መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 5

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 5

ኑፋቄን እንዴት እንዋጋ ?

ልዩ ትምህርት በአበው ፣ በነቢያት ፣ በሐዋርያት ፣ በመጻሕፍት የማይታወቅ ነው ። ልዩ ትምህርት ኑፋቄ ነው ። እንክርዳድ የተቀላቀለ ስንዴ ነው ። ሰው በዝሙት ፣ በስርቆት መፈተንን ከባድ አድርጎ ያየዋል ። የኑፋቄ ፈተና ግን ከዚህ የባሰ ነው ። ኑፋቄ የእግዚአብሔርን ትክክለኛ መልክ ይወስድብናል ። የእረኞቻችንን መልካምነት ያጠለሽብናል ። ጸሎታችንን እምነት አልባ ያደርገዋል ። የግላችንን የሥነ መግባር መርሖ እንድናወጣ ፣ ጆሮ ነሥቶ አፍ ብቻ ያደርገናል ። ከዚህ ለመውጣት የጠራውን ምንጭ ፣ ነገረ እግዚአብሔርን ከዓይናማ መምህራን መማር ፣ በጸሎት መማጸን ፣ እምነታችንን ሊያጠናክሩ ከሚችሉ ሰዎች ጋር መዋል ፣ የተቀደሱ መጻሕፍትን ማንበብ ፣ የበረቱ አባቶችን የጸሎት እርዳታ መጠየቅ ይገባል ።

ኑፋቄ የሚያምሳት ቤተ ክርስቲያን ወዳጅና ጠላትዋን መለየት ያቅታታል ። እረኛውም ልቡ በኀዘን ፣ አእምሮው በጥርጣሬ ይመታል ። ከፍተኛ ቅራኔ በምእመናን መካከል ይፈጠራል ። መከፋፋትና መጠፋፋት ይመጣል ። በዚህ ውስጥ እረኛው ወይም ወጣቱ አገልጋይ ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ አለበት ። ማስተማር እንጂ ማሳመን የእርሱ ድርሻ አለመሆኑን አምኖ መረጋጋት ፣ ዛሬ የተገፋው እውነት አንድ ቀን እንደሚረታ መገንዘብ አለበት ። ሰድበውት የሄዱት አልቅሰው እንደሚመጡ እርግጠኛ መሆን አለበት ። ውሸት ሁልጊዜ ጥላ አይሆንምና ።

ልዩ ትምህርት የሚመጣበት ምክንያት የመጀመሪያው ሰርገው በሚገቡ የኑፋቄ አራማጆች ነው ። ሰይጣን ከቤተ ክርስቲያን ማስወጣት ብቻ ሳይሆን ወደ ቤተ ክርስቲያንም አስርጎ ያስገባል ። የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለመጉዳት የጥርጣሬ ሠራዊቱን ያዘምታል ። ሁለተኛው መምህር በሌለበት የሚደረጉ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች ለኑፋቄ መነሻ ይሆናሉ ። መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት መልካም ቢሆንም ስንስት የሚመልሱን መምህራን ቢኖሩ የተሻለ ነው (የሐዋ. 8፡30-31)። እግዚአብሔር መጽሐፉን በመንፈሱ እንዳጻፈ ፣ በመንፈሱም ይተረጕምልናል ። ለማጻፍ ሰዎችን እንደ ተጠቀመ ለመተርጎምም መምህራንን ይጠቀማል ። የዓይናማ መምህራን የትርጓሜ መጻሕፍትም ጥናታችንን ሊያግዙ ይችላሉ ። ሦስተኛው የስህተት ትምህርት መግቢያው የሰይጣን ፈተና ነው ። ሰይጣን በስንዴው ላይ እንክርዳድ ፣ በእምነት ላይ ጥርጣሬ መንዛት ልማዱ ነው ። በርኵስ መንፈስ ውጊያ ውስጥ የሚያልፉ የኑፋቄ ፈተና ይገጥማቸዋል ። የሥላሴን ምሥጢር ፣ የክርስቶስን ጌትነት ፣ የምሥጢራትን ክብረት ለመረዳት ይቸገራሉ ። አራተኛው የስህተት ትምህርት መገኛ ሥልጣንና ገንዘብ ፈላጊነት ነው ። በስህተት ትምህርት መንጋውን ነጥቆ ፣ እረኛውን በማባረር ስፍራውን መቆጣጠር የሚፈልጉ ፣ አሊያም በጎችን ሰርቀው የራሳቸውን ማኅበር ሊመሠርቱ የሚሹ መሣሪያ የሚያደርጉት ልዩ ትምህርትን ነው ። ልዩ መባሉም በነቢያት ፣ በሐዋርያት ፣ በሊቃውንትና በቤተ ክርስቲያን ጉዞ የማይታወቁ ስለሆኑ ነው ።

ልዩ ትምህርትን ያመጡ ሰዎች ሲገኙ ወጣቱ አገልጋይ ማስተዋል ያለበት ነገር አለ ። ልዩ ትምህርት የመሰለው እርሱ ስላልተማረ ወይም ስላላወቀው ነው ወይስ በእርግጥም ልዩ ትምህርት ነው ወይ ? ብሎ መጠየቅ አለበት ። ብዙዎች ሰምተው የማያውቁተን እውነት ሲሰሙ ውሸት ይመስላቸዋል ። በሁለተኛ ደረጃ የልዩ ትምህርት አምጪዎቹን በግል ጠርቶ ማነጋገር ያስፈልጋል ። ከባለቤቱ ሳይሰሙ ፍርድ መስጠት እንኳን በመንፈሳዊ በዓለምም ችሎት የለም ። አንዳንድ ጊዜ በቅናት ፣ በምቀኝነት ለሰው ስም መስጠት አለና ። የሚፈሩትን ሰው መናፍቅ ማለት የተለመደ ነው ። በጉቦ ማውገዝም የሰው ጠባይ ነው ። አዎ ውግዘት በፖስታ አይላክም ። ደርሶ ማውገዝ የሚወዱ በመጨረሻ እርስ በርስ ይወጋገዛሉ ። ውግዘት ለቤተ ክርስቲያን የጭንቅ መፍትሔዋ እንጂ ደስ እያላት የምታደርገው አይደለም ።

ያ ልዩ ትምህርት የያዘው ሰውም እንደ ጠላት ሳይሆን በእምነት እንደ ደከመ ሰው ታይቶ እርዳታ ሊደረግለት ይገባዋል ። የያዘውን ትምህርት እንዲገነዘበው ጊዜ መስጠት ፣ እንዲመለስም መማጸን ይገባል ። አንዱ ሰው አንድ አይደለምና ብዙዎችን ይዞ ይሄዳል ። ከስህተቱ አልመለስ ብሎ ፣ ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን የማሰላሰያ ጊዜ ንቆ በክፋቱ የበረታ እንደሆነ ሊለዩት ይገባል ። ይህ መለየትም እስኪመለስ እንጂ ጨርሶ እንዲጠፋ አይደለም ። አካለ ክርስቶስ የሆነች ቤተ ክርስቲያን በሌሎች መጥፋት አትደሰትምና ። የውግዘት ዓላማው በቀል ፣ በርን መዝጋት ሳይሆን በፍቅር መቅጣት ነው ።

የሚሆነው ሲሆን የነበረ ነውና ልዩ ትምህርት ሲነሣ መደናገር አይገባም ። የደነገጠ መሪ ወዳጆቹንም ያጠፋል ። መሪ ሲደነግጥ ፣ አውሬ ሲቆስል እርምጃው ልክ የለውም ። ከዚሁ ጋር የቤተ ክርስቲያን አንድነት ዶግማ መሆኑን መገንዘብ ይገባል ። አንድነትን የሚጎዳ ነገር ሲመጣ ተገቢውን ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል ። ነቢዩ ኢሳይያስ 700 ዓመት አሻግሮ ትንቢት ተናገረ። ቤተ ክርስቲያን ሰባት መቶ ዓመት አሻግራ የምታይና የምትዘጋጅ ናት ። የምታየው በዓይነ መለኮት ነውና ።

አገልጋይ ሆይ ! በውስጥ ከስህተት አስተማሪዎች ፣ በውጭ ከአረማውያን ጋር ትግል አለብህና እግዚአብሔር ያጽናህ !

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 5

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 20 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም