይተው ሂዷል ። ያለውም የማይጠፋ እስኪመስል ያስጨንቃል ። ያለው የሚያልፈው እንዳለፈው ጊዜ ነው ። ሁሉም ተረት ለመሆን ይቸኩላል ። ከዘመናት በፊት የነበረው የታላላቅ ጀግኖችና የጦርነት ውሎአቸው ዛሬ የሕጻናት መጫወቻ ሁኗል ። የሚታየው ወደ አለመታየት ይለወጣል ። የማይታየው ከታየ ፣ የታየውም የማይታይ ይሆናል ። ዛሬ የሚንጎማለለው ሰው ከልደቱ በፊት የማይታይ ነበረ ። አሁን ታይቷል ። ነገ ደግሞ የማይታይ ይሆናል ። ጊዜ ይመጣልና ተጽናኑ ። እግዚአብሔር ለሁሉ ሰው ጊዜ አዘጋጅቷል ። ሳትሰለቹ በበጎ ሥራ ጽኑ ። ብድር ከፋዩ ይመጣል ። አንድ የሰሜን ኢትዮጵያ አባባል አለ ፡- “ክፉዎች ይጕዱህ እንጂ ክፉ አያድርጉህ።”
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም