መግቢያ » ትረካ » ጳውሎስን አገኘሁት » ጳውሎስን አገኘሁት /ክፍል 3/

የትምህርቱ ርዕስ | ጳውሎስን አገኘሁት /ክፍል 3/

 

ሐዋርያውን ትክ ብዬ አየሁት ። እርሱ ግን የዛሬ መልኬን ሳይሆን ነገ የምፈጽመውን የሃይማኖት ገድል እያሰበ ድልን በሚመኝ መንፈስ ያየኝ ነበር ። ማዕበል የሚያሰጋው መሐል ባሕር ላይ እንጂ ወደቡ ላይ ለደረሰች መርከብ አይደለም አለኝና “እኛ በዕረፍት ነን ፣ እናንተ ግን ገና በተጋድሎ ላይ ናችሁ፤ እኛ ስለ እናንተ እናስባለን ፣ ሰማይ በምድር ያሉትን ምእመናን እየጠበቀ ነው” አለኝ ። ያለፉት አባቶች ለሚመጡት ልጆች ቢመክሩ ፣ ያሉት ልጆች ያለፉትን አባቶች ቢያከብሩ ምንኛ መልካም ነው ! ብዬ አሰብኩ ። የሞቱት ስለ ዕረፍታቸው ሙታን ቢባሉ የሕያዋን አምላክ የተባለው በእነዚህም ቅዱሳን ላይ ነውና ሕያዋን ናቸው ። 

ሐዋርያው አሁንም፡- “ወደ አገሩ የገባ አምባሳደር/እንደራሴ ከመንግሥቱ ጋር የሚኖር ፣ የክብር ዕረፍት ያለው ነው ። እናንተ ግን ከአገራችሁ ርቃችሁ ያላችሁ አምባሳደሮች ናችሁ በርቱ ። በገዛ አገሩ አምባሳደር ሁኖ የሚሾም የለም ። አምባሳደር ስትባሉ ከአገራችሁ ርቃችሁ እንዳላችሁ እንድታውቁ ነው ። ራሱን ጠርቶ አምባሳደርነቱን ትቶ ወደ አገሩ የሚመለስ የለምና የላካችሁ ጌታ እስኪጠራችሁ ድረስ ታገሡ እንጂ ደርሶ ሞታችሁን አትለምኑ ። የዕድሜ ልክ መከራችሁ በመንግሥተ ሰማያት የአንድ ደቂቃ ደስታ ይካሳል ። እኛ ክብሩን ስናይ ምነው ተመልሰን በተጋደልን ብለን ጠየቅን ። እግዚአብሔር ግን ወደ ዕረፍቴ የገባውን ወደ ውጭ አላወጣውም አለን ። ሰማይ ስትደርሱ ትልቅ የመሰላችሁ አገልግሎት ያንስባችኋል ። ዘመኔን ለእግዚአብሔር ሰጥቼ እያላችሁ በደስታ ሳይሆን እግዚአብሔር የእኔ ዕዳ አለበት በሚል ስሜት ስትናገሩ ይሰማል ። ክርስቶስ ሕይወቱን እንደሰጣችሁ ፣ ብዙ ኃያላን መላእክት ሳሉት እናንተን ደካሞቹን መውደዱን ትረሳላችሁ ። ዘመናችሁ ለእርሱ ካልሆነ ለሥጋና ለሰይጣን ለዓለም መሆኑ የማይቀር ነው ። ባዶ ጊዜ የለም ። እግዚአብሔር የሚከብርበት አሊያም ሰይጣን የሚያድፋፋው ዘመን ይኖራችኋል ። ስትመለስም የብዙዎችን ድካም ተሸክመው የእነርሱን ጥቂት ድካም የሚሸከምላቸው አጥተው በማዘን ወደ ዓለም የተመለሱትን አገልጋዮች በርቱ ፣ ሰማይ እየጠበቃችሁ ነው ፤ ዘመኑ እያለቀ ነውና ልደቱ ሲደርስ በምጥ አትሙቱ በላቸው ። ይህን የምልህ ወደ ላይ ስትወጣ ሰውን የሚለያይ የድንበር መስመር የለም ። ሰው ግን የድንበር መስመርን በአሳቡ እየሳለ ከእኔ ወገን አይደለህም ይላል ። ክርስትና ግን የእኛ ላልሆነው ፍቅርና ደግነት ማሳየትም ነው ። እግዚአብሔር ዓለምን እንደ አንድ ቤት ስለሚያውቃት አንድ ፀሐይን አደረገላት ። ከቤታችሁ ወጥታችሁ የሰማዩን ጠፈር ተመልከቱ ። አጭሩ ጣራ ቅርብ እያሳያችሁ ነው ። በምክር አድልኦ የለምና ይህን መልእክት ለሁሉ አድርስልኝ አለኝ ። ዞር ስል ቅዱሱ መልአክ ትክ ብሎ ያየኛል ። መላእክት በጆሮ ሳይሆን በልብ የሚሰሙ ሰዎችን ይወዳሉ ። እግዚአብሔርን መፍራት ባለበት ሠራዊቱ ይገኛሉ ። ሠራዊቱ ንጉሡንና የንጉሡ የሆነውን ሁሉ እንደሚጠብቁ መላእክትም የእግዚአብሔር የሆኑትን ምእመናን ይጠብቃሉ ። 

ሐዋርያው ጳውሎስ የሕይወቱን ታሪክ ሊነግረኝ ተነሣሣ ። እኔም የረሳ መስሎኝ ላስታውሰው ስል በልቤ፡- “በሰማይ ዝንጋዔ የለም ። የሚያዘናጋው ያ ሥጋ እንደ አዳፋ ልብስ ወልቋል” አለኝ ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በቁሙ ይህን ሁሉ ሊነግረኝ ሲሻ መቀመጥ ቢችል ብዬ አሰብኩ ። እርሱ ግን፡- “ከምድር ገና በመምጣትህና የሰማይ ድንበር ላይ ስላለህ አላወቅህም እንጂ መቀመጥም ፣ መቆምም ፣ መነሣትም ፣ መንበርከክም እነዚህ ያለ ድካም የሚፈጸሙ ናቸው ። እንደቆምን ሺህ ዓመት ሊፈጸም ይችላል ። የእግዚአብሔር ደስታ ኃይላችን ነው ። ልጆቹ ወደ መንግሥቱ በሰላም ስለገባን ሁልጊዜ ደስ ይለዋል ። እኛም እንደ ቆምን ሳናውቀው ሺህ ዘመን በምድር ተቆጥሯል እንባላለን ። ሺህ ዘመንን እንደ አንድ ቀን የሚያደርግ የእግዚአብሔር ደስታ ነው ። እናንተ ዓመቱ ቶሎ አለቀ እያላችሁ ታዝናላችሁ ። ቶሎ ያለቀላችሁ ስለጣፈጣችሁ ነው ። መራራ ቀን አንዱ ሰዓትም የዓመት ያህል ነው” አለኝ ። 

ሐዋርያው ቀጠለ፡- “እኔ በኪልቅያ አገር በዋና ከተማዋ በጠርሴስ የተወለድሁ አይሁዳዊ ነኝ ። አይሁዳውያን ከባቢሎን ምርኮ በኋላ በአገራቸው አድረው አያውቁም ። ሃይማኖታቸውን በልባቸው አድርገው በመላው ዓለም ተበትነው ነበር ። ይህም በመላው ዓለም ያለውን ቋንቋ እንዲያውቁ ረድቷቸዋል ። በእነርሱ ዓለምን መስበክ የፈለገው እግዚአብሔር በዚህ የቋንቋ ሀብት ባርኮአቸዋል ። ስደትንም የሚባርክ እግዚአብሔር ነው ። ከባቢሎን ምርኮ በኋላ የሜዶንና የፋርስ ጥምር መንግሥት ቀጥሎ የግሪክ መንግሥት ከዚያም የሮም መንግሥት መጣ ። እኔ የተወለድሁት ሮም መላውን ዓለም በምትገዛበት ፣ መንገዶች ሁሉ ወደ ሮም ያደርሳሉ ተብሎ በሚነገርበት ዘመን ነው ። የሮማውያን አገዛዝ መላውን ዓለም በመንገድ ያገናኘና በመላው ዓለም ለመዘዋወር ፈቃድ የማይጠየቅበት ፣ ለንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት እውቅና በመስጠት ብቻ ሁሉም አገር በራሱ ሥርዓት የሚኖርበት ነበር ። ክርስትና በዚህ ዘመን ሲመጣ ዘመንን መርጦ ነው ። እኔም በሮማ ግዛት ውስጥ በመወለዴ ሮማዊ ዜግነትን በልደት አግኝቻለሁ ። በዚያ ዘመን ሮማዊ መባል ትልቅ ክብር ያለውና በአጥቢያ ዳኞች የማይዳኝ ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ከተማ የሚዳኝ ነበር ። ለዚህ ነው በኢየሩሳሌም በተያዝሁ ጊዜ ወደ ሮም ለይግባኝ የሄድኩት ። በሮማ ዘመን ወንጌል መስበክ መልካም ነበረ ። ድንበሮች ክፍት፣ መንገዶች ምቹ ነበሩ ። ሮማውያንም እስከ ስድሳ አራት ዓመተ ምሕረት ድረስ ክርስትናን የሚቃወሙ አልነበሩም ። እግዚአብሔር የኦሪት መጻሕፍትን ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በሦስተኛው ዘመን ወደ ግሪክ ቋንቋ እንዲተረጎም አደረገ ። መላው ዓለም ወደ ግሪክ ቋንቋ አዘንብሎ ዓለም አቀፋዊ ቋንቋ ግሪክኛ ሁኖ ነበር ። መላው ዓለምም ብሉይ ኪዳንን ለማንበብ ዕድል አገኘ ። የክርስቶስ ልደት በቤተ አሕዛብም ይጠበቅ እንደነበር በበለዓም ትንቢት ፣ በሰብአ ሰገል ስግደት መረዳት ትችላለህ ። እኔም ባልመካበትም ፣ ሰማይ ለደረሰ ምድር ትንሽ ብትሆንም ሮማዊ ዜግነቴን ለወንጌል ማሮጫ ፣ የግሪክ ቋንቋ ማወቄን ለመስበኪያ አውዬው ነበር ። መርጠን ሳይሆን ያለንን ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብር ስናውለው ያለን ነገር የጸና ይሆናል ። በአካል ጠርሴስ ብሆንም በልቤ ግን በሃይማኖት አገሬ በኢየሩሳሌም ነበርሁ ። ከቤተሰቦቼም የዕብራይስጥን ቋንቋ ፣ ከረበናቱም የብሉይ ኪዳንን ትምህርት ተምሬአለሁ ። በወቅቱ የነበረውን የሄለናውያንን ወይም የግሪኮቹን የአኗኗር ዘይቤ ጠንቅቄ መርምሬአለሁ ። ስለ ክርስቶስ የሚጎዳኝን ብቻ ሳይሆን የሚጠቅመኝን ትቼ መጥቻለሁ ። የሚጎዳቸውን መተውማ ብልጦችም ያደርጉታል ፣ እኔ ግን የሚጠቅመኝን ነገር ትቼ ሀብትና ሥልጣንን ከንቱ ነው ብዬ ለክርስቶስ ገብሬአለሁ” አለኝ ። 

ሐዋርያው ሲናገር ልቤ በደስታ ይዘል ነበር ። በሰማይ ያሉ ስለ ታሪክ የማያውቁ ይመስለኝ ነበር ። ሰማይ የምንሄደው ለመላቅ እንጂ ከእውቀት ለማነስ አይደለም ። የምንኖረው የእኛ ኑሮ ፣ ያለፉት ሺህ ዘመናትና የሚመጡት ዓመታት ሁሉ በሰማይ በሸራ ላይ እንደ ተወጠረ ሥዕል ይታያሉ ። ቀጣዩን ሊነግረኝ ሲል እኔም ቆይ እንደ ገና ላሰላስለው አልሁት ። ቅዱሳን የሚያግዙ እንጂ የሚታዘቡ አይደሉምና የጌታን ትዕግሥት አሳየኝ ። እኔም የልብ አውቃ ወዳጅ እፈልግ ነበርና ለካ ብዙ ወገን በሰማይ አለኝ አልኩ ።

ሐዋርያው ጳውሎስም ወደ ቀጣዩ ትረካ ከማለፉ በፊት፡- “አንተንና የአንተ የሆኑትን እግዚአብሔር ይባርክ” ብሎ ሐዋርያዊ ቡራኬ ሰጠኝ ። እኔም ቆሜ ከመቀበል ዝቅ አልኩኝ ። እኔ ተባርኬ የእኔ የሆነው ካልተባረከ የፈረሰ አጥር ነው ፣ የእኔ የሆነው ተባርኮ እኔ ካልተባረክሁ በበረከቴ የምሞት ነኝ ። አዎን ጌታ ሆይ እኔንና የእኔ የሆነውነ ባርክ ። 

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታሕሣሥ 23 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም