መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /12/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /12/

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለ መልእክታቱ ይተነትንልኛል ብዬ አስቀድሜ ብጠይቅም የረሳው መስሎኝ ነበርና ለማስታወስ ስሞክር አንድ ምሥጢር ብልጭ አለልኝ ። በዓለመ ነፍስ መርሳት እንደሌለ ፣ የፈጠረውንና ዕቅዱን የማይረሳውን እግዚአብሔር የሚያገለግሉ ወገኖች እንደማይረሱ ገባኝ ። በምድር ላይ የሚኖሩ ኑሮና ሕይወትን ፣ ምድርና ሰማይን ፣ ዓለምና ቤተ ክርስቲያንን ፣ እግዚአብሔርንና ሰውን ለመያዝ ስለሚሞክሩ ለመርሳት ይዳረጋሉ ። በሰማይ ግን ኑሮ ፣ ምድር ፣ ዓለም ፣ እንዲሁም ከንቱ የሆነው የሰው ይሁንታ/ሙገሳ የለም ። ኑሮ ባለመኖሩ መባከን ፣ ምድር ባለመኖሯ መርከስ ፣ ዓለም ባለመኖርዋ ከንቱነት ፣ ሰዋዊ ሙገሳ ባለመኖሩ ጉልበት መጨረስ የለም ። በሰማይ ለአንድ ጌታ ማደር ስላለ አሳብ ሁሉ ያርፋል ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክታቱን እንዴት እንደ ጻፈ ለመናገር ሲዘጋጅ እኔም ከሮሜ መልእክቱ ቢጀምር ብዬ አሰብሁ ። እርሱም ቀና ነውና ደስተኛ ሆነ ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን በአንደበት ሳይሆን በልባችን እናወጋና እንግባባ ነበር ። ወደ ምድር ስመለስ ተናግሬ የማልግባባቸውን ሰዎች አሰብሁና አዘንሁ ። እንደገናም ይህ ዓለም ስላለኝ ፣ ጉዞዬን ስፈጽም ተመልሼ ስለምመጣ ደስ አለኝ ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ሮሜ መልእክቱ መናገር ጀመረ፡- “በርግጥ እኔ እንኳን ከመጀመሪያው መልእክቴ ከገላትያ መልእክት ልጀምርልህ አስቤ ነበር ። እየመረጥን ያለነው ከመልካምና ከመልካም ነውና ከየትኛውም ብንጀምር ደስተኛ ነኝ ። የመልእክታቴን ቅደም ተከትል ለማወቅ ከፈለግህ  የመጀመሪያው የገላትያ መልእክት ፣ ሁለተኛው አንደኛ ተሰሎንቄ ፣ ሦስተኛው ሁለተኛ ተሰሎንቄ ፣ አራተኛው አንደኛ ቆሮንቶስ ፣ አምስተኛ ሁለተኛ ቆሮንቶስ ፣ ስድስተኛው የሮሜ መልእክት ፣ ሰባተኛው ወደ ቆላስይስ ሰዎች የተላከ ፣ ስምንተኛው የፊልጵስዩስ መልእክት ፣ ዘጠነኛ የፊልሞና መልእክት ፣ አሥረኛው ወደ ጢሞቴዎስ የተላከ አንደኛው መልእክት ፣ አሥራ አንደኛ የኤፌሶን መልእክት ፣ አሥራ ሁለተኛ የቲቶ መልእክት ፣ አሥራ ሦስተኛ ሁለተኛ ጢሞቴዎስ ፣ አሥራ አራተኛ ወደ ዕብራውያን ሰዎች ናቸው ። መልእክታቱንም የጻፍኩበት ዘመን ከ48-66 ዓ.ም ገደማ ነው ። መልእክታቱም በአንደኛ የወንጌል ጉዞ የገላትያን መልእክት ፣ በሁለተኛ የወንጌል ጉዞዬ አንደኛና ሁለተኛ ተሰሎንቄ እንዲሁም አንደኛና ሁለተኛ ቆሮንቶስ ፣ በሦስተኛ የወንጌል ጉዞዬ ዋዜማ ላይ የሮሜን መልእክት ጽፌአለሁ ። ሌሎቹን መልእክቶች በሮም በእስራትና በቁም እስረኛነት ሁኜ ጽፌአለሁ ። የእሥራት መልእክቶቼ የኤፌሶን ፣ የቈላስይስ ፣ የፊልጵስዩስ ፣ የፊልሞና መልእክታት ናቸው ። ከእስር ከተፈታሁ በኋላ ደግሞ አንደኛ ጢሞቴዎስን ቲቶን ስጽፍ በሁለተኛው እስራቴ ደግሞ ሁለተኛ ጢሞቴዎስን ፣ በመጨረሻም አሳሳቢ የነበረውን ሁኔታ ለመግፈፍ የዕብራውያን መልእክቴን ጽፌአለሁ ።

መልእክታቱን የጻፍሁት ለአብያተ ክርስቲያናት ፣ ለቤተ ክርስቲያን መሪዎችና ለግለሰቦች ነው ። ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች የጻፍሁት ለጢሞቴዎስና ለቲቶ ነው ። ለግለሰብ የጻፍሁት ለፊልሞና ነው ። ለመሠረትኋቸው አብያተ ክርስቲያናት ስጽፍ ላልመሠረትኋቸው አብያተ ክርስቲያናትም ጽፌአለሁ ። እነርሱም ሮሜና ቈላስይስ ናቸው ። መልእክታቱን የጻፍሁት ለማበረታታት ፣ ስህተትን ለማረም ፣ ወደ ኋላ እየተመለሱ ያሉትን ለመገደብ ፣ የተጣሉትን ለማስታረቅና አገልጋዮችን አይዟችሁ ለማለት ነው ።

እኔ ከሞትሁ በኋላ ቤተ ክርስቲያንን የተረከቡ አባቶች የሮሜ መልእክቴን የመጀመሪያ አድርገው በማስቀመጣቸው ደስ ብሎኛል ። ሌሎቹ መልእክታት ወቀሳና ተግሣጽ ፣ ወቅታዊ ጉዳይ አለባቸው ።፣ የሮሜ መልእክቴ ግን ወቀሳ የለበትም ። ሙሉና ወጥ የሆነ የጽድቅ መልእክት ነው ። ይህን ከፊት ማድረጋቸው በወቀሳ መጀመር ተገቢ አይደለም ብለው ነውና ላመሰግናቸው እፈልጋለሁ ። ሮሜ ወይም ሮም የኢጣልያ ዋና ከተማ ናት ። የተመሠረተችውም ከክርስቶስ ልደት በፊት በስምንተኛው ምእተ ዓመት ገደማ ነው ። ብዙዎችን ያማከለ ሥልጣንን ለመከተል ከክርስቶስ ልደት በፊት በአምስተኛው ክፍለ ዘመን ጉዞ የጀመረችው ሮም ይህ የአስተዳደር ዘይቤዋ በሦስተኛው ምእተ ዓመት ፈራረሰ ። በዚህ ምክንያት አገሪቱ በእርስ በርስ እልቂትና በመሳፍንት አገዛዝ ስትታመስ ከቆየች በኋላ አገሪቱን አንድ አድርጎ የሚገዛ አንድ ጠንካራ መሪ ሲፈለግ ጁሊየስ ቄሣር ተገኘ ። አገሪቱም በእርሱ አስተዳደር ብትረጋጋም ቆይቶ ግን በተቃዋሚዎች ተገደለ ። ከእርሱ ቀጥሎ አውግስጦስ ቄሣር ነገሠ ፣ አውግስጦስ ቄሣር ዓለም ሁሉ እንዲጻፍ ትእዛዝ ያወጣ ሲሆን ጌታችን የተወለደውም በእርሱ የሥልጣን ዘመን ነው ። ይህ አውግስጦስ ቄሣር እስከ 14 ዓ.ም. አስተዳድሮ የሥልጣን ዘመኑ አበቃ ። ከእርሱ በኋላም ጢባርዮስ ቄሣር እስከ 37 ዓ.ም. ድረስ አስተዳደረ ። ልብ አድርግ ጌታችን የሞተው በጢባርዮስ ቄሣር የሥልጣን ዘመን ነው ። ከጢባርዮስ ቀጥሎ ቀላውዴዎስ ቄሣር ከ41-54 ዓ.ም ነገሠ ። ከ54 ዓ.ም. እስከ 68 ዓ.ም ደግሞ እኔን የገደለኝ ኔሮን ቄሣር ነገሠ ።

የሮም መንግሥት ሰላምን በማስፈኑ ፣ ፍርድን በመስጠቱ ፣ ለጊዜው ባሕልና ሃይማኖትን ባለመንካቱ ተወዳጅ ነበር ። ክርስትና የተመሠረተውም የተሰበከው በዚህ ሮም ከእንግሊዝ እስከ መካከለኛ ምሥራቅ እስከ ሰሜን አፍሪካ በምትገዛበት ዘመን ነው ። በአምስተኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻም እዚህ ግባ የማይባል የሽፍቶች ቡድን የሮምን መንግሥት ጣለው ። በዚህ ምክንያት የሮም አወዳደቅ እያላችሁ ትተርካላችሁ ።

በዚህች በሮም ደማቅ ከተማ ለሚኖሩ ምእመናን የጻፍኩት የሮሜ መልእክት ተብሎ ይጠራል ። እኔ እነርሱን እያሰብሁ ብጽፍም መንፈስ ቅዱስ ደግሞ እናንተን እያየ ያጽፈኝ ነበር ።”

እኔም ሐዋርያው ጳውሎስ ብዙ ታሪኮችን ስለነገረኝ ፣ ታሪክ የመገንዘብ አቅሜን ተጠራጠርሁትና ትንሽ ለማሰላሰል ከዚያም ወደ ሮሜ መልእክት ጭብጥ አሳብ ለመግባት ጠየቅሁት ። እርሱም ደስ እያለው እሺ አለኝ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

የካቲት 23 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም