የትምህርቱ ርዕስ | ረቡኒ/6

 ጌታችን የሴቶችን ሽቱ በሁለት ምክንያት አይቀባም ። የመጀመሪያው እርሱ ሕያው ነውና ለሙታን የተዘጋጀ ሽቱ አይቀባም ። መላእክትም “ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ?” ብለዋል ። በእውነት ሕያው ጌታን ሙት ከሆነው ዓለምና ኃጢአት መካከል አንፈልግም ። ከደጎች እንደ አንዱ ፣ ከቅዱሶችም እንደ አንዱ አይደለም ። እርሱ ልዩ ነው ። ጌታችን የሴቶችን ሽቱ ያልተቀባበት ሁለተኛው ምክንያት በትንሣኤ አካል እንደ ማርታ እንጀራ ቢያዘጋጁለት የሚበላ ፣ እንደ መግደላዊት ማርያም ሽቱ ቢያመጡለት የሚቀባ አይደለም ። በትንሣኤ አካል የሚቀባው የምስጋናን ሽቱ ነው ፤ ለስሙ ዕጣን ከፀሐይ መውጫ እስከ መግቢያው ይታጠንለታል ። አሁን ለእርሱ ሽቱ ከማምጣት በፊት ሽቱ ሁኖ መቅረብ ይገባል ። ጌታችን የተናገረው ስለ ሞቱ ብቻ ሳይሆን ስለ ትንሣኤውም ነው ። ሰዎች ትንሣኤ ቀድሞ ሞት ቢከተል ማዘናቸው ፣ ሞት ቀድሞ ትንሣኤ ቢሆን መጠራጠራቸው አይቀርም ። ዓለም እርግጠኛ ኀዘንና አጠራጣሪ ደስታ አላት ። እገሌ ወደቀ ሲባል ሁሉም ያምናል ፣ ተነሣ ሲባል ግን ላስብበት ይባላል ። ሞትን የሚቀበል አእምሮ ትንሣኤን አይቀበልም ። የሚያመነታ ማንነት ባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ ሲወዛወዝ የሚኖር ነው  ። መወዝወዙ በቀንና በሌሊት በመሆኑ ዕረፍት የለውም ።

ጌታችን እነሣለሁ ያለውን ቢያምኑ ኑሮ ብዙ ነገሮች ይወገዱ ነበር፡- ወደ መቃብሩ ከመገስገስ እቤታቸው ሁነው ይጠብቁት ነበር  ። በጨለማና በቋጥኝ ስጋት አይያዙም ነበር ። ሊጥሉት ሽቱ በመግዛት ገንዘብ አያባክኑም ነበር ። የእግዚአብሔርን ተስፋ አለማመን ዕረፍትን ያሳጣል ፣ ከንቱ ዋጋ መክፈልን ያመጣል ፣ ገንዘብን ያባክናል ። በተስፋውና በፍጻሜው መካከል ብዙ ነውጥ አለ ። እስራኤል 430 ዓመት በባርነት ኑረው አርባ ዓመት ግን በምድረ በዳ መታገሥ አቃታቸው ። ተስፋ ከተነገረ በኋላም መቅበጥበጥ ይኖራል ። መድኃኒቱ፡- “እኔ እግዚአብሔርን አልቀድመውም” ብሎ መታገሥ ብቻ ነው ። እግዚአብሔር ተስፋን የሚሰጠን ፡- ከመቅበዝበዝ ሊያድነን ፣ ባዶ ነገር ፍለጋ እንዳንሮጥና የሌለ ነገርን አለ ብለን እንዳንሰጋ ፣ ገንዘባችንም እንዳይባክን ነው ። በዚያ ሌሊት በአሳብ ተናጡ ። ቅዱስ ሥጋውን ላያገኙ ወደ ባዶ መቃብር ገሰገሱ ። ድካሙ ተጨባጭ ነው ፣ ውጤቱ ግን እንዳሰቡት አይደለም ። የሌለ ነገርን እንዳለ አሰቡ ። ነገር ግን ቋጥኙም ወታደሮቹም የሉም ። ስንደርስ ባዶ በሆኑ ነገሮች ፣ አሉ ብለናቸው በሌሉ ስጋቶች ፣ ገንዘባችንን በጨረስንባቸው ነገሮች ተጠያቂው አለማመናችን ነው ።
ሴቶች በኩሽና የተቆለፈባቸው ፣ የሠሩትን ምግብ እንኳ በሳሎን ለመመገብ ያልተፈቀደላቸው ፣ እንደሚናገር እንስሳ በሚታዩበት በዚያ ዘመን ሰማይና ምድር የሚጠብቁትን ትንሣኤ ለማየትና ለመመስከር በቁ ። በጣም በሰው መናቅ እንዴት መልካም ነው ! የምንከብረው በናቁን መጠን ነው ። ሰዎች ገፍተው የሚያደርሱን እግዚአብሔር ጋ ነው ። ዳዊት ቢንቁት ንጉሥ ሆነ ። እግዚአብሔር ውጭውን አያይም ፣ ዙሪያውንም አያማትርም ፣ የሚመርጠው በልባችን መሠረት ነው ። መናቅ ሰዎች ከፍ የምንልበትን ደረጃ መሥራታቸው ነው ። ከሰው ንቀት ከእግዚአብሔር ክብረት አይጠፋም ። ያከበርነው ሲያሳፍረን ፣ የናቅነው ግን ዝም ያሰኘናል ። ብርታታችንን የሚያበረቱ ፣ እሳትን የሚያቀጣጥሉ የሚንቁን ሰዎች ናቸው ። ባይንቁን ኑሮ የማንደርስባቸው ብዙ ከፍታዎች ነበሩ ። እግዚአብሔር ሆይ ስለ ናቁን ሰዎች ፣ ገፍተው አናት ላይ ስላወጡን ወገኖች ተመስገን ።
መግደላዊት ማርያም ከሌሎች ቅዱሳን ሴቶች ጋር ወደ መቃብሩ ብትጓዝም እርምጃቸው አላረካትም ። ልቧ ደርሶ ስለ ነበር እግሯ አልፈጥን አላት ። በብስጭትም ሩጫ ጀመረች ። ወደ መቃብሩ ቀድማ ደርሳ መቃብሩ ባዶ መሆኑን ስታይ ወደ ጴጥሮስና ወደ ዮሐንስ እንደገና ሮጠች ። ያደረሰችው ወሬ ጌታን ወስደውታል የሚል ኀዘን ነው ። አለማወቅ ደስታን ኀዘን ፣ እልልታን ልቅሶ አድርጎ ይውላል ። በምርኮው ቀን ጌታን ወስደውታል ብላ አዘነች ።
መግደላዊት ማርያም ሁሉም ጥለዋት ሄዱ ፣ እርስዋም ብቻዋን በመቃብሩ ስፍራ ቀረች ። ጌታን ያኖሩበትን ስፍራ ካላወቅሁ አልመለስም አለች ። መቃብሩን ማዶ ማዶ እያየች ታለቅስ ነበር ። የምታለቅሰው ለሞቱ ሳይሆን ለአሟሟቱ ፣ ጠላቶቹ ሞቶም ላልተኙለት ወዳጅዋ ነው ። እንደ ሞኝ ጠብ ጠባቸው ማለቂያ አጣ ። ዛሬም ገፍተውም ፣ አውግዘውም ፣ ሰድበውም ፣ ይሙት በቃ ፈርደውም የማያርፉ አሉ ። በሥራቸው ከማልቀስ ለሥራቸው ማልቀስ ዕረፍት ለማጣታቸው መንሰቅሰቅ ይገባል ።
ከእኛ በላይ ኃያል የለም ያሉት ሮማውያን ፣ ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉት ሰዱቃውያን ፣ ገደልነው ያሉት ፈሪሳውያን ፣ “አገር ከምትሞት ግለሰብ ይሙት” ያሉት ፀሐፍትና ዳኞች ፣ የራሳቸው ጠብ የሌላቸው አዳማቂዎች የክርስቶስ ትንሣኤ አሳፈራቸው ። ከሐፍረት ፍርሃት ይሻላል ። ፍርሃት መናጥ ነው ፣ ሐፍረት ግን በፈቃድ ልነቀል ማለት ነው ። ሰው የሚፈራው ራሱንና ሰዎችን ነው ። የሚያፍረው ግን ሰማይና ምድርን ነው ። ሰዎችን እያማናቸው ሲደርሱብን ፣ ስማቸው እገሌ ነው እያልን ስማቸው ሌላ ሲሆንብን ፣ ይጥፉ ብለን በላያች ሲሾሙብን ፣ ገደልን ብለን ሕያው ሲሆኑብን ፣ እናጥፋቸው ስንል ይበልጥ ሲበሩብን እናፍራለን ። ሐፍረት ሲኦልን በምድር መለማመጃ ነው ። ክርስቶስ ከሐፍረትን ሊያድነን ከሞት ተነሣ ። በሰማይ ታላቅ ዝማሬ በምድር ታላቅ ኀዘን ነበረ ። በሰማይ እውነቱ ፣ በምድር ስሜቱ አይሎ የተለያየ ድምፅ ተሰማ ። ከሰማያውያን ጋር አንድ ለመሆን ጌታ የተናገረውን መስማት በቂ ነው ። ሰማይና ምድረን አንድ የሚያደርግ የእርሱ ቃል ነው ። ሰማይ ተነሥቷል ይላል ፣ ምድር ተሰርቋል ይላል ። ሁሉም ነገር ከሰማይና ከምድር ሲያዩት ትርጉሙ ልዩ ነው ። ጌታችን የተነሣው ባዶ መቃብርና ምሉዕ ሕይወትን ለመስጠት ነው ።
የካህናት አለቆች የፈጠሩትን ውሸት አምነውታል ፣ “ውሸቴን እንዳላምነውና የአዞ እንባ እንዳላነባበት ጠብቀኝ” ማለት ትልቅ ጸሎት ነው ። የውሸት ክፋቱ ሲቆይ ባለቤቱንም ያሳምነዋል ። ውሸት ካፒቴኗ ሰይጣን ነው ። በአቡሀ ለሐሰት ነውና ። እነ መግደላዊት ማርያምም ወስደውታል የሚለው ስሜት ተቆጣጥሯዋል ። ሰው ልቡን የሚያምነውን ያህል ቃሉን አያምንም ። ሰይጣን ለአንዳንዶች በልባቸው ጥርጣሬን ፣ ለሌሎችም በጆሮአቸው ውሸት ይዘራል ። ማሳደጉ ግን የሰው ድርሻ ነው ።
በዚያች ሰዓት ያለው ልቅሶ ግምትን ማመን የወለደው ነው ። በግምት ስንት ትዳር ፈረሰ ፣ ስንት ወዳጅነት ሜዳ ቀረ ፣ የለፋንበትን ሳንለፋ በተንነው ። ጌታችን በሰማይ ያለውን ምስጋና እየሰማ በምድር ያሉ ወገኖቹን እንባ ያብስ ነበር ። ሰዎች ጠፍቷል እያሉ ያለቅሱልናል ፣ እኛ ደግሞ የጠፉት ፈላጊ የሆነው ጌታ ጋ ነን ። የሚለቀስላቸው ባለማወቅ ያለቅሱልናል ። ለማን እንደሚለቀስ አለማወቅ ከባድ ነው ። በደስታ ቀን ማዘን ፣ በእልልታ ቀን ማምረር በእውነት አለማመን ነው ።
ብዙ ጊዜ የሚሰሙ ክርክሮች አንድ ቀን ልባችንን እንደገዙት እናውቃለን ። አለመስማት በሚመስሉ መስማቶች እንደ ተሸረሸርን እናውቃለን ። በፈሪሳውያንና በሰዱቃውያን መካከል ትንሣኤ ሙታንን በሚመለከት ክርክር ነበር ። ማንበብና መጻፍ የማይችለው ሕዝብ ያልተጨበጡ ረቂቅ ነገሮችን አናምንም በሚለው በሰዱቃውያን ሳይንሳዊ ጉዞ ተስቦ ነበር ። ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉት የመቅደሱን ሥልጣን የያዙት ሊቃነ ካህናት ናቸው ። ፈሪሳውያን የሚባሉት ቡድኖች ዘርዐ ክህነት የሌላቸው ቀናዒነታቸው ያሰባሰባቸው እሳቶች ናቸው ። የመቅደሱ ሥልጣን ዘመናውያንና ቁሳውያን በሆኑት በሰዱቃውያን እጅ ነው ። መስመሩን ጠብቀው ስለ መጡ ሥልጣኑን በዘር ሐረግ ያገኙታል ። እምነት ግን የላቸውም ። መቅደሱ መሥሪያ ቤታቸው እንጂ አምልኮት መፈጸሚያቸው አይደለም ። ስለ ረቂቅ ነገርና ስለ ትንሣኤ አያምኑም ። ገንዘብ ሲባል ግን ንቁ ናቸው ። ፈሪሳውያን ደግሞ ድህነትን እንደ ጽድቅ የሚያዩ በድብቅ ግን ገንዘብ የሚያከማቹ ፣ ቀናዒ ነን በማለት እንቢ ለአገሬ ፣ እንቢ ለሃይማኖቴ በማለት የዋሁን ሕዝብ ልቡን የሰለቡ ናቸው ። አመለካከታቸው ጥልቅ የነገረ መለኮት እሳቢ ስለሌለው ለብዙኃኑ ተስማሚ ናቸው ። የላኛው አካል ከሀዲ ፣ የታችኛው ደግሞ የሃይማኖት እውቀት የሌለው ወገኛ ቡድን ነበር ። ሕዝቡ በእነዚህ ሁለት ቡድኖች ተውጦ እግዚአብሔርን ማየት አልቻለም ። ደቀ መዛሙርቱ  ትንሣኤ ሙታን የለም በሚለው ከሀዲዎች ንግግር አእምሮአቸው ተሞልቶ እነሣለሁ ያለውን ለማመን ፣ በባዶ መቃብር ፊት ለፊት ለመዘመር ለጊዜው አልታደሉም ። ዛሬ ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉ አስተማሪዎች በመካከላችን አሉ ። አዲስ መገለጥ ሳይሆን ሰዱቃዊ እንደሆኑ ዘንግተዋል ። እንኳን አዲስ እውቀት ፣ አዲስ ኑፋቄም የለም ።
ጌታችን ትልቁን ትንሣኤ ያምኑ ዘንድ ከሳምንት በፊት አልዓዛርን ከሞት በማሥነሣት አለማምዶአቸዋል ። እርሱ የሰውን አቅም ያውቀዋልና ቀድሞ ያዘጋጃል ። ከሁሉ በላይ እነሣለሁ ባለው ቃሉ ሊያምኑት ይገባል ። እግዚአብሔር የእሳት ላንቃ ነው ፣ መያዣ የለውም ፤ የሚያዘው በቃሉ ነው ።
መግደላዊት ማርያም ወደ መቃብሩ እያየች ስታለቅስ በመቃብሩ ራስጌና ግርጌ ሁለት መላእክት ታዩአት ። መላእክቱ የተገለጡት በጎበዝ አርአያ ነው ። እግዚአብሔር ኃያል ነው ማለታቸው ነው ። ነጭ ልብስ ለብሰዋል ። ጽድቅ አሸነፈ ፣ ደስታ ተበሠረ ማለታቸው ነው ። “አንቺ ሴት ስለምን ታለቅሻለሽ?” አሏት ። ለምን እንደምታለቅስ ያውቃሉ ። ችግሯን በገዛ አንደበቷ ስትናገረው ይቀላታልና ጠየቁአት ። የዚች ሴት ልቅሶ ጓደኞቼ አግብተው እኔ ብቻ ቀረሁ የሚል አይደለም ። ሳልወልድ ጊዜ ተላለፈኝ ብላም አይደለም ። ልቅሶዋ “ጌታዬን ወስደውታል” የሚል ነው ። መግደላዊት ማርያም ሁሉም ጥለዋት ቢሄዱ ጨክና ተቀመጠች ። ሃይማኖት ግራና ቀኙን ሳያዩ እግዚአብሔርን ብቻ መከተል ነው ። መግደላዊት ማርያም ምላሽዋ ወስደውታል የሚል ነው ። መግደላዊት ማርያም ሌላ መቃብር ላይ ቀብረውታል የሚል አሳብ ገብቷታል ። ስለ ሁለት መቃብር ታስባለች ። አንዱም እንደ ፈረሰ ረስታለች ። ብቻ “ጌታዬን ወስደውታል” አለች ። ሞቶም ጌታዋ ነው ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 8  ረ
ሚያዝያ 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም