መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ቶማስ ሐዋርያ

የትምህርቱ ርዕስ | ቶማስ ሐዋርያ

 “ነገር ግን ከአሥራ ሁለቱ አንዱ ዲዲሞስ የሚሉት ቶማስ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ ከእነርሱ ጋር አልነበረም ። ሌሎቹም ደቀ መዛሙርቱ። ጌታን አይተነዋል አሉት ። እርሱ ግን፦ የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም አላቸው ።” ዮሐ. 20፡24-25
በሦስቱ ወንጌላት ከሐዋርያት ጋር ስሙ ተጠቅሶ የምናገኘው በዮሐንስ ወንጌል ግን ጥቂት ጠባዩና ድርጊቱ የተጻፈለት ሐዋርያ ቶማስ ነው ። ቶማስ በአረማይክ መጠሪያ ስሙ ሲሆን በግሪኩ ዲዲሞስ ተብሏል ። የሁለቱም ፍቺ “መንታ” ማለት ነው ። አይሁድ በዓለም ሁሉ ተበትነው ይኖሩ ነበርና አንዱን ስም በዕብራይስጥና በግሪክ ቋንቋ መጥራት ልማድ አድርገውት ነበር ። ግሪክ ዓለም አቀፍ ቋንቋ ሲሆን አረማይክ ወይም ዕብራይስጥ ደግሞ የአገር ቤት ቋንቋ ነው ። ኬፋ በአረማይክ ሲሆን በግሪኩ ጴጥሮስ ተብሏል ። የሁለቱም ትርጉም “ዓለት” ማለት ነው ። ጳውሎስ የሮማዊ ስሙ ሲሆን ሳውል ደግሞ የዕብራይስጥ ስሙ ነው ። እንዲሁ በአረማይክ “ቶማስ” ሲባል በግሪኩ “ዲዲሞስ” ተብሏል ።

ቶማስ አስደናቂ ጠባያት የታዩበት ሐዋርያ ነው ። እንደ ግትርና እንደ ተጠራጣሪ ቢታይም እውነተኛ ማንነቱ ግን እንደዚህ አይደለም ። አንድ ነገርን ቶሎ የማይቀበሉና ከተቀበሉ በኋላ የማይለቁ ሰዎች አሉ ። ቶማስ አንድን ነገር ለመቀበል በቂ እውቀት የሚፈልግ ሲሆን ላመነበት ነገርም ቆራጥ የሆነ ሐዋርያ ነው ። ቶማስ ክርስቶስን መከተል ሞትን እንደሚያስከትል አውቆ ዋጋ ተምኖ የሚጓዝ ከክርስቶስ ጋር ለመሞትም ዝግጁነቱን የገለጠ ፣ ደፍሮ ሌሎችንም በማደፋፈር የታወቀ ሐዋርያ ነው ። ሕይወቱንም አስቀምጦ የተከተለ ነው ። ጌታ ወደ አልዓዛር መቃብር እንደሚሄድ በተናገረ ጊዜ፡- ስለዚህ ዲዲሞስ የሚሉት ቶማስ ለባልንጀሮቹ ለደቀ መዛሙርት፡- ከእርሱ ጋር እንሞት ዘንድ እኛ ደግሞ እንሂድ አለ። /ዮሐ. 11፡16 ።/ ይህ ጉዞ ታላቅ መከራ እንዳለበት ሐዋርያው ቶማስ ተገንዝቦአል ። ታላላቅ ተአምራቶች ታላላቅ ፈተናዎችን ያሥነሣሉ ። ጌታችን ከዚህ ቀጥሎ ወደ መስቀል የሄደው በሳምንቱ ነው ። ቶማስ ስለ ክንውኖች ብቻ ሳይሆን ቀጥሎ ስለሚመጡ ነገሮች የሚያይና የሚመዝን ነው ። ምንም እንኳ በጌታ የመከራ ሰዓት አብሮ ለመቆም ባይችልም እውነተኛ የልቡ አሳብ ግን ከክርስቶስ ጋር መሞት ነበረ ። በዚህም አሳብና ኃይል የሚባሉ ነገሮች እንዳሉ እንገነዘባለን ። ሰው ለመቀደስም ለክርስቶስ ለመሞትም አሳብ አለው ፣ ቦታው ላይ ሲደርስ ግን ኃይል ያጣል ። አሳብ ከውለታ የማይቆጠረው በሰው ዓለም ነው ፣ እግዚአብሔር ግን የልብንም አሳብ ያያል ፣ ከውለታ ይቆጥራል ። ቶማስ ልቡ ከክርስቶስ ጋር እንደሚሞት እርግጠኛ ነው ። በራሳችን ላይ ግን የምናውቀውና የማናውቀው ማንነት አለ ። ለዓርብ ዕለት ባይገኝም በሕንድና በፋርስ ወንጌል ሰብኮ በ72 ዓ.ም. በሰማዕትነት አርፏል ። እስክንበረታና እስክናድግ እግዚአብሔር ይጠብቀናል ።
ቶማስ ያልገባውን ነገር እንደ ገባው ለመምሰል የሚሞክር ሰው አልነበረም ። አንድ ነገር ካልገባው አልገባኝም ለማለት አያፍርም ። በዚህም ምክንያት ወደ ትክክለኛ እውቀት ይደርሳል ። ጌታችን “እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ” በማለት የተናገረው ተወዳጅ ንግግሩ ለቶማስ ጥያቄ የተሰጠ መልስ ነው ። ጌታችን፡- ወደምሄድበትም ታውቃላችሁ ፥ መንገዱንም ታውቃላችሁ”ብሎ ሲናገር ቶማስም፡- ጌታ ሆይ ፥ ወደምትሄድበት አናውቅም ፤ እንዴትስ መንገዱን እናውቃለን ? አለው ።” /ዮሐ. 14 ፡ 4-5/ ሌሎቹ ሐዋርያት የጌታን ንግግር አልተረዱት ይሆናል ፣ እንደ ገባቸው ሁነው ዝም ሲሉ ቶማስ ግን አልገባኝም ለማለት የሚያፍር ሰው አልነበረም ። በእውቀት የሚያድጉ ሰዎች እንዴት በሰው ፊት አልገባኝም እላለሁ ብለው የሚኮፈሱ ሳይሆኑ በትሕትና አልተረዳሁም የሚሉ ሰዎች ናቸው ። የማወቅ መሠረቱ አለማወቅን መቀበል ነው ። ቶማስ ጥያቄ ልፍጠርና ርእስ ልሁን ፣ ሌላውን የማስጮህ ምክንያት ልሁን የሚል ፣ የአትርሱኝ ስእለት ያለበት አይደለም ። አንዳንድ ሰዎች ቆባቸውን ቀደው የሚሰፉ ፣ ያልበላቸውን ነገር የሚያክኩ ፣ መልሱን ደርሰውበት ጥያቄ የሚጠይቁ ፣ የአእምሮ ጡንቻቸውን ለማፍታታት ክርክር የሚፈጥሩ ፣ በሰላም የተቀመጠውን ካላስጮኹ ደስ የማይላቸው ፣ የተረሱ ሲመስላቸው መምህራንን በአጉል ጥያቄ የሚያበሳጩ ናቸው ። ቶማስ ግን ለመረዳት ብቻ የሚጠይቅ ፣ የተማሪነት ቦታውን ያልረሳ ደገኛ ሰው ነው ።
እንኳን ከክርስቶስ ከመምህራንም የምንጠቀመው ዝቅ ስንል ነው ። እየበሰልን ስንመጣ ደስ ከሚያሰኘን ንግግር አንዱ “አልገባኝም” የሚለው ንግግር ነው ።
አውቀን ከጨረስን የምንኖርበት ምክንያት የለንም ። ገና የማናውቀው ነገር መኖሩ ሕይወትን እንግዳ ያደርጋታል ።
ቶማስን የምናገኘው ጌታችን ከሙታን ከተነሣ በኋላ ነው ። ጌታን ያዩት ደቀ መዛሙርት በነገሩት ጊዜ ካላየሁ ካልዳሰስሁ አላምንም አለ ። ከሐዋርያት የጌታን ትንሣኤ ዘግይቶ የተቀበለ ቶማስ ነው ። የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም አላቸው።” ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በቶማስ ንግግር መሠረት ቅዱሳን ክርስቶስን የሚለዩት በችንካሩ ምልክት ነው ። ለአንድ ቅዱስ ሰይጣን “ክርስቶስ ነኝ” ብሎ ተገለጠለት ። ያ ቅዱስ ግን፡ “የችንካሩ ምልክት የት አለ?” ቢለው ሰይጣን እንደ ጉም ተነነ ፣ እንደ ጢስ በነነ ። ጌታችን ቶማስ እንደሚፈልገው ተገልጦ እንዲያምነው አደረገ ። በርግጥም ትንሣኤው ምትሐት ሳይሆን እውነት መሆኑን ፣ የተነሣው የሞተው ክርስቶስ መሆኑን አወቀ ። ቀጥሎ ያለው ንባብ ይህን ይገልጥልናል ።
“ከስምንት ቀን በኋላም ደቀ መዛሙርቱ ደግመው በውስጥ ነበሩ ፥ ቶማስም ከእነርሱ ጋር ነበረ ። ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፡- ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው።” ሰላም ለእናንተ ይሁን የሚለው ማዕበልን የሚገሥጽ ቃል ነው ። እኛ ዳግም ትንሣኤ የምንለው ይህን ቀን ነው ። ጌታችን ለቶማስ ትንሣኤውን የገለጠበት ቀን ነው ። በተዘጋው ደጅ መግባቱ አምላክነቱን ሲያሳይ የተወጋ ጎኑን ማሳየቱ የሞተበትን ሥጋ ጥሎ እንዳልተነሣ የሚያሳይ ነው ። አምላክ በሥጋ ባይሞት ድኅነት አይኖርም ነበር ። በፍጡር ሞት ዓለም አይድንምና ። በተዘጋው በር ሲገባ በተዘጋው የቶማስ ልብም ለመግባት ነው ። ጌታችን ቶማስ እንዲያምነው አገዘው እንጂ አልፈረደበትም ።
“ከዚያም በኋላ ቶማስን፡- ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው ፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን አለው ።” ጌታችን ጎኑ እንዲዳሰስ ፣ የተቸነከሩ እጅና እግሮቹ እንዲታዩ ፈቀደ ። ትንሣኤውን ካላመኑ ሐዋርያት መሆን አይችሉምና ። እኛም ትንሣኤውንም ካላመንን ክርስቲያን መሆን አይቻለንም ። በመጨረሻው ቀን ሲመጣም የተቸነከሩ እጆቹንና እግሮቹን የተወጋ ጎኑን እያሳየ ይመጣል ። ችንካሩ የፍቅር ፊደል ነው ። ይህን ፊደል አንብቦ በክርስቶስ ያላመነ ይፈረድበታል ። ቶማስ ግን አመነ ። ጌታዬ አምላኬም ብሎ መለሰለት።” ጌትነቱንና አምላክነቱን አመነ ። ጌታችንም ጌታና አምላክ ነውና ተቀበለው ።
ደጆች ቢዘጉም ፣ ለማመን ልባችን እየከበደ ቢመጣም ፣ ጌታ ሆይ አምንህ ዘንድ እርዳኝ እንበለው ። እርሱ ራሱን በመግለጥ የታወቀ አምላክ ነው ።
ጸሎት
ጌታዬ ሆይ እያየሁህ አንተን ማየት ፣ እየዳሰስኩህ አምላኬ ማለት አልቻልኩም ። የማምነው በዓለም ወሬ እንጂ በወንጌል አይደለም ። ራሴን አይና በእኔ አቅም አንተን እለካለሁ ። እባክህን በልቶ ካጅ እንዳልሆን እማጸንሃለሁ ። አለማመኔን አንተን በማመን ለውጠው ። ለዘላለሙ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ /11
ግንቦት 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
https://t.me/Nolawii
እባክዎ ይህን ቻናል ይቀላቀሉ፣  ለሌሎች ወገኖቻችንም ያስተዋውቁ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም