መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የፈጠርከውን አክብረው

የትምህርቱ ርዕስ | የፈጠርከውን አክብረው

 ከተጻፈው በላይ የሆንህ ፣ ከተዘመረልህም ይልቅ ድንቅነትህ የሚያበራ ፣ ከተሰበከው ጠልቀህ የምትኖር ፣ ከተቀደሰው ቅዳሴ በላይ መዓዛህ ልዩ የሆነ እግዚአብሔር አንተ ነህ ። የአቅማችንን ያህል እናመስግንህ እንጂ ይህ ልክህ ይህ መጠንህ አይደለም ። ምስጋናን የከንፈር ፍሬ ፣ መላ ሕይወታችንን የሚቃጠል መሥዋዕት ፣ በመጠን መኖራችንን የእህል ቊርባን ፣ ፍቅራችንን የኅብረት መሥዋዕት ፣ ንስሐችንን የኃጢአት መሥዋዕት ፣ ዓለም በቃኝ ማለታችንን የበደል መሥዋዕት አድርገን እናቀርብልህ ዘንድ እንወዳለን ። መሻት እንጂ አቅም የለንምና ካለ መቻል ታድነናለህ ። በፊትህ ሁሉም ነገር የተገለጠ ፣ የተራቆተና ባዶ የሆነ የካህናት አለቃ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የአሳባችንን ብክለት በመንፈስህ አየር አንተ ለውጠው ። በፊትህ እኛን ሁነን ስንመጣ ያንተ አድርገህ መልሰን ። ስንጀምር አንተ ፈጽምልን ፣ ስንፈጽምም ጅማሬአችንን እይልን ። የእኛ ጅምር ማለቅ ፣ የእኛ ፍጻሜ ደስታ የለውምና አንተ አግዘን ። የሚበጀንን ባለ ማወቅ በሞት ሰፈር የምንኖር ፣ እውቀት ተስኖን የእሳትን ውበት እንጂ ማቃጠል የማንለይ ልጆችህ ነንና አድገን እናሳርፍህ ዘንድ ሠርተህ ፈጽመን ። የምስጋናን ዘውድ ጭነህ ፣ በግርማ ተከበህ ፣ በራስህ ክብር ደምቀህ ትኖራለህ ።
የሰጠኸው እንጂ የሰጠህ ፣ የሾምኸው እንጂ የሾመህ ማንም የለም ። እንደማትችል ዝምታህ ፣ እንደማይሰጥ መዘግየትህ ይደንቃል ። ልቤ እንደ መሰንቆ ሁኖ አንተን ቢያከብርህ ፣ ዓይኔ እንደ ዋሽንት ሁኖ አንተን ቢያስስህ ፣ እጄ እንደ በገና ሁኖ ንጉሥነትህን ቢተርክ እመኛለሁ ። ዝንጉዎችን በማስታወስ ፣ አላዋቂዎችን በአእምሮ የምትባርክ እኔ መሪያቸው ነኝና እባክህ አበርታኝ ። የሰጠኸኝን ሳላየው ሌላ ያምረኛል ፣ በምንጩ አጠገብ ቆሜ የጥማት ሲቃ ይተናነቀኛል ። የሌለኝን ከመስጠትህ በፊት ያለኝን አሳውቀኝ ። መቶ የበሽታ ዝርዝር ቢመጣ ዘጠና አምስቱ የለብኝም ። ጌታ ሆይ ስለበዛው ጤና የማመሰግንህ ከቶ መቼ ነው ። ፀሐይ ባሪያህ ሁና ሳይደክማት ታበራለች ፣ አንተ ግን የዓለም ብርሃን ባልካቸው ልጆችህ መብራትነት ትደሰታለህ ። ባንተ ዘንድ የተወደደ መሥዋዕት አቀርብልህ ዘንድ እጄን በአምኃ ፣ አፌን በምስጋና ፣ ልቤን በመወሰን ባርክ ። ሕዝቡ ያንተ ነውና እንደ ጎርፍ ወደ ጥፋት ሲሄድ መልሰው ። የምድር መሪዎች የሚመሩትን ንቀው የሚናገሩት ሁሉ ቀላል ንግግር ነው ። የፈጠርከውን ወገን አንተ አክብረው ።
ተራራው ላይ ስወጣ ሁሉ ይታየኛል ። ወደ ተራራ ለመውጣት ግን ድካሜ ያሳስበኛል ። ያደከመኝ ተራራ ከፍታ እንደሚሆነኝ እባክህ አስረዳኝ ። ያልተገፋ ራስ ላይ አይወጣም ። የጎን ጦር የሌለበትም ስለ ዕድገት አያስብም ። ዛሬ የደረስኩበት ነገር ሁሉ ጠላቶቼ ላጥፋህ ሲሉ ያበሩኝ ነውና ጠላቶቼን ባርክልኝ ። ፈርዖንን አስነሥተህ እስራኤልን ለንስሐ የጋበዝህ ፣ የተመቻቸው ባሪያ ከመሆን ነጻነት ያላቸው ድሆች እንዲሆኑ ያነቃቃህ ፣ በክፉዎችም እየሠራህ ልጆችህን የምታበረታ አንተ ነህ ።
የምስጋናህ ጤዛ ነፍሴን ያርሳት ፣ የክብርህ ጠል ይረፍብኝ ። ያነሰ ኑሮ ከመኖር ፣ ዝቅ ባለ አስተሳሰብ ዝቅ ከማለት ጠብቀኝ ። ዘመንን የማይብህ ዓይኔ ነህ ተመስገን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /8
የካቲት 28 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም