መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የጻፍክልኝ ሕይወት ነው

የትምህርቱ ርዕስ | የጻፍክልኝ ሕይወት ነው

የጻፍከኝ በብራና አይደለም ፣ የጻፍከኝ በልብህ ነው ፤ ስለዚህ ሊሰርቅ የሚመጣው ሌባ አያገኘኝም ። የጻፍከኝ በቀለም አይደለም ፣ የጻፍከኝ በደምህ ነው ፤ ስለዚህ የጠላት ብዛት አያጠፋኝም ። የጻፍከኝ በአሸዋ ሰሌዳ አይደለም ፣ የቀረጽከኝ በዓለት ላይ ነው ፤ ስለዚህ የዘመን አቧራ አይሸፍነኝም ። የጻፍከኝ በወረቀት ላይ አይደለም ፣ የጻፍከኝ እንዳትረሳኝ በመዳፍህ ላይ ነው፤ ስለዚህ በረከቴ ፈጣን ነው ። የጻፍከኝ ልትደመስሰኝ አይደለም ፣ የጻፍከኝ ለዘላለም ነው ፤ ስለዚህ ነገ አያሰጋኝም ። የጻፍከኝ ለገበታ ላይ አይደለም ፣ የጻፍከኝ ለበጉ ሰርግ ነው ፤ ስለዚህ የማያልፍ ዓለም አለኝ ። የጻፍከኝ በሞት መዝገብ አይደለም ፣ የጻፍከኝ በሕይወት መጽሐፍ ነው ፤ ስለዚህ የሞት ግርማ አያስደነግጠኝም ። የጻፍከኝ በአሳሳቢ አይደለም ፣ የጻፍከኝ በፍቅርህ ነው ፤ ስለዚህ በሰዎች ሐሜት አትጠላኝም ። የጻፍከኝ ለኮንትራት አይደለም ፣ የጻፍከኝ በማይፈርስ ውል ነው ፤ ስለዚህ ታምነህ አትከዳኝም ። የጻፍከኝ ዕዳ አለበት ብለህ አይደለም ፣ የጻፍከኝ ዕዳው ተከፍሎለታል ብለህ ነው ፤ ስለዚህ ወደ ቤትህ ስመጣ አታሳቅቀኝም ። የጻፍከኝ ለውግዘት አይደለም ፣ የጻፍከኝ ይቅር ለማለት ነው ፤ ስለዚህ አክብረህ አታዋርደኝም ።
የጻፍከው የትላንት ታሪኬን የዛሬ ድካሜን አይደለም ፣ የጻፍከው የነገ ተስፋዬን ነው  ። የጻፍከኝ ከአገር እንዳይወጣ ብለህ አይደለም ፣ የጻፍከኝ መንግሥቴን ሰጥቼዋለሁ ብለህ ነው ። የጻፍከኝ ከውርስ ይነቀል ብለህ አይደለም ፣ የጻፍከኝ የእኔ ሁሉ የእርሱ ነው ብለህ ነው ። የጻፍከኝ ለሞት አይደለም ፣ የጻፍከኝ ለሕይወት ነው ። የጻፍከው የሕይወቴ መጽሐፍ መግቢያው ፍቅርህ ፣ ማጠቃለያው መንግሥትህ ነው ።
የጻፍክልኝን አታሎ ማንም አይወስደውም ። የጻፍከውን የከሳሽ ብዛት አይሰርዘውም ። የጻፍክልኝ ያለው በልብ ነውና ሌባ አይሰርቀውም ። ለእኔ ያልከው ለሌላ እንዳይሆን ለአንድ ሰው ብቻ የሠራኸው ነው ። የጻፍክልኝ የማይኮረጅ ጥበብ ያለበት ነው ።
እንደ ጻፍክልኝ ልኑር ። እንደ ጻፍክልኝ ልቅር ። በጻፍከው ላይ ደርቤ ልጻፍ ። የጻፍክልኝን እንዳልሰርዝ እርዳኝ ። እንደ ጻፍክልኝ ልገለጥ ። እንደ ጻፍክልኝ ልዋል ። እንደ ጻፍክልኝ ልጓደድ ። የተጻፈልኝን ትቼ የተጻፈላቸውን እንዳላይ ዓይኔን ከምቀኝነት ጠብቃት ። እግሬንም በጽሕፈቱ ፈለግ ምራት ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይሁን ። ከልባችን እስከ አርያም ፣ ከምታልቀዋ ከዛሬዋ ቀን እስከ ዘላለም ድረስ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 21
መጋቢት 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም