መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሚበላና የሚወራ አይታጣም

የትምህርቱ ርዕስ | የሚበላና የሚወራ አይታጣም

 ባልና ሚስቱ ወደ ገበያ ሲወጡ አህያ ላይ ተሳፍረው ይጓዛሉ ። ሰዎችም አዩአቸውና፡- “እንዴት ሁለቱም አህያ ላይ ተቀምጠው ይሄዳሉ ? ለአህያዋ አያስቡም ወይ ?” አሉአቸው ። እነርሱም ይህን ትችት ሰምተው ባል በአህያዋ ተቀምጦ ሚስት በእግሯ ልትሄድ ተስማሙና ጉዞ ጀመሩ ። ያዩአቸው ሰዎች ግን፡- “ምን ዓይነት ጨካኝ ቢሆን ነው ሚስቱን በእግር እንድትሄድ የሚያደርጋት ?” አሉ ። ባልም፡- “እኔ ልውረድና አንቺ በአህያዋ ላይ ተቀምጠሽ እንጓዝ” አለ ። ሚስቲቱም በአህያዋ ላይ ተቀምጣ ባልዋ በእግሩ መጓዝ ጀመረ ። ያዩአቸው ሰዎችም፡- “ምን ዓይነት ዘመን መጣ ? ሚስት ባልን ማክበር ተወች” አሉአቸው ። በዚህ ጊዜ ባልና ሚስት ግራ ተጋቡና ሁለቱም በእግራቸው እየተጓዙ አህያዋን መንዳት ጀመሩ ። በዚህ ጊዜ ያዩአቸው ሰዎች፡- “እንዴት ያሉ ሞኞች ናቸው ? በአህያ መገልገል እንኳ አያውቁም” አሏቸው ። 

ሰነፎችና አላዋቂዎች ተናብበው የሚሠሩ ናቸው ። አንዱ ላንዱም አሳልፎ ይሰጣል ። ስንፍና ወደ አለማወቅ ያደርሳል ። ማወቅ ዋጋ የሚያስከፍል ፣ ከብዙ ምርጫዎች የሚሻለውን መምረጥ የሚጠይቅ ነው ። ሺህ ንባብ ፣ ሺህ ትምህርት ባለበት በዚህ ዘመን የሚሻለውን ያልመረጠ የወሬ እንጂ የእውቀት አባት መሆን አይችልም ። ገበያ ውስጥ ብዙ ዓይነት ምርት አለ ። ይሁንና ሁሉንም ይዘን አንገባም ። የሚያስፈልገንን ፣ አቅማችን የሚችለውንና ያማረንን ገዝተን እንገባለን ። ብዙ ዓይነት እውቀትና መረጃ ባለበት ዘመን የሚያስፈልገውን ፣ የሚችለውንና ያማረውን መምረጥ ካልቻለ ዘመኑን በፍለጋ ይጨርሳል ። ሰነፎች በማያስፈልጋቸው ነገር ጊዜ የሚያጠፉ ፣ የሚያስፈልጋቸው ጋ ሲደርሱ ጊዜ የሚያጡ ናቸው ። ለማያስፈልገው ነገር የነበረው ጉልበት ለሚያስፈልገው ነገር መዋል ይችላል ። ለወሬ አቅም አጠረኝ ያላሉ ሰዎች ፣ ለእውቀት ግን አቅም አጠረኝ ይላሉ ። እውቀት ለመኖር በምንመገበው ምግብ የምንሰበስበው ሀብት ነው ። ለትምህርት ተብሎ የሚበላ ልዩ ምግብ የለም ። እውቀት በዚህ ዘመን በመዳፋችን ላይ የተቀመጠ ነው ። ባለመምረጣችን ግን ተጎድተናል ። 

ስንፍና ቀላል ነገር አይደለም ። ስንፍና አምላክ የለም የሚያሰኝ የክህደት መገኛ ነው ። ስንፍና ንዋይ ስለመሰብሰብ እንጂ ስለሞት የማያስብ ነው ። /መዝ. 52፡1፤ ሉቃ. 12፡20/ ስንፍና ስለሌሎች አስተያየት ሲሰጥ የሚውል ነው ። 

የተሰጠን ጊዜና አቅም ለሚመለከተን ነገር ብቻ የሚበቃ ነው ። የሚመለከተን ነገርና የማስፈልግበት ቦታ የቱ ነው ? ካልን በቂ አቅምና ጊዜ አለን ። ሰዎችን ለመተቸት አደራ የተቀበልን መስሎን ከተሰማን ስህተት ነው ። በሕሊና ፣ በዜግነት ፣ በመንፈሳዊነት ግዴታ ግን የማናልፋቸው ነገሮች ፣ ፍርድ ልንሰጥባቸው የሚገቡ ጭካኔዎች ፣ ትክክል አይደለም የምንልባቸው ሚዛናዊነቶች በጣም ያስፈልጉናል ። የራሳችንን ኑሮ ረስተን ግን የግለሰቦችን ጓዳ ስንተች መዋል ተገቢ አይደለም ። ባለቤቱ ፈቅዶ ችግሩን ነቅሰን እንድንነግረው ምክር ካልጠየቀን በቀር ሲዘልፉ መዋል ፣ አግድም አደግነትን የሚገልጥ እንጂ መልካም ሰብእናን የሚያሳይ አይደለም ። 

ከቤታችን መውጣት ስንጀምር የሚቀበለን ነገር ቢኖር ትችት ነው ። ትችትን የሚፈራ ሰው በሩን ቆልፎ መቀመጥ አለበት ። በሩን ከፍቶ የወጣ ሰው ይተቻል ። ላስተምር ያለ በነፍስ ነጋዴዎች ፣ ልጻፍ ያለ ማንበብ በማይወዱ ሰዎች ወይም ንባባቸውን ለቁማር በሚጠቀሙ ሰዎች ፣ ላገልግል ያለ በሕዝብ በሚገለገሉ ወገኖች ይተቻል ። ትችት ፈርተው ዝም ያሉ ምሑራን ፣ መስጠት ያቆሙ ሀብታሞች ፣ የማይወስኑ ባለሥልጣኖች ብዙ ናቸው ። በእግዚአብሔር ዘንድ ተምሮ ዝም የሚል ፣ ሀብት እያለው የሚነፍግ ፣ ሥልጣን እያለው የማይወስን የተጠሉ ናቸው  ። የምንሄድበትን ወስነን መውጣትና የሚመጣውንም ዋጋ መተመን ከቻልን ትችቶች መንገድ ላይ አያስቀሩንም ። ተቺዎች ባያስቆሙ ማዘግየት ይወዳሉ ። ተቺዎች እንደ እነርሱ የቆመ ሰው ማብዛት ዓላማቸው ነው ። የሚሄዱና የሚሠሩ ሰዎችን ሲያዩ የሕሊና ወቀሳ ስለሚያመጡባቸው እነርሱን በማስቆም ዕረፍት ለማግኘት ይፈልጋሉ ። ተቺዎች ራሳቸውን በብዙ ማጽናኛ የሚመግቡ ናቸው ። የሚናገር መሳሳቱ ፣ የሚራመድ መደናቀፉ አይቀርም ። ተቺዎች ግን እንኳን አልተናገርኩ ብለው በአዋቂዎች ፣ እንኳን አልተራመድኩ ብለው በወደቁት ይስቃሉ ። እውቀት ከሌለው ጨዋነት መሳሳት ያለበት የእውቀት ንግግር ይሻላል ። ብዙ ጊዜ ለመሳሳት የማይደፍር ተመራማሪ መሆን አይችልም ። ቤተ ሙከራ የምንለው ስፍራ የመሳሳቻ ስፍራ ነው ። ብዙ ስህተቶች ግን አንድ እውነትን ያወጣሉ ። በዕድሜ እየበሰልን ስንመጣ መውደቃችንን እየወደድነው እንመጣለን ። 

በጉዞአችን ላይ ተቺዎች አራት ዓይነት ትችቶች ይሰነዝሩብናል ። የመጀመሪያው ትችት የርኅራኄ ጥያቄ ያለበት ነው ። ያገለግላሉ ግን ደመወዝ ይላሉ ፣ ይጽፋሉ ግን ውድ ገንዘብ ይጠይቃሉ ። እንዴት ለሕዝቡ አያዝኑም ? የሚል የርኅራኄ ጥያቄ ያነሣሉ ። መንፈሳዊ ሰዎች ሳሉ እንዴት ውድ ቤት ፣ እንዴት ውድ ልብስ ያስፈልጋቸዋል ፣ ብዙ ድሆች አሉ አይደለም ወይ ? በማለት በርኅራኄ ስም ጥያቄ ለማሥነሣት ይሞክራሉ ። ይሁዳ ለጌታ በተረጨው ውድ ሽቱ ተቃዋሚ ነበረ ። ተቃውሞው ግን መንፈሳዊ ካባ የለበሰ ነበር ። “ይህ ሽቱ ለሦስት መቶ ዲናር ተሽጦ ለድሆች ያልተሰጠ ስለ ምን ነው? አለ።” ዮሐ. 12፡5 ። መጽሐፉ ግን ሲመልስ እንዲህ ይላል፡- “ይህንም የተናገረ ሌባ ስለ ነበረ ነው እንጂ ለድሆች ተገድዶላቸው አይደለም፤ ከረጢትም ይዞ በውስጡ ከሚገባው ይወስድ ስለ ነበረ ነው።” 

እነዚህ ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ሲሠራ ዋናው ሰው መሠራት አለበት የሚሉ ፣ ቀለም ሲቀባ እኛ አገራችን በሰማይ ነው የሚሉ ፣ ለአገልጋዮች በጎ ሲደረግ ዓለም ዓለም ሸተተ የሚሉ ናቸው ። እግዚአብሔር ግን ልብን የሚመዝን አምላክ ነው ። 

በጉዞአችን ላይ የሚነሣው ሁለተኛው ትችት የፍቅር ጥያቄ ያለበት ነው ። ሁሉን በእኩል አያዩም ፣ ላለውና ለሌለው እኩል አይደርሱም ፣ የቀደመውን ሰው ኋላ በመጣ ሰው ይለውጡታል ። ቅድሚያ ለመጣው ክብር የላቸውም  የሚሉ ትችቶች ይነሣሉ ። ይህ የፍቅር ጥያቄ ያለበት የሚመስል ነው ። ነገር ግን የማያድጉ ፣ ከአንቀልባ የማይወርዱ ፣ ሁልጊዜ እሹሩሩ ከሚወዱ ሰዎች የሚመነጭ ትችት ነው ። የቱንም ያህል ጠንቃቃ ብንሆን ከሰዎች ነቀፋ ነጻ አንሆንም ። እነዚህ ሰዎችም የቀደሙ የሚሏቸውን ሰዎች ያስተባብሩና የመብት ጥያቄ መጠየቅ ይጀምራሉ ። ባንቀጥልም አፈራርሰን እንሄዳለን ብለው ይነሣሉ ። ለእኔ ያልሆነ ለማንም አይሁን ብለው በቅናት ጥላሸት ይቀባሉ ። 

በጉዞአችን ወይም በራእይ መንገዳችን ላይ የሚገጥመን ሦስተኛው ትችት የክብር ነው ። የበላዮቻቸውን አያከብሩም ፣ በእውቀት ለሚበልጡአቸው ንቀት አለባቸው ፣ ያሳደጉአቸውን የሚገድሉ ናቸው ፣ ለመንፈሳዊነት ዋጋ አይሰጡም ፣ ባለሥልጣናትን ይንቃሉ የሚል ክብር መሳይ ያለበት ትችት ይነሣል ። ይህ ትችት ከምሑራንና አቅም ካላቸው ባለሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የሚውል ነው ። ጌታን ይሰሙ ከነበሩ ሕዝቦች መካከል ጥቂቶቹ ከአፉ ቃል ለቅመው ለአይሁድ የሃይማኖት አባቶች ፣ ለሮማ የፖለቲካ መሪዎች ለመክሰስ ነበር ። ይህኛው ትችት ስደት ፣ መከራና ሞት ለመጋበዝ የሚነሣሣ ነው ።

በመንገዳችን ላይ የሚገጥመን አራተኛው ትችት የሞኝነት ስድብ ያለበት ነው

። ከፈተናውና ከመከራው የተነሣ ሁሉን ትተን ስንቀመጥ ፣ ይስፋችሁ ብለን ወንበሩን ጥለን ስንሄድ ፣ አንደበታችንን ለዝምታ ፣ እጆቻችንን ጽሑፍ በቃኝ ለማለት አሳልፈን ስንሰጥ ምን ዓይነት ሞኞች ናቸው ? ይሉናል ። አባቶች ስንቱን ታግሠው ነው ለክብር የበቁት በማለት ግብ የለሽ ሰው መሆናችንን ለማወጅ ይፈልጋሉ ። ጥለው ወደቁ ፣ አስክደው ካዱ ፣ ደብድበው ተመረሩ ፣ አውግዘው ወጡ እያሉ የሚተቹ ሰዎች አሉ ። ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ እንደሚጮኽ የእኛን ጩኸት እየቀሙ የሚጮኹ አሉ ። 

አዎ ሰው የሚለውን አያጣምና መንገዳችንን መሄድ ፣ እግዚአብሔር ያሳየንን መፈጸም ይገባናል ። ከዚያ በተቃራኒ በዘመናዊው ዓለም ድርጅቴን ተቹልኝ ተብለው የሚከፈላቸው ፣ ጉድለትን አጥንተው የሚያቀርቡ ተቋማት አሉ ። ጉድለትን በፍቅርና ከመፍትሔው ጋር የሚያሳውቅ ካለ ልንከፍለው ይገባል ። ያላየነውን ላሳዩን ዓይኖችም ምስጋና ማቅረብ አለብን ። 

ጌታ ሆይ የጥሪህን ድምፅ እንጂ የተቺዎችን ትችት እንዳልሰማ እርዳኝ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 27 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም