መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ሰላማችን

የትምህርቱ ርዕስ | ሰላማችን

 “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ዮሐ. 20፡19
ያለ ቦታው ፣ ያለ ጊዜውና ያለ ሁኔታው የተነገረ ቃል አይደለም ። ቦታው ደጆች የተዘጉበት ፣ ጊዜው ምሽት ፣ ሁኔታውም ቅዱሳን ሐዋርያት በፍርሃት የሚናጡበት ነው ። በምድረ በዳ ላይ ፣ በጥማት ስፍራ እንደ ተገኘ ውኃ በታላቅ ጉጉት የሚቀበሉት መልእክት ነው ። ከቦታ ፣ ከጊዜና ከሁኔታ በላይ ያልሆነ ይህን ሊናገር አይችልም ። ስለ ሰላም የተነገረ የምኞት መግለጫ አይደለም ፣ ሰላምታን ማጣፈጫም አይደለም   ። እንዲህ ያለ ሰላምታ በቀን ሊነገር ይችላል ። አንድ ሰው በምሽት፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ብሎ እቤታችን ቢመጣ መልሳችን “በሰላም ነው?” የሚል ነው ። ጌታ ግን በምሽት “ሰላም ለእናተ ይሁን” አለ ። ምሽትን ማለዳ ማድረግ ይችላልና ። በተዘጋ ደጅ የገባም በተዘጋ ልብ ገብቶ ማረጋጋት ይችላል ። እርሱ የሰላም አለቃ ነው ። አለቃ የበታቹን ናና ሂድ ይለዋል ። ክርስቶስም ሰላምን ማዘዝ ይችላል ። እርሱ ራሱም ሰላማችን ነው ።

ጌታችን በሞቱ ሰማይና ምድርን ፣ ሰውና እገዚአብሔርን ፣ ሕዝብና አሕዛብን ፣ ሰውና መላእክትን ፣ ነፍስና ሥጋን አስታርቋል  ። ሰላም ተሰደው የነበሩት መመለስ ፣ ተራርቀው የነበሩት መቀራረብ ፣ ደስታ አጥተው የነበሩት ደስታ ማግኘት ፣ ተለያይተው የነበሩት አንድ መሆን ፣ ጠላቶች የነበሩት አንድ ላይ መዘመር ፣ ዋጋ አጥተው የነበሩ ነገሮች ዋጋ ማግኘት ነው ። በሰላም ውስጥ ዕርቅ ፣ መመለስ ፣ መቅረብ ፣ መደሰት ፣ ያጡትን ማግኘት ፣ አንድ መሆን ፣ ወዳጅነት አለ  ። ጌታችን ሰላምን ለማምጣት የከፈለው ውድ ሕይወቱን ነው ። ሰላም የእግዚአብሔር ልጅ የሞተበት ትልቅ ርእስ ነው ። ሰላም ውድ ዋጋ ያስከፍላል ፣ ከሄደ በኋላ ግን ዋጋ ለማገኘት ያስቸግራል ። ሰላም ሁሉም ነገር ነው ። ነግዶ ለማትረፍ ፣ ወልዶ ለመሳም ፣ አገልግሎ ለመጦር ፣ አስማምቶ ለመግዛት ፣ ተወዳድሮ ለማሸነፍ ፣ ዘርቶ ለመቃም ፣ አፍቅሮ ለመደሰት ፣ ወጥቶ ለመግባት ፣ ተቀጣጥሮ ለመገናኘት ፣ ደግሶ ለመሰረግ ፣ ሞቶ ለመቀበር እጅግ አስፈላጊ ነው ። ሰላም ማጣት የሚያስከፍለው ዋጋ ከባድ ነው ። የአንድ ዓመት ሁከት የሚያመጣውን ውድቀት የሦስት ዓመት ሰላም አያነሣውም  ። ሰላም ስናጣ ሰዎች ይፈሩናል ። የቀረቡንም ይሸሹናል ። ሰላም የሌለው ምንም ከማድረግ አይመለስም በማለት ይጠሉናል ። የተናቅን ሕዝቦች የሚያደርገን ሰላም ማጣት ነው ። በሰላም ዘመን ገንዘብ የሚያበድሩን በጦርነት ዘመን የጦር መሣሪያ ያበድሩናል ። የእኛ ሰላም ያለው በክርስቶስ እጅ እንጂ ሌላውን በመግደል ውስጥ አይደለም ። ጨው በሁሉ ቦታ ያስፈልጋል ። የጨው ዘር ከቤተ መንግሥት እስከ ድሀ ቤት ተበትኗል ። ጨው በሁሉ ምግብ ላይ ቢገባ ጣዕም ይሰጣል ። ሰላምም ሁሉንም ነገር አስደሳች ያደርጋል ። ጨው ማዳበሪያ ይሆናል ፣ ሰላምም የፍሬያማነት መገኛ ነው ። ጨው ቍስል ይደርቃል ። ሰላምም ብዙ በሽታዎችን ይፈውሳል ። ጨው በረዶውን ያሟሟል ፣ ሰላምም ጠጣሩን ነገር ፈሳሽ ፣ ክፉውንም ደግ ያደርጋል ። ሰላም በሌለበት ካህን መቀደስ ፣ ሰባኪ ማስተማር አይችሉም ። ሰላም በሌለበት ሰው ራሱን ሊያይና ሊለወጥ አይችልም ። ሰላም ሳለች እርካሽ ስትሄድ ግን ውድ ናት ። እናት እያለች ብዙም ጥቅም ያላት አትመስልም ፤ ስትሞት ግን ልጆች ሲበተኑ ፣ አሳዳጊ ሲያጡ ፣ ቤቱ ሲቀዘቅዝ ፣ ስምምነት ሲጠፋ ፣ የሁሉን አመል የሚሸከም ሲታጣ ፣ ተጎዳሁ ባይ ሲበዛ ፣ ጎዳሁ የሚል ሲጠፋ ያን ጊዜ ዋጋዋ ይታወቃል ። ሰላምም እንደ እናት ናት ።
ጌታችን ኀዘንም ደስታም ያወካቸውን ደቀ መዛሙርት ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው ። ማዕበሉም የማዕበሉም ጌታ ካወከን አስቸጋሪ ነው ። መጸለይና አለመጸለይ ሁለቱም አንድ ከሆነብን እንደ ገና ራሳችንን መመርመር አለብን ። ደቀ መዛሙርቱ ሞተ ሲባል እንዳዘኑ ተነሣ ሲባል ሊደፍሩ አልቻሉም ። በነፍሳቸው ላይ ማዕበል ማዕበልን እየጠራ ይቀጣጠል ነበር ። አንደኛው ማዕበል ጸጥ ሳይል ለሌላኛው ያስረክባቸው ነበር ። አጥተው ያዘኑ አግኝተው ካላመሰገኑ ፣ ብቻዬን ነኝ ያሉ እግዚአብሔር ሲያበዛቸው ተመስገን ካላሉ አስቸጋሪ ነው ። መልሱ መልስ ያልሆነው ጥያቄው ጥያቄ አልነበረም ማለት ነው ። ጌታችን ግን በመካከላቸው ቆሞ፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው ። ገድለው ወደ ደፈሩት አልሄደም ፣ አዝነው ወደ ፈሩት መጣ እንጂ ። ይህ ቢያንስ ሰውነት ነውና ። ገድለው የሚፈረጥሙ አራዊት ናቸው ፣ ባዩት ክፉ ነገር አዝነው የሚፈሩ ሰዎች ናቸው ። ልብን በእግዚአብሔር ማበርታት ግን እርሱ እምነት ነው ። እንደ ሰውነታችን ብንፈራም እንደ አማኝነታችን መበርታት አለብን ።
ጌታችን፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው ። የንግግር መክፈቻ አይደለም ። የልብን ማዕበል እየገሠጸ ነው ። ራሱ ተናጋሪ ራሱ ሰሚ የሆነውን የሰውን ስሜት እያበረደ ነው ። በእሳት ላይ ውኃ እንደመቸለስ ጌታችን “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው ። በሲኦልም የተሰማው የምሥራች ይህ ነው ። የመውጫው በር ጠፍቷቸው የሺህ ዓመት መንገድ ለተጓዙት ነፍሶች “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው ። ይህ የምሥራች ቅድስት ቤት ክርስቲያን ተናግራ የማትጠግበው ነው ። ካህኑ “ሰላም ለኩልክሙ” ይላል ። በሲኦልና በዝግ ቤት ገብቶ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ያለውን ክርስቶስን ወክሎ መናገሩ ነው ። ሲኦልን ፣ ዝግ ቤትን ፣ ፈሪ ልብን የሚያረጋጋው ክርስቶስ ነው ። ሰላም ካሣ ይፈልጋል ። በደሙ የካሰው ለሲኦል ነዋሪዎች “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው ። እንዲከፍሉ ሳይሆን እንዲቀበሉ ጠየቃቸው ። በዝግ ልብ ላሉም እንዲከፍሉ ሳይሆን እንዲቀበሉ ሰላምን ሰበከላቸው ።
እርሱ ስሙ በተጠራበት የሚገኝ ነው ። በዝማሬ ስሙን ስናወደስ በመካከላችን ነው ። ጸሎት ሲጠፋብን ፣ ሁሉም ነገር አውሬ ሁኖ ሲሳልብን ፣ ማመን ሲቸግረን ፣ ፍቅር ሲቀዘቅዝብን ፣ ተስፋ ሲጨልምብንም በመካከላችን ቆሞ፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ይለናል ። የብርታታችን ወዳጅ ነው ፣ የድካማችንም ዋስ ነው ።
ለደቀ መዛሙርቱ ሰላም ከሰበከ በኋላ ሥልጣንን ሰጣቸው፡- ኢየሱስም ዳግመኛ፡- ሰላም ለእናንተ ይሁን ፤ አብ እንደ ላከኝ እኔ ደግሞ እልካችኋለሁ አላቸው ። ይህንም ብሎ እፍ አለባቸውና፡- መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ ። ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል ፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው ።” /ዮሐ. 20፡20-23 ።/ ኃጢአት ሰይጣን ሰውን የገዛበት ሕጋዊ ሰነድ ነው ። አሁን ግን ኃጢአት ይቅር የማለት ሥልጣን ለአገልጋዮች ተሰጠ ። ንስሐ ፣ ስርየት ፣ ሰላም ተገኘ ። የኃጢአት የመጀመሪያ ውጤት ፍርሃት ነበረ ፣ ሰላምን ከሰበከላቸው በኋላ ሥሩን እንዲያደርቁ ኃጢአትን ይቅር የማለት ሥልጣን ሰጣቸው ። በተዋሕዶ አምላክ ሰው ፣ ሰው አምላክ ሆነ ። አምላክነትን ለዚህ ሥጋ ሲሰጥ ተቀብለናል ፣ ይቅር ማለትንም ለሰው ልጆች ሰጠ ። ኃጢአትን ይቅር ለማለት ማስተማር ፣ ወንጌልን መስበክ ይገባል ። ያን ጊዜ ሰዎች ራሳቸውን በክርስቶስ አይተው ወደ ንስሐ ይቀርባሉ ። ስርየትንም ይቀበላሉ ።
ጸሎት
ጌታ ሆይ ቃል ብቻ ተናገር ብላቴናው ሰላማችን ይፈወሳል ። አሁን ደፍረን አሁን የምንበረግግ ፣ አሁን ታርቀን አሁን ዕርቄን አፍርሻለሁ የምንል ፣ ብላቴና ሰላማችን የታመመብን ነንና እባክህን ቃል ብቻ ተናገርና ፈውስልን ። ሰላማችን ሞቶ እንዳንቀብረው ብቅ ይላል ። ኖሮ እንዳንደሰት ይሰወራል ። እባክህን በተዘጋው ልባችን ገብተህ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” በለን ። የሁከት ምንጩ ይደርቅ ዘንድ አንተ እንዲህ ያለውን ሥልጣን ለሰው ልጆች ስለሰጠህ ምስጉን ነህ ። በከበረው ዙፋንህ ለዘላለሙ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ/ 10
ግንቦት 22 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም