መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » መልከ ብዙ ፣ ፍሬ ባዶ

የትምህርቱ ርዕስ | መልከ ብዙ ፣ ፍሬ ባዶ

“በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል ።” /ዮሐ. 15፡7 ።/

እግዚአብሔር እንዲህ አለ፡-

ልጄ ሆይ ፣ የምትውለው በከንቱ ወሬ ፣ የምታድረው ከዓለም ጋር ነው ። የምትኖረው እኔን ከሚያሳዝኑ ሰዎች ጋር ግፋቸውን አወዳሽ ሆነህ ነው ። የምትስቀው ድሀን ለሚበድሉ ፣ ፍርድ ለሚያጓድሉ ጨካኞች ነው  ። አንተን ካልነካህ ዓለም ቢደባለቅ ፣ ደም እንደ ጅረት ቢፈስስ ፣ የእልቂት ዜና ቢሰማ ግድ የለህም ። በቅጡ ሳትታጠቅ የምትሮጠው የኃጢአት ጓደኞችህ ሲጠሩህ ነው ። ከምታውቀው ሰው ጋር ተኮራርፈህ ከማታውቀው ሰው ጋር ስታወራ ፣ የልብህን ስትጫወት ትውላለህ ። ከሚታየው ዓለም ወጥተህ መንፈስ ሆነሃል ፣ መናፍስትን ረቂቃን ወዳጆችንም አበጅተሃል ። የሚያውቁህ እንዳይታዘቡህ ፈርተህ ከማያውቁህ ዘንድ ተራቁተሃል ። ዓለምን ሁሉ ጠቅልለህ ፍትወት ማሰሪያ ውስጥ ከተሃል ። ሁሉን ስለ እኔ መተዉ ሲገባህ ሁሉን ስለ ሥጋ ፈቃድህ ታደርጋለህ ። ለመጸለይ የሥራህን ጫና ታወራለህ ፣ ከሥራ ወጥተህ እስከ እኩለ ሌሊት ግን ከንቱ ነገርን ታስሳለህ ። ቃሌን ለመስማት ዋጋ መክፈልን ትጠየፋለህ ፣ ሕሊናን ለሚያቆሽሽ ነገር ግን ገንዘብህን ትረጫለህ ።

ልጄ ሆይ ፣ የአበባ እርሻ መልክ እንጂ ፍሬ የለውም ፣ የዘመኑ ሰውም ለላዩ እንጂ ለውስጡ የማይጨነቅ ነው ። ነፍሱን በሥጋው የለወጠ ፣ ነጭ ልብን ትቶ ነጭ ልብስን ያፈቀረ ፣ ከእግዚአብሔር መንግሥት ይልቅ ለፀጉሩ የሚጨነቅ ነው ። ፒኮክ ሰው ሲያያት ክንፏን ትዘረጋለች ፣ እዩኝ እዩኝ ትላለች ። አንተም ታይተው የጠፉትን ማሰብ አቅቶህ እኔ ብቻ ርእስ ልሁን ብለህ ትጨነቃለህ ። ዓለም ተረኛ እንጂ ቋሚ ወዳጅ እንደሌላት ረስተሃል ። የበላዮችህን እየናቅህ የበታቾችህን የምታከብር ይመስልሃል ። የበታችህን ያከበርከው እንዲሞትልህ እንዲሳደብልህ እንጂ እንድትሞትለትና እንድትሰደብለት አይደለም ። እናትህን እየናቅህ እጮኛህን ታወድሳለህ ፣ መምህርህን እንቢ እያልህ ፣ ጓደኞችህን ትታዘዛለህ ። 

ልጄ ሆይ ፣ በውስጥህ ያለው ምነድነው  ቃሌ ሳይሆን ቂም ነው ። ፍቅር ሳይሆን በቀል ነው ። ደግነት ሳይሆን ብድር መመላለስ ነው ። በማታስፈልግበት ቦታ በግድ ተገኝተሃል ፣ በምታስፈልግበት ቦታ ደግሞ ጠፍተሃል ። የሚለምኑህን ትተህ ለማይለምኑህ ተገኝተሃል ። ከሌለው እየወሰድህ ላለው ሰጥተሃል ። በቤትህ ያለው የእኔ ቃል አይደለም ፣ ስለዚህ ቤትህ የጭቅጭቅ መድረክ ሁኗል ። እንከን ፈላጊ ሁነህ  ፣ ለደጅ እየሳቅህ ለቤተሰብህ አኩርፈሃል ። የተስፋ ቃላቴን በልብህ ማስቀመጥ እንቢ ብለህ ዓለም ስጋቷን ሞልታብሃለች ። ኃጢአትን እየደፈርህ በሽታን ትፈራለህ ። መግቢያ እንዳበጀም አንዳንዴ በእልህ ብሞትስ ትላለህ ። የምትናገረውን ስለምትሰማ እኔ የምነግርህን እየሰማህ አይደለም ። እኔ ካንተ ጋር ነኝ ፣ አንተ ግን ከእኔ ጋር አይደለህም ። አንተ በልቤ ውስጥ አለህ ፣ እኔ ግን ባንተ  ልብ ውስጥ የለሁም ። ከልብህ አባረኸኝ ፣ በአፍህ ትፈልገኛለህ ።

ልጄ ሆይ ፣ እኔን እንደ መሰላል መወጣጫ አድርገኸኝ ፣ የደረስህ ሲመስልህ ገፈተርከኝ ። ለመውረድም እንደማስፈልግህ ዘንግተሃል ። ይህችን ቀን ስለ እምነትህ ሳይሆን ስለ ታማኝነቴ ሰጥቼሃለሁ ። በእኔ ብትኖር በሁለንተናህ ብታከብረኝ በነገር ሁሉ ብትታመነኝ ፣  እውነት እውነት ብዬ የነገርኩህን አማን አማን ብለህ ብትቀበለኝ መሥዋዕትህ ሥሙር ፣ ልመናህ ግዳጅ ፈጻሚ ይሆን ነበር ።

ምእመኑም እንዲህ አለ፡-

ጌታዬ ሆይ ከሩቅ እየፈለግሁህ  ከልቤ አገኝሃለሁ ። እየለፈለፍኩ የሚያውቅልኝ አጥቼ አንተ ግን ዝምታዬን ታነበዋለህ ። የምከተላቸው እየሸሹኝ አንተ ግን ትከተለኛለህ ። ለመክሰር ባልንጀሮቼን ስፈልግ አንተ ግን መልካም ማትረፊያ ልትሆነኝ ትፈልገኛለህ ። የመሰለኝን ነገር አምነዋለሁ ፣ ግጥምጥሞሽን እንደ ሐቅ አየዋለሁ ፣ ግምቴን እከተለዋለሁ ። አእምሮዬ ከቀናነት ርቋል ። ፍቅርን ማስመሰል ፣ ደግነትን ልፍስፍስነት ይለዋል ። የችግረኞች ወዳጅ ፣ የድሀ አደጎች አሳዳጊ ፣ የሙት ልጆች ሰብሳቢ ፣ የባልቴቷ ደጋፊ አልሆንኩም ። ልቤም እንደ አፌ በሆነልህ ብዬ እመኛለሁ ። ቀትር የጨለመባቸውን እያየሁ የማይመሽብኝ ይመስለኛል ። የታመሙትን እያየሁ የማልታመም አድርጌ ራሴን እቆጥረዋለሁ ። ሕያው ሰላምህን ፣ ከሙት ኃጢአት መካከል የምፈልግ ከንቱ ሰው ነኝ ። ቁራጭ ሥጋ የሆነው ሰው ከዳኝ እያልኩ ምሉዕ በኩለሄ የሆንከውን አምላክ ማስታወስ ዘንግቼአለሁ ።

አምላኬ ሆይ ፣ ሰዎችን ወደ ቤትህ እየጠራሁ እኔ እንዳልወጣ ፣ እያሳመንኩ እኔ እንዳልክድ ፣ ሱባዔ እያዘዝኩ እኔ ዋዛ ፈዛዛ ነገር እንዳልከፍት እፈራለሁ ። የዓለም ወሬ እሬት ፣ ያንተ ቃል ማር ይሁንልኝ ። የተበደለ ይካስ የሚለው ፍርድ አልባነቴ ይወገድ ። የሞተን ትቼ ገዳይን ማጽናናቴ ከእኔ ይራቅ ። ላሸነፈ ክፉ ሳይሆን ለተሸነፈ ደግ ምስክር አድርገኝ ። ፍትሕን ንቄ ሰላምን መፈለግ ከንቱ መሆኑን አስተምረኝ ። አንተ ከእኔ ጋር ስላለህ አመሰግንሃለሁ ፣ ደስታዬ ሙሉ እንዲሆን እኔም ካንተ ጋር ልሁን ። በልብህ ስፍራ ስላገኘሁ አወድስሃለሁ ፣ እባክህን በእኔም ልብ አንተ ንገሥበት ። አንተም ፣ ቃልህም ፣ መልስህም ከእኔ ጋር ለዘላለም ይኑሩ ። አሜን ።

የፍቅር ጥሪ /1
ሰኔ 8 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም