የትምህርቱ ርዕስ | ረቡኒ

 “ኢየሱስም፦ ማርያም አላት ። እርስዋ ዘወር ብላ በዕብራይስጥ፡- ረቡኒ አለችው ፤ ትርጓሜውም፡- መምህር ሆይ ማለት ነው ።” ዮሐ. 20፡16
. . .
“ይትፌሣሕ ሰማይ ወትትሐሠይ ምድር ወይንፍሑ ቀርነ መሠረታተ ሕምዝ ወይወውዑ አድባር ወአውግር ወኩሉ ዕፀወ ገዳም ወዮምሰ ዐባይ ፍሥሐ በሰማያት ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ” /መጽሐፈ ድጓ/
ትርጓሜ፡-
“ሰማይ ይደሰታል ፣ ምድርም ትደሰታለች ፣ የምድር መሠረቶችም ቀንደ መለከትን ይንፉ /ይደሰቱ/ ፤ ተራሮችና ኮረብቶችም /ነገሥታት መኳንንት/ ይጩኹ/ይደሰቱ/ ፣ የምድረ በዳ እንጨቶችም ይጩኹ ፣ ዛሬ በሰማያት ታላቅ ደስታ ሆነ ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካን/ደስታን/ ታደርጋለች ።”
. . .
የጥቁሮች መብት ታጋይ የነበረው ማርቲን ሉተር ኪንግ፡- “ከዋክብትን ማየት የሚቻለው በጨለማ ብቻ ነው” ብሏል ። ጨለማው የሚሰውራቸው ተራሮች አሉ ፣ ጨለማው የሚገልጣቸው ከዋክብት ደግሞ አሉ ። ጨለማው የሚሰውራቸው የቅርብ ከፍታዎች አሉ ፣ ጨለማው የሚገልጣቸው የሩቅ ብርሃናት አሉ ። በቀን የሚታዩ ኮረብታዎች በማታ አይታዩም ። ሰርጋችንን ያጀቡ መከራችንን ማጀብ አይፈልጉም ። ቍስላችን ላይ እንጨት የሰደዱ መከራቸው ላይ እንድናለቅስ ይፈልጋሉ ። አመመኝ እንጂ ያማቸዋል የማይል ሰው ከሁሉ ይልቅ አላዋቂ ነው ። ራስን ብቻ እያዳመጡ መኖር ብቸኛ ያደርጋል ። ሥልጣን ፀሐይ ነው ፣ ብዙ ሰዎችን በፊታችን ይኮለኩላል ። ሰው ባይኖረንም ያለን አስመስሎ ያደነዝዘናል ። ሀብትም ደስታን ሳይሆን ሳቅን ፣ የልብ አክባሪዎችን ሳይሆን አንገት አዘቅዛቂዎችን ያተርፍልናል ። ዝናም እንደ ጎርፍ ጠርጎ እስኪወስደን ሳቅ ፣ ሳቅ ይለናል ። እዩኝ እዩኝ ማለትም ደብቁኝ ፣ ደብቁኝ ያሰኛል ። የከበቡን ብዙዎች ሲበተኑ የሚቀሩ ትንሽ ከዋክብት አሉ ። እነዚህን በሰላም ቀን ለማየት ዓይን አላበጀንም ነበር ። ጨለማው ግን ያበሩ ፀሐዮች የሚጨልሙበት የተሰወሩ ከዋክብት የሚገለጡበት ነው ። ይህ ሰዓት ባይኖር የእውነት ሳይሆን የግምት ነዋሪዎች እንሆን ነበር ። መግደላዊት ማርያም በጨለማ ሰዓት የታየች ኮከብ ናት ። መከራውን የተካፈሉ ደስታውን ያያሉ ። ቀድመው የመጡ የምሥራቹን ቀድመው ይሰማሉ ። በዋጋ እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ዋጋቸው ከፍ ይላል ።

የለመድነው አለ ብለን ያልነው ነገር ስንደርስ መሞቱ ነው ። አለው ብለን የገሰገስንበት ስናገኘው ለማኝ ሁኖ ፍርፋሪ መልቀሙ ነው ። ቁንጅናው እየገረመን በድሮ መልኩ የመዘንነው ስንደርስ እንደ አበባ መርገፉ ነው ። በዓለም ላይ የምንጠብቀውን ብቻ ሳይሆን የማንጠብቀውንም እንድንቀበል ሕይወት ዕዳ ጥላብናለች ። መግደላዊት ማርያም የገጠማት ግን በተቃራኒው ነው ። ሞትን ስትጠብቅ ትንሣኤ ፣ በድን እየፈለገች ሕያውን አገኘች ። ፍቅሩን ሞት አልወሰደባትም ። ፍቅር ዘላለማዊ የሚሆነው በሞት ነው ። እየወደድናቸው የሞቱ ፍቅራቸው በውስጣችን ተቀብሮ ይኖራል ። ጌታ የሞተው በፍቅሩ ፣ የተነሣው በኃይሉ ነው ። ካህናት ያወገዙትን ፣ ነገሥታት የፈረዱበትን ብትክድ ኖሮ ረቡኒ እያለች አትፈልገውም ነበር ። ፍቅር በፍቅር እንጂ በድምፅ ብልጫ አይወስንም ። ካህናትና ነገሥታት በእውነት ይመዘናሉ እንጂ እውነት በሰዎች አትመዘንም ። እውነት ነገሥታት እየፈረዱባት ፣ ካህናት እያወገዙአት ፣ አፈኞች እያሳደሙባት ፣ ጉልበተኞች እየዛቱባት ፣ ገንዘብ የበሉ የሐሰት መስካሪዎች እያሳበሏት ፀንታ ትኖራለች ። የእውነት አገሯ ወዴት ነው ? ብንል እውነት አገር የላትም ። አገራት ሁሉ በእውነት ውስጥ አሉ ። መግደላዊት ማርያም ፍቅሯ በፍቅር ላይ የተመሠረተ ነበር ። ልቧ ስለ ክርስቶስ እየነገራት ዙሪያዋን አታዳምጥም ነበር ። በዓይን የሚያዩትን በጆሮ መፈለግ ያላዋቂዎች ኑሮ ነው ። ከመንፈስ ቅዱስ ምስክርነት ወጥታ ወደ ደጋፊዎች ድጋፍ ዝቅ አላለችም ። የሆነላትን ታውቀዋለችና የሆነልኝ ምንድነው ? ብላ ጎረቤት አልጠየቀችም ። ይህ ስሜ ማነው ? እንደ ማለት ያህል ነው ። ሁሉን ይወርስ ዘንድ አምላኳ ሞተ ተባለ ። የሕያዋንና የሙታን ጌታ ይባላልና ።
ካህናትና ነገሥታት ተስማምተው የገደሉትን ሴቶችና መላእክት ተስማምተው እያመሰገኑት ነው ። አጋንንትና የሮማ ወታደሮች ይጠብቁት የነበረውን መቃብር ቅዱሳን መላእክት ድንጋዩን አንከባለው እያሳዩት ነው ። ባዶ ነገር ተጎብኝቶ አያውቅም ። የክርስቶስ መቃብር ግን ከተጎበኙ ነገሮች ሁሉ ይልቅ እስከ ዛሬ ድንቅ ስፍራ ነው ። በጉብኝት ስፍራዎች ላይ ታሪክ አዋቂዎች ወይም ጆሮ ጠገቦች ያስጎበኛሉ ፣ ቅዱሳን መላእክት ያስጎበኙት ግን ባዶው የክርስቶስ መቃብር ነው ። ቤተ ልሔም ጊዜያዊ ጽርሐ አርያም ሁና መላእክት ዘመሩባት ። በትንሣኤው መላእክት በምድር ምስክርነት ፣ በሰማይ ምስጋና አሰሙ ። አምላኩን በመግደሉ በሰው ደንግጦ የነበረው ፍጥረት በትንሣኤው ተረጋጋ ። ሰውን ፈርቶ የነበረው የምድርና የሰማይ ሠራዊት ለሰው በተከፈለው ዋጋ ሰው ትልቅ ነው አለ ። ሞት እንደ እንቅልፍ ፣ ቋጥኝ እንደ ጠጠር ፣ ወታደሮች እንደ ሕፃናት ፣ ወርቅና ገንዘብ እንደ ዝገት ፣ ጉልበት እንደ ውድቀት የሆነባት ያች የክርስቶስ ትንሣኤ ቀን ምንኛ ትደንቅ ! ክርስቶስን ለማሥነሣት የመጣ መልአክ የለም ፣ ክርስቶስ መነሣቱን ለማብሰር ግን መልአክ መጥቷል ። በዳግም ምጽአት ሙታን ይነሡ ዘንድ የመለከት ድምፅ የሚነፋው ያ መልአክ ነው ። ትንሣኤው ትንሣኤያችንን ካላስታወሰ ክርስቶስ በከንቱ ተነሣ ይባል ነበር ። መግደላዊት ማርያም አምላኳን እንደ ሳለችው ሳይሆን እንደ ራሱ አገኘችው ። ለሕያውነቱ የሚወርደውን የመላእክትን ምስጋና ስትሰማ ለሙታን የሚሆነውን ሽቱ ጣለችው ። ደስታ የሚጥል ቢሆንም የእግዚአብሔር ደስታ ግን የሚያቆም ነው ። ደስታችንን እንቋቋም ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ይደግፈናልና ። መግደላዊት ማርያም ፀናች ። ብሥራቱን በመልአክ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሰማች ፣ ትንሣኤውንም መልአክ ለመግደላዊት ማርያም አበሰራት ። ብሥራቱ ለተቀደሰችው ለቅድስተ ቅዱሳን ለድንግል ማርያም ተነገረ ፣ ትንሣኤው ወድቃ ለተነሣቸው መግደላዊት ማርያም ተሰበከ ። ድንግል ማኅፀኗን ያድርበት ዘንድ ተበሠረች ። መግደላዊት ማርያም ያደረበትን መቃብር ታይ ዘንድ ተጋበዘች ።
ነገሥታት ግብዐ መሬታቸው ሲፈጸም መድፍ ይተኮሳል ፣ ክርስቶስ ግን ነፍሱን ሲሰጥ ምድር ተናወጠች ። የያዘቻቸውንም ሙታን ተፋች ፣ ብዙ ቅዱሳንም ተነሡ ። ነገሥታት ጉዞ ሲጀምሩ የደስታ መሣሪያ ይተኮሳል ። የነገሥታት ንጉሥ ክርስቶስ ሲነሣም ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ ። በንጉሡ ፊት ወታደሩ እየቀደመ ንጉሥ መምጣቱን ያበሥራል ፣ መልአኩም ትንሣኤን አበሰረ ። ሙትልን የማይሉት ብዙ ቅዱሳን ሳሉት ለእኛ መሞቱ ይደንቃል ።መላእክት ዓርብ ዕለት ተደነቁ ፣ እኛ እሑድ ዕለት ተገረምን ። የሕይወት ባለቤት ሲሞት መላእክት አረመሙ ። ሞት ድል ሲነሣ የሰው ልጆች ተገረሙ ። ርኩሳን ሰዎች የዘበት ስግደት ዓርብ ዕለት ያቀረቡለትን መላእክት በሰው ዓለም ላይ ቆመው ሰገዱለት ። ጎልጎታ ከሰማይ በልዩ አትኩሮት ትታይ ነበር ። ጥቂት ሴቶች የተገኙበትን መቃብር እልፍ አእላፋት ወትእልፊት የሚሆኑ ቅዱሳን መላእክት ከሰማይ በጽሞና ያዩ ነበር ። ዓርብ ዕለት ቢቀየሙን ኑሮ መላእክት እሑድ ዕለት አይመጡም ነበር ። የጌታቸው ይቅርታ ወርሶአቸዋል ። የወዳጅ ልጅን ማየት በጣም ደስ ይላል ፣ ሰው በተፈጠረ ጊዜም የእግዚአብሔር ወዳጆች መላእክት አዳምን ወደውት ነበር ። ሰው በዋጋ ተፈጥሮ ያለ ዋጋ በሞተ ጊዜ አዘኑ ። ትንሣኤውን ሲያዩ ግን የወዳጃቸው ልጅ እንደሚነሣ ፣ የሰው መጨረሻ ሞት እንዳልሆነ በማሰብ እፎይ አሉ ። በአንድ ኃጢአተኛ መመለስ በሰማይ የሚዘምሩ መላእክት ለኃጢአተኞች ሁሉ በተከፈለው ዋጋ በትንሣኤው ደስ ቢላቸው የሚጠበቅ ነው ። መላእክት ወዳጆቻችን ናቸው ። ሰይጣን ጠላታችን ነው ስንል የምንውል ፣ መላእክት ወዳጆቻችን መሆናቸውንም መናገር አለብን ።
ሰው የሚከብረው በእግዚአብሔር ነው ። ይድን ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋንና ነፍስን ከድንግል ነሣ ። አሁንም በትንሣኤ ሥጋው ሲነሣ ፣ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሶችን ሲማርክ የሰው ሥጋና ነፍስ በድል ሽቱ ታወደ ።መቃብር  መወርወሪያውና ቁልፉ ተሰበረ ። መቃብር የታተመ ሳይሆን እስከ ምጽአት ገርበብ ያለ በር ሆነ ። ለዘመናት እስር ቤት በር አለው ፣ መቃብር ግን በር የለውም ሲባል ኖረ ፣ ዛሬ ግን በክርስቶስ ትንሣኤ መቃብር በር አገኘ ። ዓለም ክርስቶስን ስትሰቅል ቀኑ ጨለመ ፣ ክርስቶስ ሲነሣ ሌሊቱ በራ ። በታሪካችንና በምርጫችን እርሱን ስንሰቅለው ቀኑ ይጨልማል ፣ የሚቻል ነገር የማይቻል ይሆናል ፣ የመጣውም ይርቃል ። ክርስቶስ ሲነሣ ደግሞ የአገር ጽልመት ይገፈፋል ፣ የትውልድ ውድቀት ትንሣኤ ያገኛል ። መግደላዊት ማርያም አንድ ነገር እያሰበች ወደ መቃብሩ ትገሰግሳለች ። ትንሣኤው ግን ብዙ አስተንትኖ ይዟል ። ዘማሪዋ እንደ ዘመረችው ነው፡-
እዩት ኢየሱስን መስቀሉ ማማሩ ፣
ለተመራመረው ብዙ ነው ምሥጢሩ ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 8 ሀ
ሚያዝያ 20 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም