መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /9/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /9/

 

ብዙ ስለተጨዋወትን ከቆምን መቀመጥ ፣ ከዋልን ማምሸት ይኖራል ብዬ አስቤ ነበር ። ነገር ግን የቆመ የሚቀመጠው ሲደክመው ነው ፣ የሰማዩ ዓለም ግን ከበረቱ ድካም የለበትም ። ከዋሉም ማምሸት የለበትም ። ለካ ካህናቱ በሙታን ሽኝት ላይ ሲያስተምሩ፡- “ከዚህ የድካም ዓለም ወደማያልፈው ዓለም ተሸጋገረ” እያሉ የሚናገሩት እውነት ነው አልኩኝ ። እኔም ሐዋርያውን፡- “ስንት ዘመን የኖርህ ይመስልሃል ?” አልኩት ። እርሱም ዘመን የሚቆጥሩ የሚኖሩለት ብዙ ጉዳይ ያላቸው ሰዎች ናቸው ። እኛ ግን የምንኖረው ለእግዚአብሔር ክብር ብቻ በመሆኑ ከዘመን ቍጥር ወጥተን በዘላለም ውስጥ ተሰውረናል ። ደግሞም በእግዚአብሔር ዘንድ ሺህ ዓመት እንደ አንድ ቀን ነውና ሁለት ቀን የኖርን አይመስለንም” አለኝ ። እኔም ገና ወደ ምድር ስመለስ የሚጠብቀኝን የኑሮ ትግል በማሰብ ለመጨነቅ ሞከርሁ ። መጨነቅ ግን አልቻልኩም ። ጭንቀት ከማይደርስበት ከፍታ ላይ ነበርሁና ራሴን በደስታ ጥምቀት ውስጥ ተሰውሮ አገኘሁት ። የመጨነቅ መብትን ተጠቅሞ እንኳ መጨነቅ የማይቻልበት ሰማያዊ ዓለም ስላለን ደስ አለኝ ።  ምድርን የመጨረሻ ቤታቸው አድርገው ለሚኖሩና ተስፋ ያደረጉት ነገር ሲሰበርባቸው በእግዚአብሔር መጽናናት ላቃታቸው ወገኖቼ እንዲህ ያለ ተድላ መኖሩን ለመንገር ቸኮልሁ ። 

በአንዱ ልቤ፡- “ሰማይ ደርሶ በመምጣቱ ተአምር ሆነለት” ብለው እንደሚቀበሉኝ እንጂ ከልባቸው የሰማይን ምሥጢር ለማወቅ እንደማይሹ አወቅሁና አዘንሁ ። መለኮታዊ የሆነ መገለጥን ትተው ስለ ሽሮና በርበሬ እንዲነገራቸው የሚፈልጉ ፣ ስለ ሰማይ ሰርግ ትምህርት ይሰጣል ሲባል ቀርተው ጓደኛ መያዝ እንዴት ይቻላል ? የሚል ትምህርትን ከቤተ ክርስቲያን የሚናፍቁ ሰዎችን በማሰብ ልቤ ስርቅ አለብኝ ። ጳውሎስ ሊገድል ወጥቶ ሐዋርያ ሆኖ ተመለሰ ። ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ያለው ብዙ ወገን ግን ሊድን መጥቶ ገዳይ ሆነ ። የእስራኤል የመጀመሪያው ንጉሥ ሳኦል አህያ ፍለጋ ወጥቶ ንጉሥ ሆኖ ተመለሰ ። አሁን የያዝነው ምእመን ግን ክርስቶስን ብሎ መጥቶ ሥጋዊ ነገር ይዞ ይመለሳል ። በሰማያዊና በመንፈሳዊ በረከት ተባርከሃል ሲባል አይሞቀውም ፣ በትዳር ተባረክሁ ብሎ ግን የምስጋና መርሐ ግብር ይዘረጋል ። ክርስቶስ ሞተልህ ሲባል ጆሮውን ጥጥ ደፍኖ ልጅ አልወለድሁም እያለ የእግዚአብሔርን ስጦታ ነቢይ ነን ከሚሉ ሰዎች ይፈልጋል ።

ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ አሥራ አራቱ መልእክታቱ ከመተንተኑ በፊት ስለ መጨረሻው የሕይወት ታሪኩ እንዲነግረኝ ፈለግሁ ። ሐዋርያውም፡- “ኔሮ ቄሣርን እወደዋለሁ” አለኝ ። እኔም ድንግጥ አልኩኝ ። ሐዋርያውም፡- “የምወደው እርሱ ባይገድለኝ ሰማዕት ፣ እርሱ ሞትን ባይፈርድብኝ ሰማይን ቶሎ አላይም ነበር ። ደግሞም ለፊልጵስዩስ ሰዎች የምመኘውን ትልቅ ነገር ነግሬአቸው ነበር ። እርሱም ክርስቶስን በሞቱ ልመስለው ነበር ። ይህን ሕልሜን ያሟላልኝ ይህ ንጉሥ ነው ። እጅግ ክፉ በሆነ ሰው እጅግ ደግ ነገር ሆነልኝ ። እንደ ሻማ ብርሃን የሆነችውን ሕይወቴን ለመንጠቅ ሞክሮ ምሽት ከሌለበት ቀን ፣ ከማይጠልቅ ፀሐይ ውስጥ ነፍሴን ጨመራት ። ሰዎች ያጎደሉብህ ሲመስላቸው ብዙ እየጨመሩልህ ነው ። ፣ ያመሰገኑህ ሲመስላቸው ግን ብዙ እያጎደሉብህ ነው ። ኔሮ ቄሣር በ54 ዓ.ም ሥልጣን ይዞ እስከ 64 ዓ.ም. በክርስቲያኖች ላይ ጥላቻ አልነበረውም ። በድንገት ግን ይህ ጠባዩ ተለወጠ ። ሰዋዊ የሆነ ቅንነት በድንገት ይለወጣል ። ምክንያቱም የመቅረዝ ብርሃን ዘይት ካልተሞላ እንደሚጨልም ፣ የሰው መልካምነትም ከእግዚአብሔር ጸጋ ካልተጠጋ እየጎደለ ይመጣል ። እጅግ ክፉ ነገሥታት የሚባሉ ደግ የነበሩ ናቸው ። ሰው ለደግነታቸው የሰጣቸውን ክፉ ምላሽ ይቆጥሩና በአቅማቸው ልክ ክፉ ይሆናሉ ። ሰው የሚያጠፋው የአቅሙን ያህል ነውና ጥፋታቸውም ምድር የማትችለው ይሆናል ። ኔሮን ቄሣር ለሥልጣንና ለምቾት የነበረው ስስት ወደ እብደት እየወሰደው መጣ ። ሥልጣንን ማፍቀር እብድ ያደርጋል ። በዚህ ምክንያት እናታቸውን የገደሉ ፣ ወንድሞቻቸውን የሰየፉ አያሌ ናቸው ። ሥልጣን ዕለታዊ እንጂ ዘላቂ ወዳጅ የለውም ። ሥልጣንን ከሥልጣን ውጭ ሲያዩትና ሲቀመጡበት እይታው ለየራስ ነው ። የምቾት ፍቅር ያሳብዳል ። ምክንያቱም ብዙዎች እየተራቡ ስለ ትርፍ ነገር ማሰብ በራሱ መንፈሰ እግዚአብሔርን ስለሚያርቅ ነው ። ራስ ወዳድነት ከእግዚአብሔር መጽናናት ይለያል ። 

ሐዋርያው ክርስቶስን በሞቱ ለመምሰል ሲመኘው የነበረ ሐቅ ነው ። ዛሬ ክርስቶስን በትንሣኤ ኃይሉ ፣ ድሆችን ባጠገበበት በረከቱ ፣ ባሕር ላይ በተራመደበት ብርታቱ ሊመስሉት የሚፈልጉ ፣ ተአምርን እንደ ትርኢት እያሳዩ ሀብትን ለማከማቸት የሚከጅሉ ብዙ ክርስቲያኖች አሉ ። ወይም አለን ። ሐዋርያው ግን ክርስቶስ በሞተበት መንገድ በአልጋ ፣ በአስታማሚ መሐል ፣ በሐኪም እርዳታ ውስጥ ሆኖ ሳይሆን በሰማዕትነትና በዓለም በመገፋት ለማለፍ ይሻ ነበር ። በርግጥ ክርስቶስ ሲሞት ቤዛ ፣ ሐዋርያው ሲሞት ሰማዕት ነው ። ሐዋርያው ስለ ክርስቶስ ሞተ ፣ ክርስቶስ ግን ስለ እኛ ሞተ ። ሐዋርያው አሁንም ሳይታክት የልቤን መሻት የአንደበቴን ጥያቄ ለመሙላት ተነሣ ። 

“በ67 ዓ.ም. ሐምሌ 5 ቀን በሮም አደባባይ ለሰማዕትነት ስቆም ሐዋርያውና ትልቁ አባት ጴጥሮስ ተይዞ መጣ ። እኔም ከኢየሩሳሌም ተከስሼ ለቄሣር ይግባኝ ብዬ መጥቼ ነበር ። ያድነኛል ያልሁት ያ ቄሣር ግን የበለጠ ፍርድ አዛባብኝ ። ሁለት ዓመት አሥሮ እንደ ገና የቁም እስረኛ አድርጎ ፈታኝ ። ከዚያም ለመጨረሻ ጊዜ ታስሬ ለሰማዕትነት በአደባባይ ቆምሁ ። ሐዋርያው ጴጥሮስን ሳየው ልቤ ተጽናና ። እግዚአብሔር አንዳችንን ለአንዳችን መጽናናት ብቻ ሳይሆን የጥንካሬ ምንጭ ያደርገናል ። እኔም ሐዋርያውን ሳስብ ትዳሩንና የሽምግልና ክብሩን ሳያስብ ለመሞት በመምጣቱ ልቤ የበለጠ ጨከነ ። ክርስቶስ ከትዳርም ከልጅም በላይ እንደሆነ ተረዳሁ ። ለመፍራት ሽምግልና ጥሩ ምክንያት ነበረ ፣ ሐዋርያው ጴጥሮስ ግን ራሱን ያሳመነውን ምክንያት ክርስቶስን ያሳምነዋል የሚል ፌዝ ውስጥ አልገባም ። ከቃሉ ይልቅ ምክንያታቸውን የሚያምኑ ፣ መለኮትን ማታለል እንደሚችሉ የሚያስቡ ፣ ለእግዚአብሔር የሰጡትን ሕይወትና ዘመን እንዲሁም በረከት መልሰው የሚወስዱ እንደ ሐናንያና ሰጲራ የሞት ፍርድን ይቀበላሉ ። ሐዋርያው ጴጥሮስም እኔን ባየ ጊዜ በረታ ። ልጄ የሚሆን የራሱ የቤት ቍጥርና የራሱ የግል ኑሮ የሌለው ጳውሎስ እንዲህ ሲጨክን ፣ ዓለም ቀረብኝ ብሎ ሳያዝን ፣ በደስታ ሰማዕት ለመሆን ሲመጣ እኔማ የበለጠ መበርታት አለብኝ ብሎ ወደ ገዳዮቹ በፍጥነት ቀረበ ። ገዳዮቹም ሞትን መሸሽ የሰው ተፈጥሮ ሳለ ወደ  ሞት መፍጠን ምን ዓይነት የልብ ቆራጥነት ነው ብለው አሰቡ ። አምላካችን ግን እንደ ሌሎች ነገሥታትና ጣኦታት ሙቱልኝ ሳይለን የሞተልን መሆኑን ማወቅ ነበረባቸውና ይህን ገለጥሁላቸው ። እነርሱም እየተቆጡኝ ያደምጡኝ ነበር ። ያመንሁትን ከመመስከር በላይ ላምንሁበት ዋጋ ስከፍል ዋጋ አስከፋዮቹ የበለጠ የማመልከውን እየወደዱት ይመጣሉ ። እውነት ላልሆነ ነገር በደስታ የሚሞት የለምና ብለው ወደ ክርስቶስ ይጠጋሉ ።” 

“ወታደሮቹና የሞት አስፈጻሚዎቹም ጳውሎስ ውርደት ባለበት የመስቀል ሞት እንዳይሞት ብለው አዘዙ ። ሮማዊ ዜግነት ያለው በመስቀል ሞት አይቀጣምና ። ጴጥሮስ ግን በመስቀል ሞት ይቀጣል ሲሉ ወዲያው ከአፋቸው ነጥቆ እኔ የምሞተው የቁልቁሊት ተሰቅዬ ነው ብሎ ወታደሮቹ እግር ሥር ወድቆ ለመነ ። እኔም ግራ ገባኝ ። ወታደሮቹም እጅግ በከፋ ሁናቴ ለመሞት መወሰኑን ማመን አቃታቸው ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ግን፡- “እንደ ጌታዬ ተሰቅዬ ለመሞት ሕሊናዬ አይፈቅድልኝም ፣ የቁልቁሊት ስቀሉኝ” አለ ። አንደኛው ወታደርም ልቡ በክርስቶስ ፍቅር መወጋት ጀመረ ። ግዳጁ ነውና የሞት ፍርዱን ለማስፈጸም ተነሣ ። እኔም ከሥጋዬ ማደሪያ ተለይቼ ወደ ሰማይ መጓዝ ጀመርሁ ።”

በሰማይ ወደብ ላይ የመሰከርሁለት ክርስቶስ ከአእላፋት መላእክት ጋር ሁኖ ሊቀበለኝ መጣ ። የድል ነሺ የመለከት ድምፅ እጅግ ያስተጋባ ነበር ። እልልታው ሲሰማ ውስጤን እንደ መብረቅ ይሰነጣጥቀው ነበር ። በምድር ላይ የኖርሁበትን ዘመን ሁሉ የሚክስ ያ ሰዓት ነበረ ። የብሉይ ኪዳን ደጋግ አባቶች ፣ የአዲስ ኪዳን አማንያን የተባረኩት ቅዱሳን በታላቅ ሽብሸባ ፣ መቆሚያ በሌለው ቅኔ ይዘምሩ ነበር ። ከዝማሬው የተነሣ ራሴ ሊያመልጠኝ ይታገለኝ ነበር ። የሚገርመው ያንን ቅኔና ቋንቋ ሰምቼው አላውቅም ፤ ከዚያች ቅጽበት ጀምሮ ግን አብሬ መዘመር ጀመርሁ ። የበገናው አንዱ አውታር ሲመታ ዳርቻ እስከ ዳርቻ ይሰማ ነበር ። አሥሩ አውታር ሲነካ ታላቅ መናወጥ ይከሰት ነበር ። ከአጀቡ የተነሣ ክርስቶስ ጋ እንዴት ልድረስ ። ሁሉም የደስታ አበባ ያስታቅፉኛል ። ከአቤል ጀምሮ ያረፉትን ሰማዕታት እያገኘሁ ከሺህ ዓመታት ጋር በአንድ ቅጽበት ውስጥ እየተነጋገርሁ ነበር ። ያለፈውና የሚመጣው ዘመን ሁሉ አሁን ሆኖልኝ ነበር ። በምድር የሰዓት አቆጣጠር ስንት ዘመን እንደ ፈጀብኝ አላውቅም ። የደስታውና የዝማሬ ጅረት ግን ልክ አልነበረውም ። በመጨረሻ የሰበክሁትን ክርስቶስን ለማግኘት ወደ ክብሩ ፀዳል ቀረብሁ ። በምድር ላይ እንደ ነበረው በትሕትና አልነበረም ። በአይሁድ ሸንጎ ተከስሶ ሲቆም አይቼው ነበር ። አሁን ግን ዓይን ሊያየው አይደፍርም ። ሳገኘው ዘልዬ የምጠመጠምበት ይመስለኝ ነበር ። እንዳልቀርበው ግርማው ፣ እንዳልርቀው ሞገሱ ይታገሉኝ ነበር ። እርሱም ወደ ራሱ አቅርቦ ሳመኝ ። ታጅቤም ርስቴን ተቀበልሁ ።” 

ሐዋርያው እነዚህን ነገሮች ምነው ባልጨረሰ እያልሁ ጭንቀት ያዘኝ ። “አንተ ገና በሥጋ ማደሪያ ውስጥ ነህና መስማት በምትችለው መጠን እንጂ በእውነቱ ልክ አይነገርህም” አለኝ ። እኔም “እውነት ነው” ብዬ እጅ ነሣሁ ።

ይቀጥላል

የካቲት 2 ቀን 2013 ዓ.ም

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም