መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /15/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /15/

 

ሐዋርያውን ብዙ ጥያቄዎች ለመጠየቅ ፈለግሁ ። በሕይወት ዘመኔ ፣ በኑሮ መንገዴ የምማራቸውን ሁሉ በአንድ ቀን ጠቅልዬ የማወቅ ብልጠት አደረብኝ ። እርሱ ቢነግረኝም አንዳንዱ ነገር በጉዞዬ ገዝፎ ካላየሁት እንደማይገባኝ ተረዳሁና ልቤን ተው አልሁት ። ሐዋርያውም ከፊት ከፊቱ ቀደም እያልሁ የምናገረው ትክክል በመሆኑ በፈገግታ ያየኝ ነበር ። ቅዱሳን ትዝብትን ጥለው ሌሎችን መርዳትን ብቻ የሚያስቡ እንደሆኑ አውቃለሁ ። ያስተምራሉ ፣ ትምህርቱ ያልገባውን ደግመው ያስተምሩታል ። በተማረው እንዲኖር ይጸልዩለታል ። በበደል በወደቀ ጊዜም አብረውት ያለቅሳሉ ። በንስሐው አጋር ይሆኑታል ። የቅዱሳን ጠባይ ፣ ክርስቶስን የሚመስሉ ቡሩካን መገለጫ ይህ ነው ። ሐዋርያውም ስለ ሁሉም መልእክታቱ በዝርዝር ለማወቅና ሊቅ ለመሆን መፈለጌን በርኅራኄ አየው ። ቢሆንም መስማት በምችልበት መጠንና በሚያስፈልገኝም መጠን ፣ ለዛሬም በታዘዘልኝ የዕለት እንጀራ ልክ ሊነግረኝ ፈለገ ። እኔም የእግዚአብሔር ቃል ለትላንት ስህተት ስርየትን ፣ ለዛሬ ቁመና ምግብን ፣ ለነገ መድረሻ አቅምን እንደሚሰጥ ተገነዘብሁ ። 

ሐዋርያው ቀጠለ፡- “አንደኛ ቆሮንቶስን የተረዳኸው በመልካም ነው ። ሁለተኛ ቆሮንቶስን የላክሁት ለማጽናናትና መደሰቴን ለመግለጥ ነው ። የሚጽናኑበትም ምክንያት አንደኛ ቆሮንቶስ በተባለውና ከዚያ በፊት በነበረው መልእክቴ መክሬና ተግሣጽ አስተላለፌ ስለነበረ ነው ። አሁን ግን የበደለው ንስሐ በመግባቱ ፣ የተቀጣው ሰው በመጸጸቱ ፣ ሥልጣንን ተጋፍቶ አገልጋዮቹን የናቀው በመመለሱ ደስታ ተሰማኝ ። ደግሞም ለኢየሩሳሌም ድሆች ልባቸው ራርቶ ስለሰጡም ላመሰግናቸው ፈለግሁ ። በዚህ ምክንያት ሁለተኛውን የቆሮንቶስ ጦማር ጻፍሁ ። ገላትያ ዛሬ በቱርክ ግዛት ውስጥ ብትገኝም እኔ በሥጋ በነበርሁበት ዘመን የሮማ ግዛት ነበረች ። የገላትያ ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ አይሁዳውያን ታውካ ነበር ። እነዚህ አይሁዳውያን ከአሕዛብ ወገን የሆኑትን የገላትያ ክርስቲያኖች አውከው ነበር ። ሁከቱ የመጣውም በእኔና በትምህርቴ ነው ። ጳውሎስ ሐዋርያ አይደለም ፣ ደግሞም ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ አይደለም ። ወንጌል ያለ ኦሪት ፣ ጥምቀት ያለ ግዝረት ፣ ክርስቶስ ያለ ሙሴ የማዳን አቅም የላቸውም ብለው በማስተማራቸው ብዙዎች ታውከውና ልባቸው ተከፍሎ ነበር ። በሮማ ግዛት የአይሁድ ሃይማኖት ትልቅ ክብር አግኝቶ ስለነበር ተሰሚነታቸው እውነቱን ሐሰት ለማሰኘት እየጣረላቸው ነበር ። እኔም ጸጋውን በእምነት እንደተቀበሉ እንዲጸኑ መዳናቸውን እንዳይጠራጠሩ ለመንገር ይህን መልእክት በቀዳሚነት ጽፌአለሁ ። 

የኤፌሶን መልእክትም አስደናቂ መልእክት ነው ። ዛሬ ቱርክ ብላችሁ በምትጠሩአት አገር ምዕራባዊ ዳርቻን ይዛ የተመሠረተች ውብ ከተማ እንዲሁም የጣዖታት መገኛ ነበረች ። በዚህች አገርም የተለያዩ ትርኢቶች ይከናወኑ ነበር ። ዛሬ በአሸዋ ተውጣ የቀረችው ያች ምድር በዚያ ዘመን ለእስያ አውራጃ እንደ መዲና ነበረች ። በግሪክ ቆሮንቶስ በእስያ ኤፌሶን መጠራታቸው የዘመኑ ልማድ ነበር ። ይህችን ቤተ ክርስቲያን በቀጥታ ባይሆንም መሪዋን ጢሞቴዎስን ለመምከርም አንደኛና ሁለተኛ ጢሞቴዎስን ጽፌአለሁ ። ዮሐንስም በራእዩ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መልእክት ሲያስተላልፍ ኤፌሶን ቀዳሚ ነበረች ። በእስር ላይ ሁኜ ከጻፍኩአቸው መልእክታት የኤፌሶን መልእክት ተጠቃሽ ነው ። የኤፌሶን መልእክት ለወቀሳ ለተግሣጽ አልተጻፈም ። የተጻፈው በሰማያዊ ስፍራ ያላቸውን ሀብትና ክብር እንዲያውቁት ለማሳሰብ ነው ። ሰው ዋጋውን ካወቀ በኃጢአትና በጣዖት አይወድቅምና ። 

የፊልጵስዩስ መልእክት በእስር ላይ ሳለሁ የጻፍሁት ነው ። ፊልጵስዩስ የሰሜናዊ ግሪክ የመቄዶንያ አውራጃ ደማቅ ከተማ ናት ። በዚህች ከተማ የሚኖሩ አነስተኛ ኑሮ የነበራቸው ምእመናን ነበሩ ። ይህች ከተማ የወታደር ከተማ እንደ መሆንዋ ኑሮዋ ዝቅተኛ ነው ። ታዲያ ከዚህ ኑሮአቸው በአፍሮዲጡ እጅ ለእስራቴ እጅ መንሻ ልከውልኝ ነበር ። እውነተኛ ስጦታ ከትርፍ ሳይሆን ከጉድለት የሚደረግ ነው ። ስጦታዬ እስካልተሰማኝና እኔን እስካልጎዳኝ ገና አልሰጠሁም ማለት ነው ። እኔም “ተቀብሎ የማያመሰግን ቀማኛ ነውና” ላመሰግናቸው ይህን መልእክት ጻፍሁ ። ደግሞም ቢጽ ሐሳውያን ገብተውባቸው የክርስቶስን ልዕልና እንዳይቀበሉ ይገፋፉአቸው ነበር ። የመናፍቃን አንዱ ተግባር ድፍረትን ማለማመድ ነው ። በዚህ ምክንያት ትዕቢትን አስለምደዋቸው ነበር ። ክርስቶስ አምላክ ወልደ አምላክ ሳለ የባርያውን መልክ ይዞ መጥቷልና ትሑታን መሆን እንደሚገባቸው ከስህተት አስተማሪዎችም እንዲጠበቁና ሁልጊዜ በክርስቶስ ደስ እንዲላቸው ይህን መልእክት ጻፍሁ ። 

የቈላስይስ ቤተ ክርስቲያን እኔ ራሴ ያልመሠረትኋት በኤጳፍራና በአክርጶስ ስብከት ያመነች ናት ። በዚህች ቤተ ክርስቲያን የስህተት ትምህርት ባየለ ጊዜ በሁሉ ዘንድ ተሰሚነት ያለው ጳውሎስ መልእክት ቢጽፍ የሚል አሳብ ከእነ ኤጳፍራ ስለመጣ ይህችን ቤተ ክርስቲያን በመልእክቱ ጎበኘኋት ። ስለ ትክክለኛው ትምህርት መጀመሪያ ገለጥሁ ። ትክክለኛውን ማወቅ ትክክል ያልሆነውን ለማወቅ ይረዳልና ስለ ሐሰት ከማጥናት ስለ እውነት ማጥናት መልካም ነው ። በሁለተኛው ክፍል ደግሞ ስለ ስህተት ትምህርቶች መልስ ሰጠሁ ። ቈላስይስ ለኤፌሶን ጎረቤት የሆነች ዛሬ በቱርክ ግዛት በእኔ ዘመን ደግሞ በሮም ግዛት የነበረች ከተማ ናት ። እነዚህ ቢጽ ሐሳውያን ስለ ግዝረት ፣ ስለሚበሉና ስለማይበሉ ምግቦች በማንሣት ከክርስትና እምነት ወደ ኋላ እንዲሉ አድርገዋል ። በአንድ እግዚአብሔርና በክርስቶስ ያመኑ አይሁዳውያን ወንድሞች ሲባሉ ከጥምቀት ጋር ግዝረት ፣ ከክርስቶስ ጋር ሙሴ ከሌሉ ሙሉነት የለም ብለዋልና ሐሳውያን ተብለዋል። በዚህ ምክንያት ቢጽ ሐሳውያን ወይም ሐሰተኛ ወንድሞች እንላቸዋለን ። 

ዴማስ በውበትዋ ተስቦ ከጠፋባት ከተሰሎንቄ ከተማ የሚኖሩ ምእመናን ነበሩ ። በሩቅ ቢያያት ውብ መሰለችው ፣ በውስጥዋ ያሉ ተሰሎንቄአውያን ግን በክርስቶስ አምነው ነበረ ። እነርሱ በአካል በተሰሎንቄ ቢኖሩም ልባቸው ግን በሰማይ ነበረ ። ከተሰሎንቄ ውጭ የነበረው ዴማስ ግን አካሉ በሌላ አገር ሁኖ ልቡ በተሰሎንቄ ነበረ ። ልባችን ባለበት እንኖራለንና ጠፋ ። የተሰሎንቄ አማንያን ግን ክርስቶስ ይመጣል ብለው በተራራ ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው ወጥተው ይጠባበቁ ነበርና አንደኛና ሁለተኛ መልእክቴን ጻፍሁ ። ተሰሎንቄ ሰሜናዊ የግሪክ ግዛት የሆነው የመቄዶንያ አውራጃ ዋና ከተማ ናት ። ብዙ ጠላቶችም የእኔን ስም እያጠፉ ነበር ። ስሜ ጠፋ ብሎ መልእክት መጻፍ ነውር ቢሆንም አዳዲስ ምእመናን ግን እንዳይጎዱ በማሰብ ለማረጋጋት ይህን መልእክት ጽፌአለሁ ። ደግሞም በክርስቶስ ምክንያት መከራ እንደ ጸናባቸው ስላየሁ ከመልእክቶቼ ሁለተኛ አድርጌ የተሰሎንቄን መልእክት ጻፍሁ ። ከገላትያ መልእክት ቀጥሎ የጻፍሁት ነው ። ወገኖቻቸው በሞት ስለተለዩአቸው ኀዘን በማብዛታቸው ፣ የክርስቶስ ምጽአትም የራሱ የሆኑ ሂደቶች እንዳሉት ለመግለጥ እነዚህን መልእክታት ጽፌአለሁ ። 

አንደኛና ሁለተኛ ጢሞቴዎስን የጻፍሁት ለመንፈስ ልጄ ፣ ለኤፌሶን ጳጳስ ፣ ለሥራ ባልደረባዬ ለወጣቱ ለጢሞቴዎስ ነው ። መንፈስ ቅዱስ ልቡን ከሰበረው ወጣትም ጳጳስ ሊደረግ ይችላል ። የደቡባዊ ቱርክ የልስጥራን ተወላጅ ለነበረው በእናቱ አይሁዳዊ በአባቱ ግሪካዊ የሆነው ባልደረባዬ ጢሞቴዎስ ስለ አገልግሎትና ስለ አገልጋዮች ፣ ስለፈተናውና ስለመስፈርቱ ስጽፍ እርጅና እየተጫጫነኝ ሞትም እየተቃረበ ነበርና ሁለተኛውን መልእክትም ለስንብት ጽፌአለሁ ። የቲቶ መልእክትም ተመሳሳይ ነው ። ቲቶ የቀርጤስ ጳጳስ የዛሬዋ ዩጎዝላቪያ የድሮዋ ድልማጥያ መምህር የነበረ እንደ ጢሞቴዎስ ወጣትና ባልደረባዬ የነበረ ቅን ሰው ነው ። ትውልዱ እንደ ሉቃስ ከአሕዛብ ከግሪክ ነው ። ስለ አገልግሎትና ስለ አገልጋዮች መስፈርት ጽፌለታለሁ ። 

የፊልሞና መልእክትም የራሱ ዓላማ ነበረው ። ፊልሞና በቆላስይስ ከተማ ይኖር የነበረ ክርስቲያን ተማሪዬ ነው ። ባርያው አናሲሞስ ብዙ ንብረት ሰርቆ ወደ ሮም በሄደ ጊዜ እኔን አገኘኝ ። እኔም በእስራት ላይ ሆኜ ሳለሁ አስተምሬ እንዲያምን አደረግሁት ። ወደ ጌታው መመለስም ግድ ሆነብኝ ። የአናሲሞስም አእምሮ ማረፍ አለበት ፣ እኔም የወዳጄን ባሪያ ይዤ መቅረት ተገቢ አይደለም ። የተጨነቅሁት ግን ሁላችን በክርስቶስ ነጻ ወጥተናልና እንደ ወንድማማች እንድንተያይ ደግሞም በዚያ ዘመን ጌታው ባሪያውን ቢገድለው እንኳ ንብረቱ ስለሆነ ሕጉ ይፈቅድለታልና ፊልሞና እንዳይጨክን ወደ ሕግ ሳይሆን ወዳዳነው ጸጋ እንዲመለከት ለማሳሰብ ነው ። የዕብራውያን መልእክቴም ለአይሁድ የተጻፈ ነው ። በይሁዳ አይሁድ ፣ በያዕቆብ እስራኤል እንደ ተባሉ በዔቦርም ዕብራውያን ተብለዋል ። እነዚህ ክርስቲያን አይሁድ ከወገኖቻቸው በደረሰባቸው መከራ ወደ ኦሪት ሊመለሱ ተቃርበው ነበርና ባሉበት እንዲጸኑ የጻፍሁት ነው ። ሁሉን ብተነትንልህ ደስ ይለኝ ነበር ። ያንተ ጊዜ ግን አጭር ስለሆነ ይበቃሃል ። በል ዝቅ በልና በረከት ልስጥህ ። 

እግዚአብሔር በሰማያዊና በምድራዊ በረከት ይባርክህ ! ባርኮ ለበረከት ያድርግህ ! የሰጠህን መልካም ነገር ያጽናልህ ! አምነህ ለመኖርና ለመሞት ያብቃህ !” 

እኔም፡- አሜን ፣ አሜን ፣ አሜን አልኩኝ ። 

ወደ ነበርሁበት ምድር ስመለስም “ጳውሎሰን አገኘሁት” ብዬ በልዑል ድምፅ ተናገርሁ ። በርግጥም ጳውሎስን አገኘሁት ።

ተፈጸመ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን 

መጋቢት 16 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም