መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » የበረሃ ምንጭ

የትምህርቱ ርዕስ | የበረሃ ምንጭ

 

ወዳጄ ሆይ !

በቀጥታ መስማት ያለብህን ከሦስተኛ ወገን አትስማ ። ከሦስተኛ ወገን ስትሰማ ቀዝቅዞ ሊያሰንፍህ ፣ ግሎ ሊያስጨንቅህ ይችላል ። በመጠኑ የምትሰማው ጉዳይህ ፊት ራስህ ስትቆም ብቻ ነው ። የሦስተኛ ወገን ጠባይ ብዙ ዓይነት ነው ። አገላለጽ ባለማወቅ የሚያድበሰብስ ፣ የቃላት ድህነት ኖሮበት መርዶ አርጂ የሚመስል ፣ ነፋስ ሊወልድ ብዙ ሰዓት የሚያምጥ ፣ ነገርን አቃልሎ ዋጋ የሚያስከፍል ፣ አጋንኖ በእሳት ላይ ቤንዚን የሚያርከፈክፍ አለ ። ዝምታን የመረጠን ሰው ተናገር ብለህ በጣም አትጎትጉት ። “የእንጦጦ መምህር ቢናገር ባመት ፣ ያውም እሬት” እንዲሉ ንግግር ባለማወቅ የሚያስቀይምህ ሊሆን ይችላል ። 

ወዳጄ ሆይ !

የጥንት እውቀት በመደበቅ ፣ የዛሬ እውቀት ግን በመስጠት ይከብራል ። በዚህ ዘመን እውቀትን ብትደብቅ አላዋቂ ትሆናለህ ። የእውቀት ስስት የጠፋበት ዘመን በመሆኑ ልናደንቅ ይገባናል ። የምትወደው ሰው ጋር ለመኖር በዝግ ልብ ሁነህ አትቅረበው ። ብዙ አለመጠበቅ ፣ ይቅር ማለትና ማለፍ እንዲሁም ጠባዩንና የአስተዳደግ ተጽእኖውን መረዳት ይገባሃል ። የምትወዳቸው አንተን የማወቅ መብታቸውን ከከለከልካቸው ይጠሉሃል ። በዝግ በር እንደማይገባ ዝግ በሆነ ልብም ወዳጅ አይስተናገድም ። 

ወዳጄ ሆይ !

ዛሬ ያበሳጨህን ነገር በትዕግሥት አሳድረው ። ከቻልህ አሠልሰው ። በልኩ ማየት ትጀምራለህ ። ፈጥነህ መልስ መስጠት ጸጸትን ፣ ተስፋ መስጠትም ቁጭትን ያመጣል ። እንደ ሄሮድስ ከእውነት ስሜትህን ካስቀደምህ ፣ ይደርን ከጠላህ የቅዱሳንን አንገት የምትቀላ ትሆናለህ ። ፈጣን ፍርድ በሚሰጥባቸው አገራት የተፈረደባቸው በሞቱ በማግሥቱ ንጹሕ ነበሩ ይባላል ። 

ወዳጄ ሆይ !

ተፈሪ ሰው ለመሆን አትሻ ። የግርማ ሞገስ ድግምትም አትፈልግ ። ግርማ ሆኖ የሚጋርድ ፣ ሞገስ ሆኖ የሚያስወድድ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። የምወደደው በምሰጠው ስጦታ ነው ብለህ ገንዘብህን አትጨርስ ። ፍቅርን እንደ ቻልህ ጠብንም ቻል ። ነገር ከፈራህ እያስፈራሩ ይበዘብዙሃል ። አፈኞችን ሳይሆን ቅዱሳንን አክብር ። የራቁትን በማሰብ ውስጥ ከሆንህ በፊት የቆሙትን ማየት ያቅትሃል ። ለተወለዱት እንጂ ለሞቱት ምንም ማድረግ አትችልምና በሥጋ ከሞቱት ጋር በስሜት አትሙት ። የሞተ ወዳጅህን መርዳት ከፈለግህ ቤተሰቡን ጠይቅለት ። መንፈሱ እንዳያዝንብህ የተከለውን አትንቀል ። የሚያይ አምላክ አለውና አያየኝም ብለህ አደራውን አትካድ ።

ወዳጄ ሆይ !

ሩኅሩኅነት ልፍስፍስ ፣ ጠንካራነት ጨካኝ ፣ ቸልተኛነት ዳተኛ አያድርግህ ። መምሰልን የመሆን ምትክ አታድርገው ። እርቦህ እንደ ሰረቅኸው ጠግበህም አትስረቅ ። በአፍህ ያለውን ሳትውጥ ለሌላ ጉርሻ አትጨነቅ ። እንዳለ ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነውና በሚለዋወጠው ሥርዓት አትደነቅ ። የከፈለ የከፈለውን ነገር ካልወሰደ ያስጨንቅሃል ፤ ዋጋ ከፍሎ ለገዛህ ጌታ ካልሆንህ ልታስብ ይገባል ። 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 20 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም