መግቢያ » ትረካ » በተዘጋው የሚመጣ » በተዘጋው የሚመጣ/2

የትምህርቱ ርዕስ | በተዘጋው የሚመጣ/2

 “ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት ፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ ፥ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፡- ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው ።”/ዮሐ. 20፡19 ።/
የጌታችንን መነሣት ቀድመው ያወቁ የሮማ ወታደሮች ናቸው ። ወዳጆቹ ሳያውቁ ጠላቶቹ አወቁ ። ሲሰቅሉት ከትሕትናውና ከፍቅሩ አልተማሩም ። መግደል እየቻለ መሞቱ ትሕትና ፣ ስለ ኃጢአተኞች ራሱን አሳልፎ መስጠቱ ፍቅር ነው ። ሲነሣ ታላቅ ብርሃንና ኃይልን አዩ ። በትሕትና ያልተሳቡ በግርማው  ፣ በፍቅሩ ያልተማረኩ በኃይሉ ቢማረኩ መልካም ነበር ። ሰው ወይ ትሕትና ወይም ግርማዊነት ፤ ወይ ፍቅር ወይም ኃይል ይማርከዋል ። ጌታችን ሰዎች ሁሉ በሚማረኩበት መንገድ ቢገለጽም አላመኑበትም ። ለማመን እንዲችሉ ራሱን አሳያቸው ። ለማመን ካልፈቀዱ ለፍርድ እንዲመቻቹ ምክንያት ያሳጣቸዋል ። ሰዎች በከተማ የተቀመጠውን አገልጋይ “የከተማ ቅዱስ አለ ወይ?” ይሉታል ። በበረሃ ያለውን መናኝ ሰባኪ ደግሞ “የምንኖረውን ኑሮ ፣ የምናልፍበትን ፈተና ሳያውቅ በእኛ የሚፈርድ እርሱ ማነው?” እያሉ ችላ ይሉታል ። ጌታችን በከተማ እየበላና እየጠጣ ፣ መጥምቁ ዮሐንስ በበረሃ እያጠመቀ ማገልገላቸው ተናባቢነት ያለው ፣ የሰዎችን ተቺነት ዝም ለማሰኘትና ለንስሐ ለማብቃት የተደረገ ነው ። ወደ ክርስቶስ ሲመጡ በዘላለም እቅፉ ይሰውራቸዋል ፣ ወደ ዮሐንስ ሲሄዱም ወደ ክርስቶስ ያመለክታቸዋል ። የሮማ ወታደሮች መነሣቱን ቢያረጋግጡም አላመኑበትም ። ማረጋገጥ ማለት ማመን አይደለም ። አረጋግጠው ያላመኑ አሉ ። ክርስትናን እንደ ምርምር ጣቢያ ቆጥረው የትምህርት ማዕረግ የሚደረድሩ የአምልኮ ልብ ግን የሌላቸው አያሌ ናቸው ። ክርስቶስን ማወቅ አስፈላጊ ቢሆንም ማወቅ ግን ከእርሱ ጋር ላለን ግንኙነት መጨረሻው አይደለም ። ክርስትና ከማወቅ ቀጥሎ ማመን ፣ ከማመን ቀጥሎ መኖር ፣ እንደ ገና ታውቆ ወደማይጨረሰው ክብሩ መገስገስ ነው ።

ወታደሮቹ ትንሣኤው እርግጥ መሆኑ ሪፖርት አድርገዋል ፣ የምሥራቹንም በቤተ መንግሥት በማለዳ አድርሰዋል ። በወታደራዊ ሙያቸው መሞቱን አረጋግጠው እንዲቀበር ፈቅደዋል ፣ አሁን ደግሞ መነሣቱን ሪፖርት አደረጉ ። ይህ ለእነርሱ መደበኛ ሥራቸው ነው ። የሃይማኖት ሰዎች ግን አንድ ነገር አስተማሯቸው ። ገንዘብ ተቀብለው ያዩትን እንዲክዱ ፣ ተሰረቀ ብለው እንዲያወሩ አግባቡአቸው ። የሃይማኖት ሰዎች ጋር ያለው ክፋት ረቂቅ ነው ። የዓለም ሰዎች ቢጣሉ ይፈነካከታሉ ፣ የሃይማኖት ሰዎች ውስጡን እንዴት እንስበረው ፣ ዘላቂ ሕመም እንዴት እናስታቅፈው ? ይላሉ ። ሰማያዊውንና ረቂቁን ነገር ያመኑ ሰዎች ካልኖሩበት እንዳመኑት መጠን ይክዳሉ ። ሰው የሚወድቀው በወጣበት ልክ ነው ።
መግደላዊት ማርያም ከወታደሮቹ ቀጥሎ ትንሣኤውን አየች ። ጴጥሮስና ዮሐንስም መቃብሩ ባዶ መሆኑን አረጋገጡ ። ጌታችንም ለመግደላዊት ማርያም ተገለጠ ። ቀጥሎ ለሴቶቹ ሁሉ ተገለጠ ። ለኤማሁስ መንገደኞች ተገለጠ ። የኤማሁስ መንገደኞችም እንደገና ወደ ኢየሩሳሌም ተሰብስበው ወደ ነበሩት ደቀ መዛሙርት መጡ ። እነርሱ ሲመጡ ጊዜው ምሽት ነበረ ። የኤማሁስ መንገደኞችም የክርስቶስን መነሣትና እንደ ተገለጠላቸው ሲተርኩ ሳለ ክርስቶስ ተገለጠላቸው ። ምስክርነታቸውን ሊያትም ተገለጠ ። ስለ እርሱ እያወሩ ሲሄዱ አብሯቸው በኤማሁስ መንገድ የተጓዘ ጌታ ስለ እርሱ ሲመሰክሩ በሰገነቱ ተገለጠ ። እርሱ ስሙ በተጠራበት አለ ። እርሱ የመሰከርነውን ሊያትም ይገለጣል ። ጌታችን ሕይወት ያዛላትን የመከራ ቋጥኝ ስትገፋ የኖረችውን መግደላዊት ማርያምን አስቀደመ ። እርሱ የደካሞችን ድካም ያውቃል ። ትንሣኤውንም ለእርስዋ ቀድሞ ባይገልጥ ኑሮ ትጎዳ ነበር ። ጌታ ቀብራ ለማረፍ ለመጣችው ፣ ለመሰናበትም ሽቱ ለያዘችው  አዲስ ምዕራፍ ከፈተላት ። ሰዓቱን የሚያውቅ አምላክ በሰዓቱ ይደርስልናል ። የኤማሁስ መንገደኞችም ተስፋ ቆርጠው ወደ ፀሐይ መጥለቂያ ይጓዙ ነበር ። እነርሱም በተሰበረ ልብ ፣ ተስፋ በቆረጠ መንፈስ እንዳያድሩ  ደረሰላቸው ። ምሽቱን ግን ለደቀ መዛሙርቱ ተገለጠ ። “አጥብቀው ያሰሩትን ዘቅዝቀው ይሸከሙታል” እንዲሉ ደቀ መዛሙርቱን ስለ ተማመነባቸው እስከ ምሽት ዝም አላቸው ። ቢሆንም እስከዚያው የምሥራቹን ይልክላቸው ነበር ። በቃሉ ቀኑን አውሎ በመገለጡ አሳደራቸው ። ነቢዩ፡- በሰላም እተኛለሁ አንቀላፋለሁም አቤቱ ፥ አንተ ብቻህን በእምነት አሳድረኸኛልና ይላል ። /መዝ. 4፡8 ።/ በሰላም እንዲያንቀላፉ ፣ በእምነት እንዲያድሩ ተገለጠላቸው ።
ቀኑ የሁከት ፣ የመጠራጠር ነበርና ። ሞቶአል የሚለው ኀዘን ነው ፣ ተነሥቷል የሚለው ግን ጥርጣሬ ነው ። ሞት ቁርጥ ነው ፣ ጥርጣሬ ግን ሲወዘወዙ መኖር ነው ። ከካዱት በላይ የሚጠራጠሩት ሲታወኩ ይታያሉ ። ጎረቤት የሚረብሽ ጸሎት የሚጸልዩት ለዚህ ነው ። ያዩት ሰው ሁሉ ላይ መንፈስ አለበት እያሉ የሚገሥጹት ለዚህ ነው ። ምግቡ ላይ ጋኔን አርፏል እያሉ ሲባርሩ የሚውሉት ለዚህ ነው ። አንዱን እግዜር ማመን ትተው የዛርና የቃልቻ ስም እየዘረዘሩ ሲቃወሙ ፣ ያንን የደርግ መፈክር “ይውደም” ሲሉ የሚውሉት ለዚህ ነው ። በግብራችን የምንስመውን ዲያብሎስ ፣ በቃላችን መርገም ከንቱ ጨዋታ ነው ።
በአትክልቱ ስፍራ ለመግደላዊት ማርያም ፣ በመቃብሩ ቦታ ለሴቶች ፣ በኤማሁስ ለመንገደኞች ፣ በሰገነቱ ላይ ለሐዋርያት ተገለጠ ። ቀኑን በሙሉ ሰዎች ሲያደክሙት ዋሉ ። ዓርብ ሙሉ ቀን ለማስታረቅ የደከመው አሁን ደግሞ እንዲያምኑት ደከመ ። እርሱ ወደ ሰው ካልመጣ በኃጢአት ዓይኑ የጨለመው የሰው ልጅ ወደ እርሱ መምጣት አይችልም ። እኛስ ከልጅነት እስከ እውቀት ብዙ እንዳደከምነው ተስምቶን ይሆን ? ስንክድም ስናምንም አላምርብን እያለ አስቸግረነዋል ። ስንክድ ሰዎችን መንቀፍ ፣ አምነን ደግሞ ስንወጋገዝ መኖር እርሱን ያደክመዋል ።
አንዳንዴ ቀትሩ ይጨልማል ። ሙሉ ብርሃን ነው ሲሉት ድቅድቅ ጨለማ ይሆናል ። ምድርም ትከዳለች ። የሚረገጥ እስኪጠፋ እግር መደላደያ ያጣል ። ሰማይ ጠቁሮ ያስፈራል ። እግዚአብሔርም ዝም ያለ ፣ ከቀኑ ጋር ያደመ ይመስላል ። ባል በጫጉላ ቤት ሲሞት ፣ ልጅ ፊት ለፊታችን የጥይት እራት ሲሆን ፣ ጠዋት ጤነኛ የነበርነው ከሰዓት የአልጋ ቁራኝ ስንሆን ፣ ኬክ ይዘው ይመጡልን የነበሩ መርዝ ጋግረው የት ነው ? እያሉ ሲፈልጉን ፣ የቅጥር ተሳዳቢዎች የተሞሉትን ሳንቲም እስኪጨርሱ ሲሰድቡን ፣ አለሁ ያሉን አርባ ክንድ ሲርቁን ፣ እንኳን ሰውን ልባችንን ማመን ሲከብደን የሚያድነንን እንፈልጋለን ። ሁሉም ነገር ዘላለማዊ ጸጥታን የተላበሰ የሚመስልበት የተዘጋ ቀን አለ ። “አምላኬ ሆይ ለምን ተውኸኝ ?” የሚል ጥያቄ አዘል ልመና ፣ ከመጉዳት ስሜታችን የሚወጣ ጩኸት በውስጣችን ያስተጋባል ። የወዳጅ ፊት ቅጭም ቢል ሰማይ ግን አይጠቁርም እንል ነበር ፣ መኖሪያ ቤት እንጂ መርገጫ ምድር አጣሁ እንደማንል እርግጠኛ ነበርን ። ነገር ግን ሰማይም የሚጠቁርበት ፣ ምድርም የሚከዳበት ዘመን አለ ። ሁላችንም ዓርብ አለንና በዚያ ቀን ከተማውን እንዳልሞላን ከከተማ ውጭ እንደ ጉድፍ እንጣላለን ። ስንደሰት ዝም ያሉ ስንሰቀል ሊያዩ ይወጣሉ ። በምድም በሰማይም የተገፋን መስሎ ይሰማናል ። ትልልቅ ተስፋዎች ወደ ትልልቅ ፍርሃቶች ይለወጣሉ ። ዕድሎቻችን ሁሉ የክሳችን አንቀጽ ይሆናሉ ። ምድር ከድታን ስንጠለጠል ፣ ሰማይ ተቀይሞን ፊቱን ሲያጠቁርብን ። ቀትሩ ጨልሞ ሁሉ ሲተወን ፣ እግዚአብሔርም እንደ ሰው የሆነ ሲመስለን ፣ የጸለይነው ጸሎት እንደ ገደል ማሚቱ ለራሳችን መልሶ ሲሰማን ፣ ካህናት ከሳሽ ፣ ንጉሥ ወቃሽ ሲሆንብን ፣ ሚሊየኖች ለአንድ እኛነታችን ሲያድሙብን ያን ቀን የዓርቡን ባለ ጽዋ ፣ ክርስቶስን እናስብ ። በቀደመበት በድል ያስከትለናል ። ለቀኑና ለስሜታችን አሳልፎ አይሰጠንም ። ዓርብ ቀትሩ እንደ ጨለመ ፣ እሑድ እኩለ ሌሊቱ ይበራልናል ። ያን ቀን የምስጋና ደቦ ጠርተንም ውለታውን ለመዝለቅ ፣ ክብሩን ለመዘመር አንችልም ።
አቤቱ ሕዝብህ ነንና አድነን ፣ ርስትህ ነንና ጠብቀን ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 9/ለ
ግንቦት 15 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም