መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ውስጣዊ ቍጣ » ውስጣዊ ቍጣ ክፍል 9

የትምህርቱ ርዕስ | ውስጣዊ ቍጣ ክፍል 9

“የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና ።” ያዕ. 1 ፡ 20 ።

10 – ፍላጎትን አለማወቅ

በትዳር ውስጥ ከሚነሡ ጠቦችና መሰለቻቸቶች አንዱ ፣ አንደኛው ወገን የሚፈልገውን አለማወቁ ነው ። እርሱን ለማስደሰት አንድ ነገር ሲደረግለት አይረካም ። ለምሳሌ ጫማ እፈልጋለሁ ብሎ በደመ ነፍስ ፍላጎቱን ይናገራል ። ጫማው ተገዝቶ ሲመጣ ግን ደስተኛ አይሆንም ። ቢረካ ተብሎ ጫማ ፋብሪካው ይከፈትለታል ፤ የበለጠ ኀዘነተኛ ይሆናል ። ስለዚህ መነጫነጭ ፣ ማዘን ፣ ማልቀስ ፣ ሌሎችን መክሰስ ያበዛል ። ለማስደሰት የሞከረው ሰውም ሙከራውን ሲጨርስ ፣ አቅርቦቱን ሲያጣ መሰልቸት ይጀምራል ። መፈራራትና ላለመገናኘት መንገድ መፈለግ ይጀመራል ። ይህም በትዳር ውስጥ ያለውን ክፍተት እያሰፋው ይመጣል ።

ብዙዎች ይሠራሉ ፣ ይነግዳሉ ፣ ይሮጣሉ ምን እንደሚፈልጉ ግን አያውቁትም ። አንድ ሕንፃ ይሠራሉ ፣ እርሱን ሳያጣጥሙት ሁለተኛው ያምራቸዋል ። መንግሥት ቤት የሚሠራ ሠራተኛ በቃህ ፣ ዕረፍ ተብሎ ጡረታ ይወጣል ። የግል ሥራቸውን የሚሠሩ ግን መቆሚያ በሌለው አዙሪት ውስጥ ይገባሉ ። ይሰበስባሉ ለምን እንደሚሰበስቡ ግን አያውቁም ። ራሳቸውን በድለው ያጠራቀሙት ገንዘብ ፣ ጤናቸውን ጎድተው የሰበሰቡት ሀብት ግቡ ምን እንደሆነ አያውቁም ። ለትዳራቸው ለልጆቻቸው ጊዜ ነፍገው ፣ የፍቅር ጥያቄን በገንዘብ እየመለሱ መኖር የሚችሉ ይመስላቸዋል ። ዓይናቸውን ሲገልጡ ግን ትዳራቸው ሄዷል ፣ ልጆቻቸው ከድተዋቸዋል። ትዳር ጊዜን የሚካፈሉበት ትልቅ ተቋም ነው ።

የሚፈልጉትን የማያውቁ በመስገብገብ ፣ ሌላውን ሰልቅጦ በመዋጥ ፣ ሁሉም ነገር የእኔ ይሁን በማለት ብዙ ጠላት ያፈራሉ ። ፍላጎትን የማያውቅ ሰው ድንበር የለውም ። የሚያቆመው ነገር አይፈልግም ። ፍላጎትን ባለማወቁ ምክንያት የመጣበትን አለመርካት ፣ ያበዛውን የጠላት ቍጥር ፣ የደረሰበትን ብቸኝነት ሲያስብ ውስጣዊ ቍጣ ይገጥመዋል ። የማይፈለግ ሰው መስሎ ራሱ ይሰማዋል።

በሃያዎቹ መጀመሪያ ያሉ ወጣቶች የሚፈልጉትን ነገር መለየት ያቅታቸዋል ። ሠዓሊ ሲያዩ ሠዓሊ መሆን ፣ ሙዚቀኛ ሲያዩ ሙዚቀኛ መሆን ያምራቸዋል ። ያልተሰጣቸው ይሆንና አቅም ሲያጡ፣ ገደብ ሲገጥማቸው ተስፋ ይቆርጣሉ ። የሚፈልጉትን ነገር በትክክል ቢያውቁ ከብስጭት ይድናሉ ። የሚፈልጉትን ማወቅ እንዲህ በቀላል የሚገኝ ላይሆን ይችላል ። የጸሎት ኃይል ፣ የአባቶች እገዛ ያሻዋል ። የሚፈልጉትን ባለማወቅ ከሃይማኖት ሃይማኖት የሚገላበጡ ፣ አህያ “እኛ ያልፈሳንበት ዳገት የለም” ብላ በክብር እንዳወራችው ፣ ያላየነው ሃይማኖት የለም በማለት ነውሩን እንደ ክብር የሚያወሩ ሰዎች አሉ ። እነዚህ ሰዎች የሚገጥማቸው ችግር ሦስት ዓይነት ሊሆን ይችላል ። የመጀመሪያው ከሀዲ መሆን ነው ፣ ሁለተኛው ሚና የለሽ መሆን ፣ ሦስተኛው ምግባር የለሽ መሆን ነው ። የምፈልገው ምንድነው ? ብለው ራሳቸውን መጠየቅ አለባቸው ። በዚህ ምክንያት እነዚህ ሰዎች በብስጭትና ሁሉም ነገር ባዶ ነው በሚል ስሜት ውስጥ ይወድቃሉ ። ምርጫችን እንጂ ሕይወት ከንቱ አይደለችም ።

ስለዚህ ሰው አስቀድሞ የምፈልገው ምንድነው ? ማለት አለበት ። የሚፈልገውን ካወቀ ገበያ ላይ ያየውን ሁሉ ልግዛ አይልም ። ቤቱን በማይጠቀምበት ሸቀጥ ሞልቶ መራመጃ አያጣም ። ሁሉም የእኔ ይሁን ብሎ ራሱን አይከስርም ። ድንበር የለሽ ሆኖም ጠላት አያበዛም ። አብረውት ለሚኖሩት ወዳጆቹም ጥያቄ አይሆንም ። የብዙ ሰዎች ዕረፍት ማጣት ፣ መነጫነጭ ፣ ማዘንና ማጉረምረም ከእኛ ጋር በተያያዘ ሳይሆን የሚፈልጉትን ባለማወቅ የመጣ ነው ። እኛም የምንፈልገውን የማናውቅ ከሆነ ተሰቃይተን ሌላውንም ሰው እናሰቃያለን ። ሰው ስላደረገው ብቻ የምናደርገው ፣ ሰው ስለገዛ ብቻ የምንገዛው ነገር እርካታ ቢስ ያደርገናል ። በአገራችን ከጎን ሰው ሳያዩ ምንም ማድረግ የተከለከለ ይመስላል ። ራሱ የሚያስደስተውን ከሚለብስ ፣ ሰዎች ይደሰቱበታል የሚለውን የሚለብስ ይሆናል ። ራሱ የሚኖርበትን ቤት የሌሎችን ደስታ በማዳመጥ ያንጸዋል ። በመጨረሻ ይሰለቸዋል ። ከገንዘቡም ከኅሊናውም መሆን ስለሚያቅተው ብስጭት ውስጥ ይገባል ።

አዎ ውስጣዊ ቍጣ ከሚያመጡ ነገሮች አንዱ የሚፈልጉትን አለማወቅ ነው ። ሥራ አልን ሥራ መጣ ፣ ትዳር አልን ትዳር ያዝን ፣ ልጆች አልን ልጆች አገኘን ። የምንጠራው ፍላጎት በመጣ ቍጥር የእኛ ደስታ እየራቀ ከመጣ የመጀመሪያው የምንፈልገውን አለማወቅ ሲሆን ሁለተኛው ከክርስቶስ የሚገኘውን ደስታ ከዚህ ዓለም ንብረትና ሰዎች እየፈለግን ነው ማለት ነው ። ዛሬ የምፈልገው ምንድነው ? በማለት ጊዜአችንን ፣ ገንዘባችንን ፣ ደስታችንን እናትርፍ ! እንደ እርጉዝ ሴት በመቅበጥበጥ ፣ ያምረናል እንጂ የሚያምረንን መለየት የማንችል ሰዎች መሆን አይገባንም !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 16 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም