መግቢያ » ትረካ » ወለተ ኢያኢሮስ » ወለተ ኢያኢሮስ / 7

የትምህርቱ ርዕስ | ወለተ ኢያኢሮስ / 7

 

ጌታችን መርዶ የገጠመውን ኢያኢሮስን ፣ የልጁን ሞት እንደ ዋዛ የሰማውን አባት ፣ በአደባባይ “ልጅህ ሞታለች” ተብሎ በሕዝብ ፊት የተረዳውን የምኵራብ አለቃ፡- “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ” አለው ። አዳኝ አገኘሁ ፣ ያስጨነቀኝን በሽታ የሚያስጨንቀውን ወደ ቤቴ ይዤ መጣሁ እያለ እያንዳንዱን እርምጃ እንደ ኪሎ ሜትሮች እየቆጠረ ፣ ቅርብ የነበረው እልፍኙ ርቆበት ፣ ደቂቃው ዓመት ሁኖበት ፣ አምላኩን ሊያሳይ ፣ ያመንኩት ትልቅ ነው ብሎ ሊመካ የጎመዠውን ሰው ወሽመጡን የሚቆርጥ ፣ እምነቱን የሚጋፋ ነገር ተናገሩት ። ጌታችን ግን እነርሱን ትቶ ላመነው የእምነት ድምፅ አሰማው ። ጌታችን ከከሀድያን ጋር አይከራከርም ፣ አማንያንን ግን ያሳምናል ። “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ” አለው ። ለበሽታ ስጸልይ ሞት መጣብኝ ብለህ በመጸለይህ እንዳትደነግጥ “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ ።” በቤቴ የምስጋና መሥዋዕት ላቀርብ ነው ስል የልቅሶ ዜማ ሊያስተጋባ ነው ብለህ አትፍራ ፤ በአደባባይ ለምኜ በአደባባይ ላፍር ነው ወይ ? ድሮስ ክርስቶስን የተከተለ ምን ያገኛል ? ብለው የምኵራብ ባልደረቦቼ ሊያላግጡብኝ ነው ወይ ? ብለህ አትጨነቅ ፤ “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ ።” የቤቴን ገበና አደባባይ አውጥቼ ራቁቴን ቆሜ ልቀር ነው ወይ ? ብለህ ለሰው እንደ ነገርህ አድርገህ እንዳትሸማቀቅ ፤ “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ ።” 

ኢያኢሮስ በዚህ ሰዓት ከማመን ውጭ ምንም ነገር የለውም ። ባለ መድኃኒት ጋ የሚሄድበት ፣ ቅጠል የሚበጥስበት ፣ መላ የሚሞክርበት ጊዜ አይደለም ። የሞት ሐኪም ፣ የሞትም መድኃኒት በዓለም ላይ የለም ። ያለው ዕድል ማመን ብቻ ነው ። የእናንተ ጉዳይ ያለቀ ነው ሲባል የሚቀረን ነገር ማመን ብቻ ነው ። የምታስታምሙት ጉዳይ ሞቷል መቅበር ብቻ ነው ብለው ሲያረዱን የሚቀረን እምነት ብቻ ነው ።  ታሪካችሁ መክኗል ፣ ሕይወታችሁ ወይቧል ሲሉን የሚቀረን ማመን ብቻ ነው ።  የደበቅነው በሽታውን ቢሆንም ሞት ግን አደባባይ ያወጣል ። ሁሉ ይሰማዋል ። የተዘጋው ደጅ ሁሉ ሞት ሲመጣ ይከፈታል ። ብቻውን ያስታመመ ብቻውን አይቀብርም ። ሞት አጋላጭ ነው ። ባስታመምነው ቍጥር የባሰበት ፣ በጸለይን ቍጥር የሞተ ጉዳይ ካለ ደስ ይበለን ። ብቻ ክርስቶስን ወደ ቤታችን ይዘን እንገስግስ ። እርሱ ሲገባበት ቤታችን እንደ ቅድሙ አይሆንም ። ልቅሶ በደስታ ዜማ ይለወጣል ። ቃሬዛ የሚሠሩ እንጨቱን ይሰብራሉ ። አቃብሩኝ ተብለው በዕድር ጡሩምባ የመጡ በመዝሙር በእልልታ ይውላሉ ። አሳሳቢው የጉዳዩ መሞት ሳይሆን ክርስቶስን አላደክመውም ብሎ እየመጣ ያለውን ጌታ ቆይ ማለት ነው ። በትሕትና የመጣው ጌታ በጌትነት ይሠራል ። 

ፍርሃት ያጠላበት ኑሮ ውስጥ የሰው ልጆች ያልፋሉ ። ፍቅርን ይፈራሉ ፣ ቀጥሎ መካሰስ ቢመጣስ ብለው ይጨነቃሉ ። ጠብን ይፈራሉ ፣ የጅል ጠብ ከገጠመ ማለቂያ የለውም ብለው ይደነግጣሉ ። ቸርነትን ይፈራሉ ፣ ደግ ሲጠቃ ያያሉ ።  ንፍገትን ይጠላሉ ፣ ካልቀቁ ከሰማይ እንደማይለቀቅ ይሰማቸዋል ። ሁሉን የፈራን ነንና “አትፍሩ” ይለናል ። 

ጌታችን ወደ ኢያኢሮስ ቤት ሲገሰግስ የምሥጢር ደቀ መዛሙርቱን ሦስቱን ጴጥሮስን ፣ ዮሐንስንና ያዕቆብን ይዞ ነው ። ከልጅም ልጅ አለው ። ከደቀ መዛሙርትም ሁሉን እንዲያውቁ የሚፈቀድላቸው የምሥጢር ደቀ መዛሙርት ያስፈልጋሉ ። ሁሉም ልጅ ቢሆንም አባት ለይቶ እናቴ የሚላት ልጅ አለች ። ሁሉም ልጅ ቢሆንም አባቴ እየተባለ የሚጠራ የልጅ አዋቂና መካሪ አለ ። ሁሉን መጋበዝ የመምህርነት ወግ አይደለም ። የምሥጢር አገልጋዮች ያስፈልጋሉ ። ወደ ኢያኢሮስ ቤትም ከእነዚህ የምሥጢር ደቀ መዛሙርት በቀር ማንም እንዳይከተለው ጌታ አደረገ ። ወደ ኢያኢሮስ ቤት ሲቃረብ ብዙ ጫጫታና ልቅሶ ይሰማል ። እንደ ነዋሪነቱ ፣ እንደ አለቅነቱም ፣ እንደ ሕዝብ አገልጋይነቱም የእርሱ ቤት ልቅሶ ደማቅ ነው ። አልቃሾቹም ጌታንና ተከታዮቹን ሲያዩ ተጨማሪ ለቀስተኛ የመጣ መስሎአቸው በእንባ ለመራጨት ፈልገዋል ። ጌታ ግን እንባን ሊገድብ መጥቷል ። ሁሉንም ደቀ መዛሙርት መያዝ ያልፈለገው እንደ ማርታ ቤት አይደለምና ቤቱ እንዳይጨናነቅ አስቦም ነው ። ሐኪም እንኳ በሽተኛ መጥቶለት ያክማል ። እርሱ ግን ራሱ የመጣ ነው ። የሞት መድኃኒት በእጁ አለና በትሕትና ገባ ። የሚታበዩ የሞት መድኃኒት የሌላቸው ናቸው ። የበሽታ መድኃኒት ያላቸው በሚታበዩበት ዓለም ፣ የሞት መድኃኒት ያለው በትሕትና ተጓዘ ። መታበይ እንዳለን እርግጠኛ አለመሆን የሚወልደው ነው ። 

ጌታችን ለቀስተኞቹን ፡- “ስለ ምን ትንጫጫላችሁ ታለቅሳላችሁም? ብላቴናይቱ ተኝታለች እንጂ አልሞተችም” አላቸው ። መንጫጫት ካለ የልጅቱ ነፍስ የወጣው በቅርብ ሰዓት ነው ። ማዜም ካለ ደግሞ ሲረጋጉ የሚቀርብ ሙሾ ነው ። የቅርቡ ሲንጫጫ ፣ ብዙም የማይደነግጠው የሩቁ ያዜማል ። የሚንጫጩ ልቅሶው አይወጣላቸውም ፣ በዜማ የሚያስነኩት ግን እፎይ ይላሉ ፣ ኀዘኑ ይወጣላቸዋል ። ማልቀስ በተገቢው ሰዓት አስፈላጊ ነው ። ያልተገለጠ ኀዘን ቆይቶ ጭንቀት ይሆናል ። የሰለጠነው ምድር የጭንቀት በሽታ ኀዘናቸውን በሳቅ ስለሚያሳልፉት ፣ በቡና ስለሚሸነግሉት ነው ። ብዙ እየቀበርን የማናብደው ኀዘንን የምንገልጥበት ሥርዓትና ዜማ ስላለን ነው ። አይብዛ እንጂ ኀዘን መገለጥ አለበት ። ራስን በመግዛት ፣ ሰውን ባለማስቸገር ፣ የምንናገረውን በመምረጥ ማዜም ማልቀስ አስፈላጊ ነው ። ጌታችን እንኳ እንደሚያሥነሣው እያወቀ በአልዓዛር መቃብር ላይ አልቅሷል ። አለማልቀስ የክርስቲያንነት ሳይሆን የአረመኔነት ምልክት ነው ። ኀዘን በወጉ እንዲገለጥ መጽሐፍ ይነግረናል ። 

ጌታችን አልሞተችም ሲል በርግጥ ነፍስዋ አልወጣም ማለቱ አይደለም ። ለእናንተ ያበቃ ነገር ለእኔ ገና ነው ማለቱ ነው ። ሁሉም ነገር በፊቱ ማለዳ ነው ። ሠርክ የሌለበት አምላክ አለን ። እነዚያ ሲንጫጩ የነበሩ አልቃሾች በጣምም ሳቁበት ። ይህ ሳቅ ከስድብ በላይ ነው ። ሰዎች ሁኔታንና ራሳቸውን በማየት ለነገሮች ድምዳሜ ይሰጣሉ ። እግዚአብሔር ራሱን አይቶ ሲናገራቸው ማመን ይቸገራሉ ። ጌታ ያደረገው ነገር ቢኖር ሁሉንም አስወጣና የብላቴናይቱን አባትና እናት ፣ ሦስቱን ደቀ መዛሙርት አስከትሎ ሬሳው ያለበትን እልፍኝ በሩን ዘጋ ። ሲናገር ሙትም ይሰማዋልና እጅዋን ይዞ “ጣሊታ ቁሚ አላት ። ፍችውም ብላቴና ማለት ነው ።” ለሞተች ልጅ ዓይንሽን ግለጪ ማለትም በቂ አይደለም ወይ ? ቢሉ ጌታ ሲፈውስ ከበሽታው በፊት ወደ ነበረው ማንነት ሳይሆን ከዚያ ወደ በለጠ ኃይል ይመልሳል ። ብላቴናይቱም የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ነበረችና ወዲያው ቆማ ተመላለሰች ። እነዚያ የሳቁ ሁሉ ደነገጡ ፣ መገረም ሞላባቸው ። ጌታችን ይህን ማንም እንዳያውቅ ብሎ አዘዘ ። የምትበሉአትም ስጡአት አላቸው ። ሩቅ አገር ደርሶ ለመጣ እንኳ ምግብ ያሻዋል ። ሰማይ ደርሳ ለመጣች ሩቅ መንገደኛ ምግብ ስጡአት አለ ። የዳኑና ከሞት ያመለጡ ምግብ ያስፈልጋቸዋል ። ሕይወት ቀጣይ የሚሆነው በምግብ ወይም በቃሉ ነውና ። ብዙዎች ከሞት ድነዋል ፣ የቃሉን ምግብ ስላላገኙ ግን ሕይወታቸው ጭል ጭል እያለ ነው ።

ጌታ ለማንም እንዳይናገሩ ማዘዙ  ኢያኢሮስ የምኵራብ አለቃ እንደመሆኑ ብዙ ጠላት እንዳያፈራ ፣ እምነቱ እስኪጠነክር ድረስ ከነፋስ ሊጠብቀው ነው ። ጌታችን ለአቅማችንም ይጨነቃል ። ጌታችን በአንድ ፈውስ ውስጥ ብዙ ፈውስ ይሰጣል ። የሥጋ ፈውስ ወደ ነፍስ ፈውስ ያደርሳል ፣ የነፍስ ፈውስም ወደ ሥጋ ፈውስ ያደርሳል ። ሁለንተናን የሚፈውስ ጌታ ክርስቶስ ነው   ። 

እመኑ ብቻ እንጂ አትፍሩ ።

እግዚአብሔር ልመናችሁን ይፈጽምላችሁ ። 

ተከታታዩ ጽሑፍ ተፈጸመ

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታሕሣሥ 15 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም