መግቢያ » ትረካ » ወለተ ኢያኢሮስ » ወለተ ኢያኢሮስ /6

የትምህርቱ ርዕስ | ወለተ ኢያኢሮስ /6

 

ወንጌሉ ስለ ኢያኢሮስ ሲናገር “አጥብቆ ለመነው” ይላል ። አጥብቆ መለመን ምንድነው ? በቤተ ክርስቲያን ጸሎትም “ቍርጥ ልመናችንን ስማ” የሚል ጸሎት ይቀርባል ። አጥብቆ መለመን ማድረግ ትችላለህ ብሎ ማመን ነው ። አጥብቆ መለመን ሰዓት የለኝምና ድረስልኝ ማለት ነው ። አጥብቆ መለመን እጁን ጨብጦ እግሩ ላይ ተጠምጥሞ አላስኬድህም ማለት ነው ። አጥብቆ መለመን ታላቅ ተማጽኖ ፣ የነፍስ መርገብገብ ያለበት ነው ። አጥብቆ መለመን ብቸኛው መፍትሔ አንተ ብቻ ነህ ብሎ ሌሎች በሮችን ዘግቶ መምጣት ነው ። አጥብቆ መለመን በጉዳዬ ላይ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጅበት ብሎ መንግሥታዊ ሥልጣኑን መጠየቅ ነው ። አጥብቆ መለመን ከልማዳዊ ጸሎት የተለየ ፣ “በሰላም ያሳደርገኝ በሰላም አውለኝ” ከሚለው የፊት መታጠቢያ ጸሎት ጠለቅ ያለ ነው ። አጥብቆ መለመን አቅሜ ደክሟል ፣ ጉልበቴ ተሟጧል ፣ ተስፋዬ ላልቷል ፣ ጉዳዬ ሳይሞት እኔ ልቀድም ነው የሚል የመንፈስ ሲቃ ያለበት ጸሎት ነው ። 

እግዚአብሔር እንዲህ ያለውን ልመና ይወደዋል ። ካንገት ሳይሆን ካንጀት የቀረበ ፣ የራስን ደካማነትና የእርሱን ሁሉን ቻይነት ያመነ ነውና እንዲህ ያለው ጸሎት በእርሱ ዘንድ ሞገስ አለው ። እግዚአብሔር ይሰማል ፣ እኛ ግን በትክክለኛ ጸሎት ውስጥ ላንሆን እንችላለን ። ዙሪያው ገደል በሚመስልበት ፣ ቀኑ ጨለማ ሆኖ በሚታይበት ፣ ተስፋ የታጣ መስሎ በሚሳልበት ዘመን አጥብቆ መለመን መልካም ነው ። አጥብቆ መለመን የእግዚአብሔርን ፈቃድ በራስ ፈቃድ ማስለወጥ ፣ እጁን ጠምዝዞ ክርስቶስን መቀበል አይደለም ። አጥብቆ መጸለይ ከነሙሉ ሸክም ክርስቶስ በሚያልፍበት መንገድ ላይ መውደቅ ነው ። እንደ ክርስቲያን ከጸለይን እንደ እግዚአብሔርነቱ ይሰማል ።

ጌታችን ከእርሱ ጋር ሄደ ። ብዙ ሕዝብም ተከተሉት አጋፉትም ። ያ ሕዝብ አጥብቀው የሚጸልዩትን የሚመለከት እንጂ አጥብቆ የሚጸልይ አይመስልም ። እነ እገሌ የጸሎት ጓድ ናቸው የሚል እንጂ እኔም መጸለይ አለብኝ ብሎ የሚያስብ አይመስልም ። ሦስት ነገሮች እየታዩ መጡ ። 

የመጀመሪያው፡- የማይጸልይ በጸሎተኞች ግን የሚቀና ትውልድ ፣

ሁለተኛ፡- ክርስቶስን በልብ የተከተሉትን ቅዱሳን የሚያደንቅ እርሱ ግን በእግር የሚከተል ትውልድ ፤

ሦስተኛ፡- ክርስቶስን በእምነት የማይነካ ነገር ግን የሚያጋፋ ትውልድ ይታይ ነበር ። እንዲህ ያለ ትውልድ ባለመጸለዩ በሰው ኑሮ ሲቀና ይኖራል ። በልብ ባለመከተሉ የቤተ ክርስቲያን አባል ሆኖ የመንግሥተ ሰማያት መዝገብ ግን የማያውቀው ይሆናል ። ክርስቶስን በእምነት ባለመንካቱ የችግሩ ወንዝ ሲፈስስ ይኖራል ። 

ጌታችን ወደ ኢያኢሮስ ቤት እየተጓዘ ሳለ አሥራ ሁለት ዓመት ደም ይፈስሳት የነበረችይቱን ሴት አገኛት ። እርሷን ለመፈወስና የነፍስ አርነት ለመስጠት ከጉዞው ቆመ ። ኢያኢሮስ ግን፡- 

“እኔ ለምኜ እንዴት ሌላ ሰው ይድናል ?” 

“እኔ በአደባባይ ጸልዬ በድብቅ የነካ እንዴት ይፈወሳል ?” 

“የእኔ ችግር ጊዜ የማይሰጥ ሳለ እንዴት አሥራ ሁለት ዓመት ሳይገድል ለኖረ ችግር ቅድሚያ ይሰጣል ?

“ወደ እኔ ቤት እየተጓዘ እንዴት በአንዲት ሴት ይቆማል ?” አላለም ። 

•  ጸሎተኞች ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ፈውስ ለሚያስፈልገው ሁሉ ይጸልያሉ ። 

•  ጸሎተኞች እግዚአብሔር ለሁሉ በቂ መሆኑን ይቀበላሉ ።

•  ጸሎተኞች ሰው እንዲያያቸውና ምላስ ሁሉ ጸሎተኛ እንዲላቸው ጸሎትን ለማስታወቂያ ሥራ አይጠቀሙበትም ። 

•  ጸሎተኞች እግዚአብሔር የዘገየ ቢመስልም በእኔ አቆጣጠር እንጂ እርሱ ከሞትም ልደትን ማውጣት ይችላል ብለው ያምናሉ ። 

•  ጸሎተኞች ሰው ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ክቡር መሆኑን ይቀበላሉ ።

ኢያኢሮስ የቤቱ ሰዎችና ጎረቤቶቹ ወደ እርሱ እየሮጡ መጡ ። ክርስቶስና ሕዝቡ ሲመጡ አይተው ሰዓቱ ረፍዷል ለማለት ገሠገሡ ። ፀሐይን አቁሞ የሚሠራ የኢያሱ አምላክ መሆኑን ዘንግተዋል ። ጊዜን የፈጠረ ለጊዜ የማይገብር መሆኑን ማወቅ ተስኗቸዋል ። በእርሱ ዘንድ የመጨረሻ የሚባል ሰዓት እንደሌለ ፣ ለሞተው ነገር ሕይወት የሚሰጥ ፣ የሌለውንም እንዳለ አድርጎ መቍጠር የሚችል መሆኑን ገና አላወቁም ። “ልጅህ ሞታለች ስለምን መምህሩን ታደክመዋለህ ?” አሉት ። መምህሩ ግን ሰማይና ምድርን ሲሠራ ረክቶ ያረፈ እንጂ ደክሞት የተቀመጠ አይደለም ። መምህሩ ሰውን ለመፍጠር አልደከመም ፣ ሰውን ሰው ለማድረግ ግን ከሰማይ ወደ ምድር ወርዷል ። 

ልዩነቱ ያለው ኢያኢሮስ እንደ ጌታ እነርሱ እንደ መምህር ብቻ መቀበላቸው ነው ። እርሱ በሽተኛን ይፈውሳል ፣ እርሱ የሞተን ያሥነሣል ፣ እርሱ የሚወዱትን በሞት ላጡ ወገኖች መጽናናት ይሰጣል ። እነዚያ መርዶ አርጂዎች የተጨነቁት ለመምህሩ መድከም ሳይሆን ላለቀ ጉዳይ የዕድር ጉዳይን ለማቀላጠፍ ነው ። አሁን የሚያስፈልገው መምህሩ ሳይሆን የዕድር ሊቀ መንበሩ ነው ። ምክንያቱም ነገሩ አልቋልና ባዮች ናቸው ። የሚጠራ ዘመድ እንጂ የሚጠራ መምህር በዚህ ሰዓት የለም እያሉት ነው ። መምህሩን ስለ በሽታ ጠይቆ ጉዳዩ ወደ ሞት ያደገበት ኢያኢሮስ በአደባባይ ማፈር የገጠመው ይመስላል ። የለመነውን ቀርቶ ያለመነውን እንደሚቀበል ግን ቀጥሎ ያውቃል ። የለመነው ስለ በሽታ ፈውስ ነው ። የሚቀበለው ግን የሞት መልስን ነው ። ስለ ሥጋ ጠይቆ ስለ ነፍስ መልስ ያገኛል ። እግዚአብሔር ከለመኑት በላይ አትርፎ ይሰጣል ። አለቀ አበቃ በተባለ ነገር አዲስ ፀሐይ ያወጣል ። ይህን የሚያደርገው እኛ ኢያኢሮስ ስለሆንን ሳይሆን እርሱ እግዚአብሔር ስለሆነ  ነው ። ነገር ግን ቍርጥ ልመና ማቅረብ ይገባል ። ነገሩ ከድጡ ወደ ማጡ ፣ ከበሽታ ወደ ሞት ሊያድግ ይችላል ። እግዚአብሔርን የችግራችን ትልቅነት አይመልሰውም ፣ የእምነታችን ማነስ ግን ይመልሰዋል ። እግዚአብሔር እንደሚችል ማመን እንጂ እንዴት እንደሚችል መመራመር ከፍጡር አይጠበቀም ። 

ጌታችን ለኢያኢሮስ የተነገረውን ለእኔ ብሎ ሰማ ። ኢያኢሮስ የስንፍናም የብርታትም ድምፅ ሳያሰማ ጌታችን ቀድሞ መልስ ሰጠ ። ኢያኢሮስ ስለሞት ሰማ ። ጌታችን ግን፡- “እመን ብቻ እንጂ አትፍራ” አለው ። የሚጠበቀው መውጣት መውረድ ፣ የሚፈለገው አቅምን መፈተሸ ፣ የሚያሻው የጉዳዩን ክብደት ከዕድርተኛ ጋር መምከር አይደለም ። ማመን ብቻ ነው ። እምነት ያስፈለገው የሚታይ ነገር ሲጠፋ ፣ የማይታየውን ለማየት ነው ። እናንተም እመኑ ብቻ እንጂ አትፍሩ ።

በብርሃን ዋሉ!

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም