መግቢያ » ትረካ » ወለተ ኢያኢሮስ » ወለተ ኢያኢሮስ /5

የትምህርቱ ርዕስ | ወለተ ኢያኢሮስ /5

 

የሰገደ ሰው ቁመቱ ሜትር ከሰማንያ አይደለም ። እጅግ ያነሰ ነው ። የሰገደ ሰው ሰማይንና አካባቢውን ለማየት ድፍረት የሌለው ተነሣሒ ነው ። የሰገደ ሰው መንገዴን ጨርሻለሁ አዲስ ጅምር ስጠኝ ባይ ነው ። የሰገደ ሰው ፊቱን ለሰጠው አምላክ ፊቱን የሚሰጥ ነው ። የሰገደ ሰው የበረከት ናፍቆት ያለበት “ካልባረከኝ አልለቅህም” የሚል ተማጻኝ ነው ። የሰገደ ሰው ይህችን ዓለም አላይም ብሎ በጌታው ለመታየት ዓይኑን የጨፈነ ነው ። የሰገደ ሰው ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ዝቅ ያደረገ ፣ እኔ ትቢያና አመድ ስሆን ከጌታዬ ጋር ለመነጋገር እንዴት ደፈርሁ ? የሚል የእግዚአብሔርን ትልቅነት የተረዳ ነው ። የሰገደ ሰው ትልቅ ምስጋናና ልመና ያለው ነው ። የሰገደ ሰው የእግዚአብሔርን አምላክነት የተቀበለ ፣ አላሳልፍህም ብሎ መንገድ የዘጋ ነው ። ኢያኢሮስ በዚያ ሁሉ ክብሩ የትልቆች ትልቅ ለሆነው ክርስቶስ ዝቅ አለ ። 

ብዙ ሕዝብ ሲንጫጫ ይሰማል ፣ ኢያኢሮስ አይደለም ወይ ? የሚሉት ወሬ አጣሪዎች የሚሰነዝሩትን የነገር ፍላጻ ያዳምጣል ። የጥብርያዶስ የባሕሩ ሞገድ በጆሮው ያስተጋባል ። እርሱ ግን ክርስቶስን እሺ ለማሰኘት ያነባል ። ክርስቶስ እሺ ሲለን ሁሉም ነገር ሺህ ይሆንልናል ። 

ኢያኢሮስ፡- “ታናሽቱ ልጄ ልትሞት ቀርባለችና እንድትድን በሕይወት እንድትኖር መጥተህ እጅህን ጫንባት” ብሎ አጥብቆ ለመነው ። ታናሽቱ ልጅ የመጨረሻዋ ፣ ታናሽቱ ልጅ የዕድሜ ድሀዋ ፣ ታናሽቱ ልጅ ጨዋታ ያልጠገበችው፣ ታናሽቱ ልጅ መወለድና መሞት ምን ማለት መሆኑን ያለየችው ልትሞት ቀርባለች አለ ። ታናሽቱ ልጅና ኢያኢሮስን የሚያመሳስላቸው ነገር አለ ። ሁለቱም ጥግ ላይ ያሉ ነዋሪዎች ናቸው ። እርስዋ የልደት ፣ እርሱ የሞት ጥግ ላይ ያሉ ናቸው ። እርሷ የልደት በር ላይ እርሱ የሞት ደጃፍ ላይ ቆመዋል ። እርስዋ ለመጀመር እርሱ ለመጨረስ ትግል ላይ ናቸው ። ነገር ግን ታሪክን የሚለዋውጥ ክስተት መጣ ። ነዋሪዋ ወደ ሞት ፣ ሟቹ ኀዘን ወዳየለበት ኑሮ ለመሄድ ጉዞ ጀመሩ ። ስለማደጓ ሲያስብ ስለሞቷ ማሰብ በመጀመሩ ማሰብን ጠላው ። 

ታናሽቱ ልጅ በየዘመናቱ ለሞት ቀርባለች ። ሕፃናቱ ያለ ተንከባካቢ በጎዳና ቀርተው ፣ ልጆቹ ያለ መሪ በራሳቸው መንገድ ጠፍተው ፣ ብላቴኖቹ ያለ ሥነ ምግባር በሱስ ቀንበር ተይዘው ፣ ወጣቶቹ የሚያዝንላቸው ጠፍቶ ለጦርነት ሲታጩ ይታያሉ ። ታናናሾች ልጆች ለሞት ተቃርበዋል ። የሚበሉትን ምግብ እንጂ የሚኖሩበትን ዓለም አልገነባንምና ለሥጋና ለነፍስ ሞት ተቃርበዋል ። ኢያኢሮስ በየዘመናቱ ያስፈልጋል ። በክርስቶስ እግር ሥር ወድቆ ለትውልድ የሚያምጥ ያሻል ። 

ኢያኢሮስ ለሞት መቃረቧን ተናገረ ። እርሱ ጠዋት ወደ ምኵራብ ሲወጣ የነበረውን ክስተት ተናገረ እንጂ እውነቱ ታናሽቱ ልጅ ሞታለች ። ጉዱን አልሰማም ። ስለ በሽታ የሚያነባው ሞት እንደመጣ ፣ ስለሞት ዋዜማ የሚናገረው መቃብር ሊወርሰው መሆኑን አላስተዋለም ። ያለ መስማት መጽናናት ፣ ያለ መስማት ደስታ ብዙ ነው ። ካልሰሙት አያውክም ። የልጅ ሕመምና ሞት ግን እንዳልሰማ ለመሆን የሚጥሩበት አይደለም ። ለሕመምዋ ብቻ ሳይሆን ለዕድሜዋ ታናሽነት እንዲያዝን ጌታን ተማጸነው ። ለአንዳንድ ሰው የሚለቀሰው ለዕድሜው ብቻ ሳይሆን ለጅምርነቱ ነው ። ሞት ወግ ነው ፣ ያለ ወጉ የሞቱት ግን ያሳዝናሉ ። ደግሞም ሕፃናት የየትኛውም አገር ዜጋና የየትኛው ወገን ጎሣ አይደሉም ፤ የሁሉም የሰው ዘር አባልና ወገን ናቸው ። ሕፃናት ጎሣና ብሔር የላቸውም ። የቀለም ጦርነት የለባቸውም ። የሀብት ውድድር የሥልጣን መጠፋፋት አይታይባቸውም ። ክንፎቻቸው የተደበቁ መላእክት ናቸው ። ስለ ሕፃናት ሞት ፣ ስለ ወጣቶች በጅምር መቅረት የማያሳዝነው ሰይጣን ብቻ ነው ። 

ኢያኢሮስ ለሞት የተቃረበችውን ታናሽቱን ልጅ እንዲፈውስለት ለመነው ። የሚሰሙትና የሚያነብቡት ክፉ የሆነባቸው ፣ በታወከ ቤተሰብ የሚገሥጽ ባጣ መንደር የሚኖሩ ፣ ሁሉም ነገር ለሰውዬው ትክክል ነው በሚል ባሕል የተጠመቁ ወጣቶች ታናናሽ ልጆች ለሞት እየተቃረቡ ነው ። የሚያዩትና የሚሰሙት የሚመርጡትን ነው ። በዚህ የመረጃ ዘመን ላይ ያሉ ወጣቶች በዚህ ሥልጣኔ ውስጥ ተደብቀዋል ። ሰው የሚፈልገውን ብቻ እያየ የሚኖር ከሆነ የሕይወትን ተግዳሮት አያውቀውም ። ከሰው ጋር የሚኖር የማይፈልገውን ያያል ፣ ይሰማል ። በዚህ ምክንያት ይናደዳል ፣ ይበሳጫል ፣ መልስ ለመስጠት ከራሱ ጋር ይታገላል ። እነዚህ ነገሮች የሰውዬውን ሁለንተና ስለሚያነቃቁት ከጭንቀትና ከድባቴ እየወጣ እንዲመጣ ይረዱታል ። የመንደሩ ፍጭት ፣ የጎረቤቱ ጉንተላ በመልካም ለሚጠቀምበት የሚያነቃቃው ብዙ የሰውነት ክፍል  አለ ። በኢንተርኔት ጫካ መሽጎ ያለው ትውልዳችን ግን የሚፈልገውን ብቻ ስለሚያይ የሕይወትን ተግዳሮት የማያውቅ ፣ አቅመ ቢስ ትውልድ ነው ።

ኢያኢሮስ እንድትድንና በሕይወት እንድትኖር ለመነ ። ድኖ በሕይወት መኖር ክብር ነው ። ድኖ የሚሞት ፣ ድኖ የሚበድል ፣ ድኖ ያዳነውን በጥፊ የሚመታ ፣ ድኖ ጌታውን “ይሰቀል” የሚል ፣ ድኖ ያዳኑትን ላጥፋ የሚል ብዙ ነው ። ገመድ ያስጣሉአቸውን አገልጋዮች በሸምቀቆ የገደሉ ፣ ያጽናኑአቸውን ካህናት ቀሚስ ገልበው የሰደቡ ፣ ያጠመቁአቸውን አባቶች አላመናችሁም ያሉ ፣ እያመሰገኑ መጥተው እየተራገሙ የወጡ ፣ ድነው የሚያበላሹ ብዙዎች ናቸው ። የኢያኢሮስ ልመና አስገራሚ ነው ። ለሞቱት ብቻ ሳይሆን ለዳኑት መጸለይ በእውነት ይገባል ። ታምሞ የተነሣ እግዚአብሔርን ረሳ እንዲሉ ። ቆመው ያገለገሉአቸውን አገልጋዮች ቁጭ ብለው እናውርድ የሚሉ ፣ የበሉበት የቃለ እግዚአብሔር ገበታ ላይ ምራቃቸውን የሚተፉ አሉና በሕይወት መኖር እጅግ አስፈላጊ ነው ። በሕይወት መትረፍ የአንድ ቀን ሲሆን በሕይወት መኖር ግን የዘለቄታው ነው ። 

ኢያኢሮስ “መጥተህ እጅህን ጫንባት”  አለው ። የክርስቶስ እጆች ወደ ሞት የሚሄዱትን የሚመልሱ ፣ በሞትና በእነርሱ መካከል አንድ እርምጃ የቀራቸውን የሚታደጉ ፣ በሕይወት ለመኖር የሚረዱ ናቸው ። ብዙዎች ለሞት ኖረዋል ፣ ለሕይወት መኖር ግን አልቻሉም ። ለመጠጥ ኑረው ለቅዱስ ቍርባን አልኖሩም ። ለዝሙት ኑረው ለእውነተኛ ፍቅር መኖር አልቻሉም ። እጅ መጫን ኃላፊነት መስጠት ነው ። ከሞት ማምለጥ ኃላፊነት ነው ። በሕይወት መኖር ኃላፊነት ነው ። ኢያኢሮስ ልጁ ከሞት መንጋጋ እንድትወጣ ብቻ ሳይሆን በሕይወት እንድትኖር ለመነ ። ይህንንም በልማድ እንደ ሆነላት ሳይሆን በእግዚአብሔር እቅድ እንደተፈጸመላት ፣ ዳግመኛም መኖር ኃላፊነት መሆኑን እንድታውቅ “መጥተህ እጅህን ጫንባት” አለው ። 

ከሞት መትረፍ ፣ በሕይወት መኖር ኃላፊነት መሆንን ተረድተን ይሆን ? 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ታህሣሥ 11 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም