መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » አባትነት

የትምህርቱ ርዕስ | አባትነት

 

“ላልጠየቁኝ ተገለጥሁ ፥ ላልፈለጉኝም ተገኘሁ በስሜም ያልተጠራውን ሕዝብ፡- እነሆኝ ፥  እነሆኝ አልሁት ።” ኢሳ. 65 ፡ 1 ።

ሰፈሩ ለድሮ በቀበሌው ስም ይጠራ ነበር ። በ13 እና በ14 ቀበሌ መካከል ያለው መንገድ ምቹ ያልነበረ ፣ ለማየትም የሚማርክ አልነበረም ። ከመንገዱ ቤቶቹ የተሻሉ ነበሩ ። ዘመን ሰለጠነና እንደ ቅቤ ያለ መንገድ ተሠራ ። መንገዱ ሲሠራ የገባው ሥልጣኔ ብቻ ሳይሆን ኃጢአትም ሆነ ። ታዲያ ሰፈሩን “ቺቺንያ” ብለው ሰየሙት ። ትርጉሙን ብጠይቅ በቺቺንያ ጦርነት ሕፃናት ይሳተፉ ነበርና በዚህም ሰፈር ሕፃናት ለዝሙት ንግድ ተላልፈው ተሰጥተዋል ፤ ስለዚህ ሰፈሩ “ቺቺንያ” ተባለ የሚል መልስ አግኝቻለሁ ። ያንን አካባቢ የማውቀው በ1986 ዓ.ም. ጀምሮ ነው ። እግዚአብሔርን የሚወዱ ፣ ሰውንም የሚወዱ ሰዎች እንደ ነበሩበት አስታውሳለሁ ። አቅም የነበራቸው ወጣቶችም ነበሩበት ። ታዲያ ከሁለት ቀን በፊት በዚያ “ቺቺንያ” ተብሎ በተጠራው ሰፈር ጎዳና ላይ በመኪና ሳልፍ ድንገት አንድ አባት ሕፃን ልጅ ይዞ መልሶ ደግሞ እያቀፈ ቀጥሎ እያወረደ በቅጽበት አየሁ ። አባቱን ሳየው ዕድሜው 35 ዓመት ቢሆነውም ያለ ጊዜው ግን አርጅቷል ። መልኩ ክልስ ይመስላል ። መልሶ ደግሞ ጠቍሯል ። መለስ ብዬ ልጁን ሳየው ሕፃኑ ጠይም ነው ። በጠይምነት ጀምሮ በጠይምነት የቀጠለ የ6 ዓመት ልጅ ቢሆን ነው ። አባቱን ኑሮ ያጠቆረው መሆኑን አረጋግጬ ልጁን መልሼ ያየሁት ምናልባት የእኛው አየር ንብረት ያጠቆረው ሶርያዊ ይሆን ብዬ ነው ። በቅጽበት የሰማሁት የአባትና የልጅ ንግግር ግን ኢትዮጵያዊ እንደሆኑ መሰከረልኝ ። ያ አባት በዓይኔ በቅጽበት ውስጥ ገባ ። የለበሰው ሙሉ ልብስ ውድ ልብስ ነው ። ነገር ግን ከወለቀ ብዙ ጊዜው ሆኖ ደክርቷል ። ያ አባት የሆነው ወጣት መልኩ በቀይ ጀምሮ እንደነበር እርግጠኛ ነኝ ። አሁን ግን ጠይም ቢሆን ሂደት ነበር ። የቀይ ዳማ ቢሆንም በቅላትና በጠይምነት መካከል ነው ። ነገር ግን አመድማና መግለጥ የማይቻል መልክ ይዟል ። እስቲ የውኃን መልክ ግለጹልኝ ፣ ያ ወጣትና አባትም እንዲሁ ነው ። ኑሮ በደንብ እንደ ጎዳው ያስታውቃል ። ጥርሶቹ ተጎድተዋል ፣ ለመቦረሽም እድል አላገኙም ። ጫማው አዘንብሏል ። አሁን ያለው ሀብት ፍቅር ብቻ ይመስላል ። ልጁ ሲከብደው ያወርደዋል ፣ መልሶ ፍቅሩ አላስችል ብሎት ይሸከመዋል ። ልጁ የጫጨ ቢሆንም ለአቅመ ደካማው ወጣት አባት ግን ከባድ ነበረ ። አካሉ የተሟላ አባት ነው ፣ አቅም ግን ጥሎት ከሄደ የሰነበተ ይመስላል ። ማናልባት ሱስ ይሆናል ካላችሁ እኔ ግን አልመሰለኝም ። የአባቱ አቅም እንደ ተዳከመ ልጁ አያውቅም ። ልጁ የሚያውቀው አባቱ አፍቃሪና ኃያል መሆኑን ብቻ ነው ። አዎ አባቱ አፍቃሪ ነው ፣ ግን በጊዜ ደክሞታል ። በዕድሜ ሳይሆን በኑሮ አርጅቷል ። ያንን አባት ለማወቅ ቤቱን ማየት አያስፈልግም ፣ ቁመናው ቤቱን ያሳያል ። 

መገመት መልካም ነው ። ይህ የተዋበ አባት በውበት ጀምሮ በመወየም እየደመደመ ነው ። በቅላት የሚያውቀው ሰው ብዙ ይኖራል ። አሁን ግን አመድማም ከሰልማም ለመባል አስቸጋሪ ሁኗል ። ሳየው አዘንኩለት ። ማግኘትና ማጣትን የሚያውቅ ሰው ፣ በልዑልነት ጀምሮ የባሪያን መልክ እንኳ ያጣ ወገን ብቻ የሚያውቀው ሰው ነው ። መኪናው ለቅጽበት ቆም ያለው ከፊት ለፊቱ ጭንቅንቅ ስለነበረ ነው ። ይህን ሰው ያየሁትም የሰማሁትም ከአንድ ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ነው ። ልጁን ቁልቁል እያየ ምነው በኖረኝ ? የሚል ስሜት ይታይበታል ። ልጁንም ሳብ አድርጎ ወደ ላይ ካወጣው በኋላ አቀፈው ። ልጁም ከፍ ያለው ማማ ላይ ሲወጣ ዓይኖቹ ማዶ ላይ አሻግረው የተዋቡ ጫማዎች የሚሸጥበት ሱቅ ላይ አረፉ ። ውድ ቤት እንደሆነ ሱቁም ጫማውም ይናገራል ። ልጁ ግን፡- “አባ” አለው ። አባትም እንደ ልጁ ጮክ ብሎ ሳይሆን ዝቅ አድርጎ መለሰ ። የአባትነት ስሙ እንጂ አቅሙ የለኝም ብሎ ይሆናል ። ልጁ “አባ” አለ፡- “አቤት” በማለት በዝቅታ ፣ በኀዘኔታና በፍቅር ድምፅ መለሰለት ። ልጁ እጁን እየጠቆመ “አባ ጫማ ግዛልኝ” አለው ። ያ አባትም፡- “እሺ እገዛልሃለሁ” አለው ። የአባት መልስ ልጁን ቢያሳርፈውም አባት ግን ያረፈ አይመስልም ። አነጋገሩ እንደማይገዛ ያሳያል ። ግን ድምፀቱን ወደ ኋላ እየፈተሽኩ ስሰማው አንድ ቀን እገዛልሃለሁ ፣ እንደ መሸ አይቀርም የሚል ነው ። 

መንገዱ ተለቀቀና መኪናው አፈተለከ ። እኔም ያንን አባትና ልጅ በአሳብ ይዣቸው ወደ ቤቴ ገባሁ ። አሁንም ፊት ለፊቴ ይታዩኛል ። ጥጋብ ሰውን ቢፈትንም ማጣት ግን ከዚያ በላይ ፈታኝ ነው ። ለወለዱት ልጅ መስጠት አለመቻል ትልቅ ሕመም አለው ። ስሙን ተሸክሞ በተግባር አባት መሆን ሲሳን ቁጭት አለው ። “እሺ እገዛልሃለሁ” አለ ። ልጁም አጭር የማስታወስ አቅም ስላለው ይረሳዋል ። በተስፋ ግን ደስ ብሎታል ። ጥያቄዬ ተመለሰ ብሎም ዝም ብሏል ። ያ አባት ግን የልጁ ጥያቄም የራሱ መልስም ሲያጫውተው ይውላል ።

 

ያ ልጅ ጠይቆ ማግኘት አልቻለም ። አባቱ ፈቃድ ቢኖረውም አቅም የለውም ። እግዚአብሔር ግን ላልጠየቁት ሕይወትን ፣ ብርሃንን ፣ የዛሬዋን ቀን ሰጥቷል ። ከሁሉ በላይ ቃሉንና ልጁን ክርስቶስን ሰጥቶናል ። ሳንለምን በተቀበልነው ነገር ውስጥ ለምነን ያላገኘናቸውን ነገሮች አስቡ ። ሦስት  ነገሮች ብልጭ ይላሉ ። የመጀመሪያው፣ ሳንለምን የተቀበልነው ውድ ነገር ነው ። ሁለተኛው፣ ለምነን የከለከለን ፣ ጌታችን ክፉ ስለሆነ ሳይሆን ዓላማ ስላለው ነው ። ሦስተኛ፣ የተሰጠን ከሚሰጠን የሚበልጥ ነው ።

አይዘለቅም እስቲ ተዉኝ ። ብቻ በቸር ዋሉ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሰኔ 25 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም